Tuesday, October 16, 2012

አንድ ለመንገድ፡- ከካምፖሎጆው ፍጥጫ ማግስት



በታምራት ተስፋዬ

እኛ ኢትዮጵያውያን ጥሎብን በብዕር ለመግለጽ ከምንችለውም በላይ በእግር ኳስ አቅላችንን እስከምንስት ድረስ ልክፍት ውስጥ ገብተን በራሳችን የሚያረካን ጠፍቶ የሌሎችን ማድነቅ ከጀመርን ይኸው ሦስት አሥርት ዓመታቶች ተቆጠሩ፡፡ ይበል ነው፤ ይኸው ጊዜ ተለውጦ ለረዥም ጊዜ አልጎመራ ያለው ፍሬ ሊበስል ከጫፍ ላይ ደርሷል፡፡ ኢትዮጵያ ሱዳንን አሸንፋ ለአፍሪካ ዋንጫ አልፋለች፡፡ ታዲያ ለምን እግረመንገዳችንን የኢትዮ-ሱዳን ጂኦ ፖለቲካዊ ግንኙነት ላለፉት 20 ዓመታቶች ምን ዓይነት ገጽታ እነደነበረው በትንሹ ለመዳሰስ አንሞክርም፡፡

ደርግና ሱዳን

የደርግ መንግስት ከሱዳን ጋር ኦፊሻላዊ ግጭት ባይኖርበትም እባብ ለእባብ እንደሚባለው የሁለቱም መንግስታዊ አስተዳደሮች እርስ በእርስ ሲጠባበቁ እነደነበር የታሪክ ድርሳናት ያትታሉ፡፡ ሱዳን ሕወሓትንና ሻዕቢያን በክልሏ ላይ እንደልብ እንዲፈነጩና የራሳቸውን ቢሮ እንዲከፍቱ ስታደራጅ ደርግ የመልስ ምት በሚመስል መልኩ የደቡብ ሱዳን ነጻ አውጪዎችን በማስታጠቅና በፋይናንስ በመደጎም የበቀል ዱላውን ይሰነዝር ነበር፡፡ በዚህ ወቅት የሱዳን ሕዝብ በሁለት ጎን ተጠቃሚ ነበር፡፡ ሕወሓት በእርሻና በትራንስፖርት ዘርፍ ተሰማርቶ ሀገራቸውን ሲረዳ በሌላ አቅጣጫ ደርግ ነጻነት ለሚፈልጉ ሕዝቦች ያለውን በመስጠት ሕዝቡ በሁለቱም ወገን ተጠቃሚ እንዲሆን አድርጎ ነበር፡፡

የገደለው ባልሽ…

ኢሕአዴግ ስልጣን በያዘ በአንደኛ ዓመቱ ወርሃ ሰኔ ላይ ዱብ ዕዳ ወረደ፡፡ ሀገራችንን ለመጎብኘት ወደ አዲስ አበባ የመጡት የግብጹ ፕሬዝዳንት ቦሌ አየር ማረፊያ ሲደርሱ አቀባበሉ በፖሊስ ኦኬስትራ ይሆናል ተብሎ ሲጠበቅ ነገሮች ተገላብጠው በክላሽ እና በቦንብ ሆነ፡፡ ስድስት የሚሆኑ የአረብ ሀገር ተወላጆች ሙባረክን በክላሽ እንኳን ደህና መጣህ ቢሉትም የግድያው ዕቅድ ሳይሳካ ቀርቶ አራቱ አዲስ አበባ ላይ ሲመቱ አንዱ ሸሽቶ ሱዳን ገባ፡፡ ግጭቱ ኢትዮጵያና ሱዳን ላይ በመሆን ክርክሩ አሳልፈሽ ስጪኝ አልሰጥም ሆነ በመሰረቱ በወቅቱ ሙባረክ ከኢትዮጵያ ይልቅ ለሱዳን ቅርብ ነበሩ፡፡ እንደውም በአንድ ወቅት በአንድ እንትን የሚባለው ደረጃ ላይ ደርሰው ነበር፡፡ መኖር መልካም ነው ብዙ ያሳያል፤ ይኸው በክላሽና በቦንብ ያልተፈቱት ሙባረክ በHeዝብ ጩኸት ተረቱ፡፡ እኛም በርእስነት የተጠቀምኩትን ተረት ሳንተርት ኢትዮጵያና ሱዳን ሰላም አወረዱ፡፡

የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት

ሱዳን በዚህ ወቅት የጆከርነት ሚናዋን ስትጫወት ሰነበተች፤ ከወደብ አከራይነት እስከ መሳሪያ አስተላላፊነት በመሳተፍ በአንድ ድንጋይ እንደሚባለው ከሁለቱም ሀገር ጋር በመሰለፍ ኢኮኖሚዋን አፈረጠመች፡፡ ጦርነቱ የሁለቱንም ሀገሮች ኢኮኖሚ ያሽመደመደ ሲሆን በተቃራኒው የሱዳን ሕዝብ በጦርነቱ ተጠቃሚ ለመሆን በቃ፡፡

የሚሊኒየም ዋዜማ

በበርበሬ ገበያ ላይ በታየው ቅጥ ያጣ የዋጋ ጭማሪ ‹‹አልጫው ሚሊኒየም›› የተባለው ሀገራዊ በዓል የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን የሱዳንም በዓል እስከሚመስል ድረስ መዲናችን በሱዳን ዘፈን ‹‹እልል በቅምጤ›› ስትል አመሸች፡፡ በዕለቱ ነፍሳቸውን ይማረውና የቀድሞው ጠ/ሚኒስትራችን ከአልበሽር እና ከባለቤታቸው ጋር በሱዳን ሙዚቃ ሲደንሱ አመሹ፡፡ በወቅቱም ጥላሁን ገሠሠ እያለ እንዴት በሱዳንኛ የሚሉ ድምጾች ከየአካባቢው መሰማት ጀመሩ፡፡ መቼም ይህቺ ነገር ለተራ ፖለቲከኛም አትጠፋም፤ ይህ ጸሐፊ ሆን ተብሎ የተደረገ ነው ብሎ ያምናል፡፡ በወቅቱ መለስ ግንኙነታችን በሙዚቃችሁ ከመጨፈርም በላይ ጥርጣሬ የሌለበት መልካም ጉርብትና እንዲኖረን እንፈልጋለን የሚል መልዕክት ለአልበሽር ለማስተላለፍ አስበው ይመስለኛል፡፡ አልበሽርም መልዕክቱን በመረዳት በሚመስል መልኩ ግንኙነቱን ማጠንከር ላይ መሥራት ጀመሩ፡፡

ጥላሁን ገሠሠና አልበሽር

ሄግ የሚገኘው ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት ዳርፉር ላይ በደረሰው ቀውስና በተያያዥ ጉዳዮች አልበሽር ላይ የበረራ እገዳና በማንኛውም ጊዜ ተይዘው ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ዋራንት ቆረጠባቸው፤ ምድር ቀውጢ ሆነች፡፡ ሰውየው በነጻነትና በመታሰር መሀል ላይ ወደቁ፡፡ እንቅስቃሴያቸው ሁላ ድጋፍ ለማገኘት ደፋ ቀና ሆነ፡፡ በዚህ ወቅት ኢትዮጵያ ታላቁን የሙዚቃ ሰው አጣች፡፡ እንደተለመደውም አጀንዳው በኢትዮጵያ ወደ አንድ አቅጣጫ ዞረ፤ ጨዋታው ሁላ ጥላሁን ጥላሁን ሆነ፤ በዚህ ወቅት አልበሽር ወደ አዲስ አበባ ድምጻቸውን አጥፍተው ከተፍ አሉ፡፡ የዋሆች ለቀብር ይሆን ብለው ያስባሉ፤ አልበሽር ግን ዋራንቱ ምንም ተጽእኖ እንዳላሳደረባቸው እና ፉርሽ እነደሆነ በኢትዮጵያ ጉብኝት አስመሰከሩ፡፡ በወቅቱ ሚዲያው ሁላ ከአልበሽር ይልቅ ጆሮዋቸውን ለሙዚቃ ተንታኙ ሠርጸ ፍሬስብሓት አዋሱት፡፡ ጨዋታው ሁላ ሞናሊዛዬ ነሽ ሆነ፤ አልበሽርም ድምፃቸውን እንዳጠፉ በአረብኛ ሞናሊዛዬ ነሽን እያንጎራጎሩ ጉብኝታቸውን ጨርሰው ወደ ሀገራቸው ተመለሱ፡፡ ዓለም አቀፉ ሚድያም የሄግ ሕግ አልተከበረም በማለት ለአንድ ሰሞን ተንጫጫ፤ ኢትዮጵያም (አልበሽርን ያለምንም ኮሽታ በማስተናገድ) ግንኙነቷ ለችግር ጌዜም እነደሆነ ለፕሬዚደንቱ ስታሳይ ጥላሁን በበኩሉ በሕይወት እያለ ሚሊኒየም አዳራሽ ባለመገኘት ለሱዳን ያደረገውን ውለታ በመሞቱ ደግሞ ሚዲያውን ይዞ አጀንዳውን በማዞር ውለታውን ዳግም አረጋገጠላቸው፡፡ ነፍስ ይማር ሌላ ምን ይባላል፡፡

ኢትዮጵያ እነደ ጆከር

በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ለሁለት ለተከፈሉት ሱዳኖች እንደ ጆከር በመሆን  በሁለቱም መሀል ላይ ድልደይ በመሆን እያገለገለች ትገኛለች፡፡ በዚህ ወቅት ለሁለቱም ሱዳኖች ከኢትዮጵያ ውጭ የጋራ ፍላጎታቸውን የሚስከብር እንደሌለ የተረዱ ይመስላል፡፡ እናም ኢትዮጵያ በዚህ ቀውጢ ሰዓት ከሱዳን ሕዝብ ጋር በመቆም አለኝታነቷን አረጋግጣለች፡፡

ያልተነካው አጀንዳ

ነፍሳቸውን ይማርና የደቡብ ሱዳን የመጀመሪያው ፕሬዝዳንት የነበሩት ጆን ጋራንግ የደቡብ ሱዳንን ወሰን (border) እስከ ባሮ መነሻ ድረስ መሆኑን በለሆሳስ ይናገሩ ነበር፡፡ ይህ መቼም ለኢትዮጵያ አስደንጋጭ ነው፤ በእርግጥም ደቡብ ሱዳን በዚህ ወቅት ድክ ድክ እያለች ስለሆነ ይህን ጥያቄ ማንሳት ባትችልም አጀንዳው ግን ጠረጴዛ ላይ እንዳለና ከጊዜዎች በኋላ መነሳቱ እነደማይቀር ግልጽ ነው፡፡ በእውነቱ የጋምቤላ ኢትዮጵያዊነት ላይ ምንም ድርድር አያስፈልግም፤ ነገር ግን ነገሮች ጥሩ ላይሆኑ ይችላሉ፡፡ በአንድ ወቅት ለሥራ ጋምቤላ በሄድኩበት ወቅት ብዙውን ቁጥር የሚወክለው የኑዌር ኽዝብ ከስልጣኑ እራሱን አግሎ ባሮን  ይዞ እየተመመ መሆኑን ለመገንዘብ ችያለሁ፡፡ የቤት ስራውን በጊዜ መጀመር መልካም ነው፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት በኅብረ-ትርኢት ሙዚቃን ከመልቀቅና የቁንጅናን አክሊል ለክልሉ ከመስጠትም በላይ ጋምቤላ ላይ ትልቅ ሥራ መሰራት ያለበት ይመስለኛል፡፡ ሕዝቡን የስልጣን ተጋሪ ማድረግና መሠረተ ልማቶችን ማስፋፋት ችግሩን በዘላቂነት ይቀርፈዋል ተብሎ ታሰባል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ነገሮች ከሆኑ በኋላ መቱ እና ቴፒ ላይ ቆሞ ዘራፍ ከማለት ውጪ አማራጮች ላይኖሩ ይችላሉ፡፡

ለትዝታ እና ለማንቂያ ያክል ይህንን ካልኳችሁ አሁን ደግሞ ወዳቋረጥኳችሁ የድል ማግስት ጭፈራ ልመልሳችሁ ‹‹…የእርግብ አሞራ……የእርግብ……የእርግብ አሞራ…›› (የእርግብ አሞራ  ማለት ግን ምን ማለት ይሆን?)
----
ጸሐፊውን ለማግኘት በኢሜይል አድራሻቸው tamrattesfaye39@yahoo.com ይጻፉላቸው፡፡

2 comments:

  1. Minew selteshetaw merate zime alkisa . . . Aresute yametamane maret . . . Ega mechame anerasawim...

    ReplyDelete