Monday, October 22, 2012

አፋዊነት… (Sweet Talk)



በብርካን ፋንታ

ሁላችን ከሆንን የቋንቋ ፈላስፋ
በተግባር መስካሪ አንድም እንዳይጠፋ

ይህ የእዮብ መኮንን ዘፈን ግጥም የዚህን ጽሑፍ ገዢ ሐሳብ ይገልፃል፡፡ ሲነገር ከንፈር የማያደናቅፍ፣ ሲደመጥ ጆሮ የማይኮረኩር፣ በአዕምሮ ሲሰላሰል የማይጎረብጥ በተግባር መሬት ላይ የማይተገብሩት የአፍ ፈሊጥ /leap service/ በከተማችን በርክቷል፡፡ በጊዜ ብዙ ሰዎችን ታዝበናል፡፡ድሮም ትልቅ ነበርክየሚል የግጥም ፉካሬ በጌትነት እንየው ከመስማት በላይ፣ በፍትህ ጋዜጣመንግስት መዶሻ ነው፤ ሕዝብ ደግሞ ምስማርሲለን ከነበረ አምደኛግድቡ በአቶ መለስ ይሰይምምስላቸው በብር ይታተምየሚል ጭብጥ የያዘን ተውኔት ድርሰት ከማየት በላይ፤ ወደ መልካምም ወደ ክፉም አገራችንን በሚመራው በዛች ቀውጢ ሰዐት ፍፁም ከሚያምኑት “Meles Zenawi is back in town” የሚል ዘገባ ከማንበብ በላይ፤አገር ማለት የኔ ልጅየሚል ውብና ጥልቅ መልዕክት ያለው ግጥም ገጣሚ / በድሉ ዋቅጅራ በፍትህ ጋዜጣ አምደኛ በሆኑ ማግስት ለጠ/ሚሩ መታሰብያ ግጥም መድረክ ላይ ሲያነበንቡ ከማየት በላይ ሌላ የመከዳት ስሜት የሚፈጥር ምን ነገር አለ?! ምንም የለም!

ይህ ጽሑፍ የአቶ መለስ ዜናዊን መልካም ያልሆነ አስተዳደር ለመተችት የተነሳ አይደለም፡፡ ወትሮም አቶ መለስ በሕይወት በነበሩበት ጊዜ የሚበጀንን ነው የሚያደርጉት ብለው ሲሞግቱ ለነበሩትም አይደለም፡፡ ክፉ ናቸው፤ በደለኛ ናቸው የሚል ወንጀል ሲያቀርቡ የነበሩት ሲሞቱ ደግሞ በተቃራኒው መላዕክትነታቸውን ሲሰብኩ ለከረሙት ታዝበናል፣ አይተናል ለማለት ነው፡፡ የቀድሞ / ተፈጥሯዊ ሞት የአንዳንድ ግለሰቦች ጭንብል አስወለቀ እንጂ ይህ ችግር በአደባባይ መታየት ከጀመረ ሰንበቷል፡፡ አቶ መለስ ዜናዊ ራሳቸው የተሳተፉበትእንደገናየተሰኝ ዘጋቢ ፊልም ላይ እንዲህም የሚል የአፍ ፈሊጦችን አድምጠን ነበረ፡፡

ዋናው ሕሊና ነውሕሊና ደግሞ ከሁሉም በላይ ነው መሆን ያለበት! ፍትሕ፣ ስርዓት ሁል ጊዜ ፐርፌክት አካሄድ ከሄደ በዚች ምድር፣ በዚች አገር ምንም አይከሰትም፡፡
(
አትሌት ኃይሌ /ሥላሴ)

ይህን የተናገረው 1997 ምርጫ ምክንያት በታሰሩ የፓለቲካ እስረኞች እና መንግስት መሐል በሽምግልና የተሰየመው አትሌት ሻለቃ ኃይሌ /ሥላሴ ነው፡፡ ወዳጄ እንደሚለው ኃይሌ እግረ ብርሃን እንጂ ልበ ብርሃን እንዳልሆነ አልዘነጋሁም፡፡ ሆኖም ግን በአፈጠጠ እውነት ላይ ተደራድሮ እስረኞቹን 12 ዓመት ሕፃን ባንክ እንዲዘርፍ ልከን አሳስተን ነው ያስገደልነው የሚል የይቅርታ ሰነድ ሕሊናው እየተመለከተ ፈርመዋል፡፡ ያን ጊዜ ሕሊናውን ከወዴት ሰውሮት እንደነበረ አላውቅም፡፡ በየትኛው የሞራል እርከን ላይ ቆሞ ሰለሕሊና እንደሚሰብክም አይገባኝም፡፡ ዛሬ የስፖርት ጋዜጠኛ ፍስሐ ተገኝና የመሳሰሉት ሕሊና እያለን ያልተፈፀመውን 11 ዓመት ታዳጊ ባንክ ሊዘርፍ ነበር የሚል ዜና አላነብም ሲሉ ከአገር ተሰደው እየኖሩ ነው፤ እነኃይሌ በአንፃሩ ዋናው ነገር ሕሊና ነው እያሉን ነው፡፡ ታዲይ ይህ ምንድን ነውይህ የአፍ ፈሊጥ ነው፡፡

ዋናው ነገር አባይን እገድባለሁ ብሎ ማሰቡ ነው ትልቅ የሚያደርገንለእኔ አባይን እንገድባለን ብለንማሰባችነው ዋናው ቁም ነገሩ!…አገራዊ ጉዳዮችን መለየት አለብን፤ ያለንበት 21ኛው መቶ ክፈለ ዘመን የተለያዩ ፓርቲዎች፤ የተለያዩ ርዕዮት ዓለሞች፣ የተለያዩ የአሠራር መንገዶች የተለያዩ ነገሮች ያለበት ነው፡፡ እብርነት ውበትነት የሆነበት ዘመን ላይ ነው ያለነው፤ ከዚህ ውጭ መሆንም አንችልም፡፡ ግን እንደገና ደግሞ እነዚህን ሁሉ የሚያስተባብር አንድ ነገረ አለ፤ እርሱም ኢትዮጵያ የሚባል ነገር አለየፖለቲካ ፓርቲዎች ልንመሠርት የምንችለው፣ ልንከራከር የምንችለው፣ አሸንፈን ፓርላማ ልንገባ የምንችለው፣ ተሸነፈን ልንወርድ የምንችለው፣ ኢትዮጵያ የምትባል አገር ስትኖር ነው፡፡
(
ዳንኤል ክብረት)

ጤናማ ሞራል እንዲኖረን በጽሑፉ የሚተጋው፣ታሪኩን የዘነጋ ትውልድ እንደተፈጠረ በበሰለ ጽሑፍ ሸንቆጥ የሚያደርገው፣ ወጋችንን ተረታችንን መዘንጋት እንደሌለብን የሚያስታውሰው፣ ከድንጋዩ ይልቅ ሰዉ ክቡር እንደሆነ የሚመክረው ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በቀረበው ዘጋቢ ፊልም ከተናገረው የተቀነጨበ ነው፡፡ ከአፄ ልብነድንግል ጀምሮ አባይን ለመገደብ ሐሳብ የነበራቸውን ነገሥታት ታሪክ ዋጋ በማሳጣት ዛሬ እንገድባለን ብለንማሰባችንብቻትልቅእንደሚያደረገን ሰብኮናል፡፡ ኢትዮጵያ የምትባል ነገር ያለ ሕዝብ ነጻነት በፍትሕ ላይ ባልተመሰረተ የፖለቲካ አስተዳደር ልትፀና እንደምትችል ከታሪክ አስታዋሻችን ምክር እየተለገሰን ነው፡፡ ይህ የዳንኤል ንግግር ከአፍ ፈሊጥነት እና ገዢው ፓርቲ ላዘጋጀው ፕሮፓጋንዳ ማጣፈጫነት የዘለለ ምን ውሃ የሚያነሳ ነገር አለው?ምንም! ይሄም የአፍ ፈሊጥ ነው!

እነዚህ ለአስረጅነት ቀረቡ እንጂ በፖለቲከኛው፣ በኪነ ጥበበኛው፣ በጋዜጠኛው፣ በነጋዴው፣ በሐኪሙ እና በሌሎችም በቀላሉ ማንም ሊያስተውለው የሚችል አገራችንን ወግቶ የያዘ ችግር ነው፡፡ ይህ አፋዊነት በዚሁ ከቀጠለ በአገራዊ ደረጃ የሚያመጣው ልክ ያልሆነ የትውልድ አስተሳሳብ ብዙ ዋጋ ያስከፍላል፡፡

አሲምባ ተራራላይ ውረዱ!


በእውቀቱ ስዩም “ኗሪ አልባ ጎጆዎች” ባሰኘው ግጥሙ ውስጥ አያቶች የወጠኑትን፣ አባቶች የገነቡትን ቤት ልጆች ምን እንደሚሉት በቅኔ ወርዶት ሲያበቃ እንዲህ ዘግቶታል፡-
የአያቶቻችን ቤት፥ ይሁን ባዶ፣ ይሁን ኦና
በኛ ቁመት፣ በኛ መጠን አልተቀለሰምና፡፡ (ግጥሙን በቃሌ ስለወጣሁት ቃላት ልገድፍ እችላለሁ!)

ከአሁን በፊት የነበረው ትውልድአሲምባ ተራራላይ ያስወጣው ድንጋይና ሳሩ አይመስለኝም፡፡ ወጣት ግምባር ላይ ጥይት የሚያሰድድ፣ የሴት ልጅን ጡት የሚያስቆርጥ፣ ከአንድ ማሕፀን የወጡ ሁለት ወንድማማቾችን ጎራ አስለይቶ የሚያታኩስ አስተሳሰባቸው ነው ወደ አሲምባ ተራራ ላይ ያስወጣቸው፡፡ ትውልድ› ዘመኑ ያፈራውን አስተሳሰብ አላምጦ ለአገሬ የሚበጃት ይህኛው ሕሳቤ ነው የሚል ስሌት ላይ ጽኑ እምነት ጨምሮ ውድ የሆነውን ሕይወቱን ያለምንም ፍርሐት ከፍሏል፡፡ ከፋም ለማም ትውልድ› ይበጃል ያለውን አድርጓል፡፡ አሁን የ‹ያ ትውልድ› ክሽፈት ታሪክ መዝገብ ወይም ትውልዱ አብሰልስሎ አገሪቱ ያስመለሳትን ሐሳብ የምንወቅጥበት ጊዜ ላይ አይደለንም፡፡ ኢሕአፓ፣መኢሶን፣ ሰደድን እያጣቀሱ፤ ፋኖ ተሰማራን እየፎከሩ ሕዝቡ ከተጨበጠበት የፍርሐት ቆፈን ለማላቀቅ መሞከር ዘመንን ያለማገናዘብ በጥልቅ ያለማሰብ ችግር ነው፡፡ ገዢው ፓርቲን የሚሞግት የሚያሳጣ ፓሊሲ፣ ተቋም፣ መዋቅር እና የፖለቲካ ርዕዮት ዓለሙ ላይ ከመመራመር ይልቅ እገሌ ደርግ ነበር፣ ኢሕአዴግ ጣኦት ነው፣ ሰውዬው ኤርትራዊ ነው፣ አራማጅ ነኝ፣ ሕዝብ ፈሪ ነው፣ መብራት ተቆረጠ፣ መብራት ተቀጠለ ሐሳቦች እኛን አያነቁም፡፡ ሕዝቡ ከተከናነበው የፍርሐት ጃኖም አያላቅቅም፡፡ ዛሬ እንደ በፊቱ ኧረ ጎራውን ብቻ ፎክሮ፣ ቀረርቶ አቅራርቶ፣ እንደው በደፈናው በሽላላ የምትነቃ ኢትዮጵያ አይደለም ያለችው፡፡ ይህን መሳይ ችግር በብዛት በጋዜጣ ጸሐፊዎቻችን የሚስተዋል ነው፡፡ ይሄን ዘመን ያገናዘበ የዚህን ትውልድ ጥያቄ መመለስ የሚችል አስተሳሰብ ያነገበ አገርን ወደፊት ሊያራምድ የሚችል ጽሑፍ ብናገኝ ነው የራሳችንን አሲምባ መፍጠር የምንችለው፡፡ እንደው በደፈናው ኢሕአዴግ ክፉ ነውና ደረታችሁን አቀብሉ ሐሳብ አሁን ያለውን አምባገነናዊ ስርዓት ያጸና እንደሆነ እንጂ ለአገር አይበጅም፡፡ 1997 .. ባልተመረመረ ፖለቲካ ደረታችንን አቀብለን የከፈልነው ዋጋ የሚዘነጋም አይደለም፡፡

መድኀኒቱን ስጡን
ቃልን መርጠን ከየቤቱ
ለመናገር መጎምዥቱ
ለእኛስ ነው ወይ መዳኃኒቱ?”

ችግራችንን በተለያዩ ተረቶችና ምሳሌዎች መዘርዘር የአዋቂነት ልኬት የመሆን አዝማሚያ ይስተዋላል፡፡ ፔዳል፣ ብስክሌት፣መዶሻ፣ ምስማር፣ድስትና ክዳን፣ የግሪክ አፈ ታሪኮች፣ የአበው ተረቶችን እያጣቀሱ በሽታችንን ማብራራት አሳቢነት (Thinker) አይደለም፡፡ ሲታከክልን ዝም ብለን እንጂ ቁስሉን አዝለን ከምንዞረው ከኛ በላይ በሽታውን የሚያውቅ የለም፡፡ አሁን ያለው ስርዓት ለአገራችን ፈፅሞ እንደማይበጃ ከኑሮ በላይ የሚያስረዳ ነገር የለም፡፡

ደራሲዎች፣ ገጣሚዎች፣ ጋዜጠኞች እና ሌሎች ጸሐፊዎች በመንደር ከሚወራው በተሻለ ለአደባባይ የሚበቃ ሐሳብ አለኝ እና ወደ ጋዜጣ መጥቻለሁ ስትሉ የበሽታውን መድኀኒት ጠቁሙን፤ አብዮታዊ ዲሞክራሲ የሚለው መርሕ አይበጀንም ስትሉ የሚበጀንን ርዕዮተ ዓለም አሳዩን፡፡ ይሄ መንግስት መውረድ አለበት ስትሉ፣ እንዴት መውረድ እንዳለበት መንገዱን ስጡን፡፡ በደፈናው ስለተበደልን ብቻ ሕይወታችሁን ማግዱ አትበሉን፡፡ እንደው ብድግ ብሎ ሕዝብ ቄጤማ ነው የሚል ፈሊጥ አንስቶ የቄጤማን ልፍስፍሰነት እየተነተኑ ሕዝቡ ፈሪ እንደሆነ መተንተን ተራማጅነት አይደለም፡፡ ይሄ ፈፅሞ ለአገርም አይረዳም፡፡

ማቅ ልበስ፤ ውደቅ በንስሐ
እንደ ቶን ፍም እሳት ይፋጃል ይልሳል
መንገዱ ከሲኦል ያደርሳል፤
የደበቅከው እውነት ሳይጮህ በበረሃ
ማቅ ልበስ ውደቅ በንስሐ
(አቤል ሙሉጌታ)

ዛሬ ይርጋለም ዱባለንና ሰለሞን ተካለኝን እየኮነኑ በደላቸውን ሊያጥቡ እየሞከሩ ነው፤ ዛሬ የራሳቸውን ጉድፍ ሳይነቅሉ ሌላው ንስሐ እንዲገባ እየሞገቱ ነው፡፡ በሁለት በኩል ተስላችሁ፣ እምነት አጉድላችሁ፣ ለስጋችሁ አድልታችሁ፣ ንዋይ አሳውሯችሁ፣ ዝና ባርቆባችሁ፣ እውቀት ስንክሎባችሁ፣ ሌላም ሌላም ምክንያት ኖሯችሁ በደል ስለፈፀማችሁ ወግዱ ሂዱ ለማለት ተፈልጎ አይደለም፡፡ የአፍ ፈሊጣችሁ በእምነት ከሆነ እንሞግታችሀለን፤ በስህትት ከሆነም ይቅር እንላችኋለን፡፡ ሁለት አሥርትመታት በስቃይ ለመሩን መሪ ለአንድ ቀንም ቢሆን ከልብ አዝነናል፤ ለይቅርታ ፍፁም ቅርብ መሆናችንን ያመላክታል፡፡ እኔ ስለአቶ መለስ ዜናዊ አንባቢነት ነው የጻፍኩት፣ የኔ ተቋም ይቅርታ ጠይቋል፣ የሰው እንጂ የራሴን ግጥም አላነበብኩም ዓይነት ሰንካላ ሰበብ ክደቱን አያክምም፡፡ ሁሉም ለፈፀመው በደል የራሱ የሆነ ምክንያት አለው፡፡ በቀጣይነት አምነናችሁ ብርሃናችሁን እንድንቀበል፣ ያለጥርጣሬ ፍሬያችሁን እንድናጣጥም አጥጋቢ የሆነ ማብራሪያ አሊያም ከልብ የሆነ ይቅርታ ይገባናል፡፡ ይሄ በደላችሁን ያጥባል፤ነጥቆ እንዳልነጠቀ ማባበልሕሊናችሁን አይበጀውም፡፡

ከአፍ ፈሊጥ በዘለለ ጥረት አድርጋ በነበረችው ዳኛ ብርቱካን ሚደቅሳ በአሜሪካ ለሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ባደረገችው ንግግር ሐሳቤን እቋጫለሁ፡፡

“…
የዚህ ፕሮግራም ዋና ዓላማ እንደሚመስለኝ ኢትዮጵያን ማወደስ ነው፡፡ እያሰብኩት ነበረእውን ኢትዮጵያ የምትወደስ ናት ወይ እያልኩኝይሄን በሐቀኝነት ስንመልስ ብዙ ቅር የሚያሰኙ ነገሮች አሉ፡፡ ከቅሬታም በላይ የሆኑ፤ ምክንያቱም ኢትዮጵያ የነጻነት አገር አይደለችም፡፡ ኢትዮጵያ የፍትሕ አገር አይደለችም፡፡ ኢትዮጵያ ዛሬም ዜጎቿ በድህነት የሚኖሩባት በሐፈረት የሚያቀረቅሩባት፣ ብዙ ዜጎቸ የሚሰደዱባት ነች፡፡ ስለዚህ እናወድሳት ውይ ብለን እንጠይቅ፡፡አይ መወደስማ አለባት የሚል አቅም ነው ያለኝ፡፡ ስናወድሳት ግን ምን አስበን ነው? ኢትዮጵያ ታላቅ አገር ነበረች፤ ይህን እኔ አይደለሁም የምናገረው ታሪክ ነው የሚመሰክረው መልዕክቴ ይሄው ነው:: ኢትዮጵያ ልትወደስ የሚገባት ታላቅ አገር ነች! ታለቅነትን ለማየት ግን ሁሌም በአንድነት እንቁምአንድነታችን ሁላችንንም የሚያቅፍሁላችንንም የሚያሰባስብና የኢትዮጵያ የጋራ መኖሪያነት በሚያውቁት ይሁን፡፡
(
ብርቱካን ሚደቅሳ)

አሜን ይሁን! … “አንድነታችን ሁላችንንም የሚያቅፍ፤ሁላችንንም የሚያሰባስብና የኢትዮጵያ የጋራ መኖሪያነት በሚያውቁት ይሁን”… ይሁን!

No comments:

Post a Comment