Tuesday, October 23, 2012

የኢሕአዴግ ስርዓት፤ ፍጹም የበላይነት ወይስ የሕግ የበላይነት?



ይህ ጽሑፍ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት ባካሄደው ሕዝባዊ ስብሰባ ላይ ካቀረብኩት ንግግር የተወሰደ ነው፡፡ ከሁሉ አስቀድሞ በስብሰባው ላይ ተገኝቼ ንግግር እንዳደርግ ዕድል ለሰጠኝ ፓርቲ ምስጋናዬን አቀርባለሁ፡፡

በቃል የቀረበውን በጽሑፍ ለማሰናዳት የፈለግኩበት ምክንያት በመጀመሪያ በጽሑፍ ሲቀርብ ሰፋ ላለ አንባቢ ተዳራሽ ስለሚሆንና በሁለተኛ ደረጃ ይህን መጽሔት [አዲስጉዳይ] ጨምሮ በሌሎች የሕትመት ውጤቶች ላይ ሲስተናገድ ትክክለኛው የሐሳብ ምስል ስላልቀረበ ምናልባት በዚህ ጽሑፍ የተሟላ መልዕክቱን ማስተላለፍ ይቻላል በሚል እምነት ነው፡፡…

ታሪክና ፍልስፍና
የሰው ልጅ በብዙ መልኩ ከታሪክ ሊማር ይገባዋል፡፡ ሆም ግን የረዥም ጊዜ የታሪክ ሒደት የሚያሳየው ሰው ከታሪክ መማር እንደሚያዳግተው ነው፡፡ ይህንንም ትዝብት ታላቁ የጀርመን የ19ኛው ክፍለዘመን ፈላስፋ ሄግል ‹‹ታሪክ የሚያስተምረን ነገር ቢኖር የሰው ልጅ ከታሪክ አለመማሩን ነው›› ሲል ገልጾታል፡፡

ኢሕአዴግም ሆነ የተቃዋሚ ፓርቲዎች በተለያዩ ጥያቄዎች ላይ ኢ-ታሪካዊ አቀራረብ እንዳላቸው ለማየት አያዳግትም፡፡ ኢሕአዴግን በተመለከተ የድርጅቱ ምሁራን ታሪክን የሚጠቅሱት አንድም ካለፈው የተሻሉ መሆናቸውን ለማስረዳት አሊያም በፍፁም ከዚህ በፊት ያልነበረ አዲስ ነገር የፈጠሩ አድርገው ለማቅረብ ነው፡፡

የዚህ ዓይነት የታሪክ ዕይታ ችግሩ አንደኛ ‹‹የታሪክን ቀጣይነትና ተከታታይነት›› (continuity and discontinuity) በመሠረቱ የሚድንና ላለንበት ወቅት የታሪክ አሻራ ዕውቅና የማይሰጥ ነው፡፡ በመሆኑም ኢሕአዴግ አብዛኛውን ጊዜ ትኩረት የሚሰጥ የታሪክ ቀጣይ አለመሆን ላይ ነው፡፡

በሁለተኛ ደረጃ ለፖለቲካችን ይበጀናል ከሚሉት የታሪክ ዕሳቤ ውጭ በትረካቸው ውስጥ ስለማያካትቱና አሁን ባለንበት ዘመን በተገኘ መስፈርት ታሪክን ከአውድ ውጪ እያዩ ስለሚፈርጁ የተዛባ ታሪክ አቀራረብ ይይዛሉ፡፡

ከአንዳንድ ተቃዋሚዎችም ወገን ቢሆን አልፎ አልፎ የታሪክ መዛባት ይስተዋላል፡፡ እንደማሳያ ለማንሳት የደርግን ስርዓት በሚያነሱበት ጊዜ የሚሰጡት አስተያየት አንድም እኩይ ድርጊቱን ያድበሰበሰ አሊያም ለስርዓቱ ይቅርባይነት ያደላ (Apologetic) ሆኖ እናገኘዋለን፡፡

ፍልስፍናም አንድን ጉዳይ ለማብራራትና ለመረዳት ብዙ ጊዜ ቀጥተኛ መንገድ ይዛ አትጓዝም፡፡ ግልገል ያየች ንስር አደኗ ላይ ተምዘግዝጋ ከማረፏ በፊት ዙሪያውን እንደምታንዣብብ ሁሉ ፍልስፍናም የጉዳዩን ፍሬ ነገር የምታስረዳው ዳር ዳሩን ከዞረች በኋላ ነው፡፡ እኛም በቀጥታ ወደ ኢትዮጵያ ፖለቲካ ከመግባታችን በፊት ግላዊ ኃላፊነት (Equality of Responsibility)፣ የሕዝብ መልካም ፈቃድ (Individual of consent)፣ እንዲሁም የሕሊና ነጻነት (Idea Conscious) የሚባሉት የዴሞክራሲያ መርሆዎች በአውሮፓ እንዴት እንደፈለቁ አጠር ባለ መልኩ እመለከታለን፡፡

የክላርክ ታሪካዊ ማህደር
ጊዜው 1647 ዓ.ም. ነው፡፡ የእንግሊዝ አብዮት ንጉሡን ከዙፋን በማውረድ በድል ተጠናቋል፡፡ የአብዮቱ መሪ ተዋንያ የአገሪቱ የፖለቲካ ስርዓት ምን ዓይነት መልክ መያዝ እንዳለበት ለመወሰን ትልቅ ስብሰባ ይዘዋል፡፡ ከተሰብሳቢዎቹ ውስጥም አንደኛ የአብዮቱ ዋ መሪ ሰር ኦሊቨር ክሮምዌል፣ ሁለተኛ የወግ አጥባቂው ፓርቲ መሪ ሚስተር አየርተን፣ ሦስተኛ የሰራዊቱ መሪ ኮሎኔል ሬይንቦ፣ አራተኛ በቃለ ጉባኤ ያዥነት የተመደቡት ሚስተር ክላርክ ተጠቃሾች ናቸው፡፡

ሀ - ግላዊ ኃላፊነት
በስብሰባው ላይ የተነሳው የመጀመሪያው ርዕሰ ጉዳይ በስልጣን ባቤትና በምርጫ ዙሪያ ነበር፡፡ ተሰብሳቢዎቹ ከእንግዲህ ወዲያ ስልጣን የሚገኘው በምርጫ መሆኑን ከተቀበሉና ዕውቅና ከሰጡ በኋላ አከራካሪ ሆኖ ያገኙት ‹‹ለመምረጥ ሕጋዊ መብት ሊያገኝ የሚገባው ዜጋ የትኛው ነው?›› የሚለው ነበር፡፡

ለዚህም የመጀመሪያው ሐሳብ አቅራቢ የወግ አጥባቂው መሪ ሚ/ር አየርተን ነበሩ፡፡ በእርሳቸው አቀራረብ የመምረት መብት ሊሰጠው የሚገባው ዜጋ ንብረት ያካበተ መሆን አለበት፡፡ ለዚህም ምክንያቱ ንብረት የሌለው ሰው ለጉዳዩ ብዙ አትኩሮት ሳይሰጥ አገሪቱን ሊጠቅምና ሊጎዳ የሚችለው ፖለቲከኛም ሳያስበው እንዲሁም በተጨማሪ በቀላሉ እየተደለለ ድምፁን ሊያስረክብ የሚችል በመሆኑ ነው፡፡

በአንጻሩ ኮሎኔል ሬይንቦው ይህን ሐሳብ በመቃወም አስተያየታቸውን እንደሚከተለው አቅርበዋል፡፡ ‹‹ለመምረጥ የንብረት ባለቤትነት እንደመስፈርት መቅረቡ በሰው ል ላይ የመብት ጥሰት መፈፀም ይቆጠራል፡፡›› ካሉ በኋላ ይኸውም አንድ ደሀ እንግሊዛዊ እነቶኔ ከአንድ ሀብታም እንግሊዛዊ እነቶኔ እኩል በሆነ መልኩ ሕይወቱን የመምራትና የመወሰን መብት ስላለው የመምረጥ መብት ተጎናፃፊነቱ መነካት እንደሌለበት አስረድተዋል፡፡

በእንግሊዝኛ የተናገሩትን ብንጠቅሰው ‹‹The poorest he that is in England has a life to live as the richest he›› ነበር ያሉት፡፡

ይሄ ሐሳብ በመሠረቱ የምርጫ ጉዳይ ቢሆንም ይዘቱ ግን ሰፋ ብሎ እያንዳንዱ ዜጋ ሕይወቱን ለመምራት ብቸኛው ወሳኝ እርሱ መሆኑንም የሚያስገነዝብ ነው፡፡ ከዚያም አኳያ ስለ ነጻነት ምንነት በ20ኛው ክ/ዘመን መባቻ ላይ ‹‹what is liberity?›› ወይም ‹‹ነጻነት ምንድን ነው?›› የሚለውን ወሳኝ ድርሳን የጻፈውን ጆን ስትዋርት ሚል (John Stwart Mill) የኮሎኔል ሬይንቦውን ሐሳብ በማጠናከር እንደሚከተለው ያስረዳል፡፡ ‹‹አንድ ሰው በመሠረቱ ያለማንም ጣልቃ ገብነት ሕይወቱን የመምራት መብት አለው፡፡ ይህም ማለት መብቱን በሚተገብርበት ጊዜ የሌላውን ሰው መብት ባልነካና ጉዳት በማያስከትል መልኩ ሊሆን ይገባል፡፡››

በታላቁ ስብሰባ ላይ እየተሳተፉ ያሉት ሰዎች፣ የኮሎኔል ሬይነቦው ሐሳብ ተቀባይነት ካገኘ በኋላ ወደ ሁለተኛው ርዕሰ ጉዳይ ተሸጋገሩ፡፡

ለ - ሕዝባዊ ስምምነት/ የሕዝብ መልካም ፈቃድ (consent)
መንግስት በመሠረቱ ሄዶ ሄዶ በሕዝብ መልካም ፈቃድ ላይ ማረፍ አለበት፡፡ በሌላ አነጋገር ከስዩመ እግዚአብሔርነት ወደ ስዩመ ሕዝብነት መሸጋገር ማለት ነው፡፡ ይህም የዘመናዊነት አንድ መገለጫ ነው፡፡

አሜሪካውያን ከእንግሊዝ በነፍጥ ነጻነታቸውን ከተቀዳጁ በኋላ ባስፋፉት የነጻነት ስልጣን የሚያገኘው ተገዢዎች ከሚሰጡት መልካም ፈቃድ ነው፡፡ (Governments derive their power from the consent of the governed) ማለታቸው ይህንን ያጠናክረዋል፡፡

የእንግሊዝን አብዮት በግንባር ቀደም የመሩት ተዋንያን ባካሄዱት ስብሰባ ላይ የነበረው አስተሳሰብ ማንም ሰው ወደስልጣን የሚመጣው የሕዝብን በጎ ፈቃድ ከተጎናፀፈ ብቻ ነው የሚል ብሒል ነበር፡፡

ይህንን የሕዝብ መልካም ፈቃድ ዕሳቤ በሚመለከት ከስብሰባው ታዳሚዎች አሁንም እንደገና ሁለት ተቃራኒ ሐሳቦች ቀርበው ነበር፡፡ በመጀመሪያ ሚስተር አየርተን ‹‹በመሠረቱ የሕዝብ መልካም ፈቃድና መንግስት እንደ ፅንሰ ሐሳብ አብረው መሄድ የማይችሉ ናቸው›› (Consent and government are not compatible) አሉ፡፡

ይህንን ሐሳባቸውንም ሲያብራሩት በሁሉም ነገር ላይ የሕዝቡ መልካም ፈቃድ የሚጠየቅ ከሆነ ስርዓት አልበኝነትእንደሚሰፍን በመግለጽ ነው፡፡

ኮሎኔል ሬይንቦው በተራቸው ለሚስተር አየርተን ስጋት የሚከተለውን መፍትሔ አቅርበዋል፡፡ በኮሎኔሉ አባባል የሕዝብ መልካም ፈቃድ ሲባል ለሁሉም ጉዳይና ለሚደነገገው ሕግጋት በመላ ሕዝቡ የግድ መልካም ፈቃዱን መስጠት አለበት ማለት አይደለም፡፡ የሕዝብ መለካም ፈቃድ ማለት ለሕግ አውጪዎች የውክልና ፈቃድ በመስጠት መሆን ማለት ነው፡፡ እዚህጋ ልብ ማለት የሚገባን የውክልና መንግስት ፅንሰ ሐሳብ የሚመነጨው ከዚህ ሐሳብ መሆኑን ነው፡፡

የውክልና መንግስትና የተደራጀ ተቃዋሚ በፅንሰ ሐሳብ ደረጃ ሊነጣጠሉ የማይችሉ ናቸው፡፡ በመሆኑም የዴሞክራሲያ መሠረታዊ ዕሳቤ የሐሳቡን አንድነት ማስተጋባት ብቻ ሳይሆን በማኅበረሰቡ ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ አስተያየቶችን እንዲያንሸራሽሩ በመፍቀድና በመጨረሻም በብዙሐን ተቀባይነት ያገኘውን ማጽደቅ ነው፡፡

ዴሞክራሲ ማለት የታይታ ስምምነት (Unanimity) የሚፈጠርበት መስክ አይደለም፡፡ እዚህጋ የሕዝብ እንደራሴዎች ወይም ወኪሎች ወደፓርላማ ድምጹን ሰጥቶ የላካቸው ሕዝብ ወኪል ብቻ ናቸው ወይስ የራሳቸው የአስተሳሰብ ልዕልና ኖሯቸው ለአገር ይበጃል ብለው ባመኑት ነገር ላይ የግል አቋም ይወስዳሉ? የሚሉ ጥያቄዎችን ማንሳት ተገቢ ነው፡፡ እንዲሁም ‹አንድ የፓርላማ አባል አላስፈላጊ ሆኖ ስታገኘው/ሲያገኘው ከፓርቲያቸው መርሕ የሚጻረር አቋም ሊወስዱ ይችላሉ ወይ?› ብሎ መጠየቅም ያስፈልጋል፡፡

በነዚህ ጥያቄዎች ዙሪያ ማለትም ከወከሉት ማኅበረሰብ (Constituency) ወይም ከፓቲ መርሕ ውጪመንቀሳቀስ ይቻላል ብለው ወሳኝ ድርሳናት የጻፉት የ18ኛው ክ/ዘመን የእንግዙ ፈላስፋ ኤድመንድ በርክ (Edmund Burke) እና የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የነበሩት ጆን ኤፍ ኬኔዲ ናቸው፡፡

ኤድመንድ በርክ ‹‹Letter to the sheriff of Bristol›› በሚለው መጣጥፍ ላይ ‹‹እኔን መርጣችሁ የላካችሁን የበሪስቶል ነዋሪዎች ብትሆኑም ባለኝ አዕምሯዊ ብቃት አምናችሁ ከመረጣችሁኝ በኋላ ፓርላማው ውስጥ በሚነሳው ክርክር እናንተ የምትፈልጉትን ብቻ ሳይሆን እኔ በግሌ ለአገር ይበጃል ብዬ የማምንበትን አቋም ከማንፀባረቅ ወደ ኋላ አልልም፡፡›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡

ጆን ኤፍ ኬኔዲ ደግሞ በበኩላቸው ‹‹profiles in courage›› (የጀግንነት አርኣያዎች ብለው አቶ ተሻገር ውቤ በተረጎሙት) መጽሐፋቸው ላይ የአሜሪካንን የ200 ዓመት የምክርቤት ታሪክ አጥንተው በተለያየ ጊዜ ከፓርቲያቸው ወይም ከወካዮቻቸው ፍላጎት ውጪ የአጠቃላይ አገርን ጥቅም በማስቀደም በግል የደረሰባቸውን ጫናና ጉዳት ተቋቁመው የጀግንነት ተግባር ፈፅመዋል ብለው ስለመረጧቸው የም/ቤት አባላት አትተዋል፡፡

ከሁለቱ ሰዎች አስተምህሮ የምንገነዘበው ነገር ቢኖር ተወካዮች አልፎ አልፎም ቢሆን በራሳቸው እምነት ሊጓዙ እንደሚገባ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ፓርላማ ከውክልናው ጋር አብሮ የሚሄድ የውይይት አጀንዳ የማፍለቅ ሚናም አለው፡፡ በፓርላማ የሚነሳው ሐሳብ በተለያዩ ሕዝባዊ አጀንዳ ይሆናል፡፡ ከዚህም የተነሳ ሰዎች የድጋፍና የተቃውሞ አቋም ይይዙበታል፡፡

የሞቀ ውይይት የሌለበት ፓርላማ እንደሞተ ባሕር በውስጡ ምንም ሕይወት አይኖረውም (ሕይወት አልባ ነው)፡፡

ሐ- ግላዊ ሕሊና ወይም የሕሊና ነጻነት
የእንግሊዝ አብዮት በተካሔደበት ወቅት የሃይማኖት ድባብ በጣም ጠንካራ የነበረበት ጊዜ ነበር፡፡ በተለይ አብዮቱን የመሩት ሰር ኦሊቨር ክሮምዌል በእጅጉ መንፈሳዊና የሃይማኖት ሰው ነበሩ፡፡ የተቀሩት የስብሰባው ተሳታፊዎችም ቢሆኑ ለሕሊና ነጻነት ከፍተኛ ስፍራ የሚሰጡ ነበሩ፡፡

ቃሉ እንደሚያመለከተው ‹‹የሕሊና ነጻነት›› ማለት የፈለግነውን ማመን፣ የፈለግነውን መርሕ መከተል፣ የፈለግነውን ሃይማኖት መቀበልና በፈለግነው ወግ የመተዳደር መብትን የሚያጎናፅፍ ነው፡፡

እዚህ ላይ ማስታወስ የሚገባን ከብዙ ዓመታት የሃይማኖት ጦርነት በኋላ አውሮፓውያን ወደሰላምና መቻቻል እንዲመጡ ያደረገው ይኸው የሕሊና ነጻነት (Liberty of conscious) ዕሳቤ ተቀባይነት በማግኘቱ መሆኑን ነው፡፡

ከዚህ ዕሳቤ በመነሳትም ኦሊቨር ክሮምዌል ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብትን አስመልክቶ ‹‹እግዚአብሔር በማን አንደበት አንደሚናገር ስለማይታወቅ ለሁሉም ዜጋ የመናገር መብት ሊሰጥ ይገባል›› የሚል አስተያየት አቀረቡ፡፡ ነገር ግን አየርተን ይህን ሐሳብ በጥርጣሬ በመመልከት ‹‹ማንም እየተነሳ እግዚአብሔር አናገረኝ እያለ የሚሆንና የማይሆን ወግ ቢያቀርብ ምን ልናደርግ ነው?›› ሲሉ ሞገቱ፡፡

ለዚህም ጥያቄ ኦሊቨር ክሮምዌል ‹‹መቼም ሁላችንም እንደምናውቀው እግዚአብሔር የምክንያታዊነት አባት ነው፡፡ ስለዚህም የማይበጅና ኢ-ሞራላዊ መልዕክት በማንም አንደበት አያስተላልፍም፡፡ አንድ ሰው እግዚአብሔር ገልጾልኛል ወይም አናግሮኛል ብሎ ሲነሳ የነገሩን ጭብጥ መርምረን በእርግጥም እግዚአብሔር እንዳናገረው እና እንዳላናገረው ማወቅ ይቻላል፡፡ ይህንንም ማድረግ የሚቻለው ለሁሉም ሰው መብት ሰጥቶ ሐሳቡን በነጻነት የመግለጽ መብትን በማክበር ነው የሚል ምላሽ ሰጡ፡፡

ስለዚህ ከዚህ የምንረዳው የመናገር ነጻነት ዕሳቤ መሠረት ያገኘው ‹‹እግዚአብሔር በማንም አንደበት ሊናገር ይችላል›› ከሚል ሃይማኖታዊ አመለካከት መሆኑን ነው፡፡

የኢሕአዴግን የፖለቲካ ስርዓት በጥቂቱ
የኢሕአዴግ የፖለቲካ ስርዓት በጥቂቱም ቢሆን ለመተንፈሻ ስንነሳ አልክዛንደር ኸርዝን የተባለ የ19ኛ ው ክ/ዘመን ዕውቅ የራሺያ የስነጽሑፍ ሰው በአንድ ወቅት የሰነዘረውን ንፅፅሮሻዊ ንግግር እንደመንደርደሪያ እንውሰድ፤ እንደ ኸርዝን አቀራረብ፣ ‹‹አንድ እንግሊዛዊ ወይም አሜሪካዊ ‹እኔ እንግሊዛዊ ነኝ› ወይም ‹እኔ አሜሪካዊ ነኝ› ብሎ ሲል፣ አንድምታው ዜግነቱን ብቻ ሳይሆን ነጻ ሰው መሆኑንም እየነገረን ነው፡፡ በአንጻሩ አንድ የጀርመን ተወላጅ ‹እኔ ጀርመናዊ ነኝ› ሲል ‹እኔ በግሌ ነጻ ሰው አይደለሁም፡፡ የአገሬ ንጉሥ ግን ታላቅና ከሌሎችነገሥታት የሚበልጡ ናቸው› ማለቱ ነው፡፡››

ሰሞኑን ‹‹ታላቁ መሪ›› እየተባለ የሚቀርበውን ስሰማ አሌክዛንደርን ኸርዝን ከመቶ ዓመታት በፊ የተናገረውን እንዳስታውስ ያደርገኛል፡፡

ወደስርዓቱ ትንተና ስንገባ ካለፉት ሁለት ስርዓቶች ስያሜዎች አኳያ በአሁኑ ስርዓት ላይ መሠረታዊ ጥያቄ እናነሳለን፡፡ እነደ ፖለቲካ ፈላስፋዎች አስተምህሮ የፖለቲካ ስርዓት ስያሜዎች በየራሳቸው መፍትሔዎቻቸውን ይጠቁማሉ፡፡ ለምሳሌ ‹‹ፍፁማዊ የዘውድ አገዛዝ›› ስንል መፍትሔው መንግስታዊ የዘውድ አገዛዝ ይሆናል፡፡ ‹‹ወታደራዊ አምባገነንነት›› ስንል ቃሉ ራሱ እንደመፍትሔ ሕገመንግስታዊ ስርዓትን ይጠቁማል፡፡ ወደኢሕአዴግ ስንመጣ ‹‹አብዮታዊ ዴሞክራሲ›› የሚለው ስያሜ እንደመፍትሔ ምን ያስቀምጥልናል?

የኢሕአደግ ጉዳይ ከፖለቲካ አኳያ ውስብስብ የሚያደርገው ስርዓቱ የፖለቲካ ሕይወቱን የጀመረው ሕገመንግስት አዘጋጅቶ በማቅረብ ነው፡፡ በመሆኑም ኢሕአዴግ ከሕገመንግስቱ ጋር ያለው ግንኙነት ምን ይመስላል ብሎ መፈተሸ ተገቢ ይሆናል፡፡ ከዚህም በመነሳት የኢሕአዴግን ስርዓት ከሕገመንግስቱ አኳያ ስንፈትሸው ሙሉ በሙሉ ሕገ መንግስቱን ጥሎ አውሮፓውያን ቄሳራዊ (Ceaserism) እንደሚሉት ፈላጭ ቆራጭ ስርዓት ሙሉ በሙሉ አልመሠረተም፡፡ ከዚህ ይልቅ የኢሕአዴግ አካሔድ ሕገ መንግስቱን በከፊል እየሻረ ሲያሻው ደግሞ እያከበረ የሚንቀሳቀስ ስልጣን በጥቂት ሰዎች እጅ ያከማቸና እንዲሁም መሪዎች የሕግ ማዕቀፍ ሳይጣልባቸው የፈለጉትን የሚያደርጉበት ስርዓት (Authourianism) ነው፡፡

የኢሕአዴግ ፍፁማዊ የበላይነት በከፊል የሚመነጨው ስለ ‹‹ፖለቲካል›› ፅንሰ ሐሳብ ካለው አመለካከት ነው፡፡ ለመሆኑ ለኢሕአዴግ ‹‹ፖለቲካል›› ማለት ምን ማለት ነው? በሌላ በኩል ‹‹ፖለቲካል›› የሚለው ፅንሰ ሐሳብስ በድርጅቱ በኩል እንዴት ነው የሚገለፀው ብለን ስንነሳ እነርሱ በጽሑፍ ላይ ያሰፈሩት ሐሳብ ባይኖርም በተግባር እንደታዘብነው ለኢሕአዴግ ፖለቲካል ማት ወዳጅና ጠላት የሚለይበት መስክ ነው፡፡

ይኸው ፖለቲካን የወዳጅና የጠላት መለያ አድርጎ የመጠቀሙ አካሔድ በ20ኛው ክ/ዘመን አጋማሽ የጀርመን ቀኝ ክንፍ አቀንቃኝና የሕገ መንግስት ምሁር የነበረው ካርል ሽሚት ቀርቦ ነበር፡፡

ወዳጅና ጠላት እየለዩ መንቀሳቀስ የሚለው ብሒል ለዴሞክራሲና አብት ለሚመጣው ብዝሐነት በእጅጉ ተፃራሪ ነው፡፡ ይኸውም የሚሆንበት ምክንያት ወዳጅ ሲባል የማቅረብ፣ ጠላት ሲባል የመደምሰስ አካሔድን እንጂ በውይይትና ሰጥቶ በመቀበል መርሕ ላይ የተመሠረተ ባለመሆኑ ነው፡፡ ከዚህም የተነሳ ለኢሕአዴግ ፖለቲካ የሁለት አፅናፍ ተፋላሚዎች መድረክ ስለሚሆን ዕርቅና ድርድር ለይስሙላ ቢቀርቡም ኢሕአዴግ ከደደቢት እስከ አዲስ አበባ የገጠማቸውን ኃይሎች አንድም አካቶ የራሱ አድርጓል አሊያም ደምስሷል፡፡ በሌላ አነጋገር የፓርቲው ታሪክ፣ ከተላያዩ ተቀናቃኞቹ ጋር የገጠመውን ችግሮች በዴሞክራቲክ ውይይት ለዘለቄታው የፈታ ስለመሆኑ አያሳይም፡፡

ኢሕአዴግ ስልጣን በጥቂት ሰዎች እጅ ሲከማችና መሪዎች የሕግ ማዕቀፍ ሳይጣልባቸው የፈለጉትን የሚያደርጉበት ስርዓት ነው ስንል የሐሳብ የበላይነት እንዲኖረው የሚያደርገውን እንቅስቃሰና ስለሕግ የበላይነት መጥቀስ አስፈላጊ ነው፡፡

የሐሳብ የበላይነት
ማንኛውም መንግስት (ፓርቲ) የሐሳብ የበላይነት እንዲኖረው ይጥራል፡፡ ኢሕአዴግም የሐሳብ የበላይነቱን ለማረጋገጥና ለመጎናፀፍ መከጀሉ የሚያስተቸው አይደለም፡፡ ጥያቄ የሚያስነሳበትና ትችት የሚጋብዝበት ማግኘት አለብኝ ብሎ የሚያስበውን የሐሳብ የበላይነት ለመቀዳጀት የተሠማራበት መንገድ ነው፡፡ ከዚህ አኳያ ሁለት ነገሮችን ማንሳት እንፈልጋለን፡፡ አንደኛ ኢሕአዴግ የመገናኛ ብዙሐን ሙሉ ለሙሉ በመቆጣጠር ለራሱ ፍፁማዊ ጥቅም ለማግኘት ይገለገልበታል፡፡ ይሄ ሙሉ በሙሉ የመቆጣጠር ፍላጎት የፖሊሲ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን የስርዓቱ ወሳኝ አካል ነው፡፡

ሁለተኛ የዚህ ሙሉ በሙሉ መገናኛ ብዙሐንን የመቆጣጠር ዓላማ የሕዝብን በጎ ፈቃድ ለመፈብረክ ነው፡፡ ይህን በሚያደርግበት ጊዜ የፖለቲካና የርዕዮተ ዓለም ፉክክር እንዲኖር አይፈቅድም፡፡ ይህንንም የአዕምሮ ውጤት ማምረቻ (Means of Mental production) መቆጣጠር ለምን እንዳስፈለገ ለመረዳት የስዕልና የሙዚቃ አቀራረብን እንደምሳሌ እንውሰድ፡፡

ሙዚቃም ሆነ ስዕል እሙን ከመሆናቸው በፊት የምንም ነገር አለመኖርን (nothingness) ቅድመሁኔታቸው ያደርጋሉ፡፡ አንድ የሙዚቃ ኮንሰርት ከመቅረቡ በፊት አዳራሹ ሰጥ ረጭ ማለት አለበት፡፡ ከሙዚቃው ውጪ ያሉ ድምፆች በሙሉ የመደመጥ ፉክክርን እንዳይፈጥሩ ይወገዳሉ፡፡ በስዕል በኩልም አንድ ሰዓሊ የሚስልበት ወይም የምትስልበትን ሸራ ከስዕሉ ውጪ ያሉ ተፎካካሪ ቀለማትን ለማጥፋት በነጭ ቀለም ይቀቡታል፡፡ ልክ እንደሙዚቃው እና ስዕል ኢሕአዴግም ተፎካካሪ የሚላቸውን የሐሳብ ድምፆችና የአመለካከት ምስሎች አስወግዶ ያለውድድር የራሱን ብቸኛ የአመለካከት ውጤት እንዲንሰራፋ ያደርጋል፡፡

የሕግ የበላይነት
የኢሕአዴግ ስልጣን በጥቂት ሰዎች እጅ ሲከማችና መሪዎች የሕግ ማዕቀፍ ሳይጣልባቸው የፈለጉትን የሚያደርጉበት ስርዓት ዋናው መሠረቱ ከሕግ ልጓም የተላቀቀና ያሻውን ያለገደብ ስልጣንን መጠቀም ነው፡፡ ከዚህ በመነሳት የተወሰኑ ነጥቦችን እናያለን፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ በሕግ የበላይነት (rule of law) እና በሕግ የመገዛት (rule by law) መካከል ልዩነት እንዳለ ማስታወስ የግድ ይላል፡፡ ይህ ሲባል ሕጋዊነት፣ የሕግ የበላይነት አካል ነው እንጂ የሕግ የበላይነት አጠቃላይ ገላጭ አይደለም፡፡

በመሆኑም ሕጉ ለመንግስት የፈለገውን ለማድረግ ገደብ የለሽ ስልጣን ቢሰጠው ድርጊቱ ሕጋዊ ሊሆን ይችላል፡፡ ሆኖም ግን በሕግ የበላይነት ማዕቀፍ ስር ሊወድቅ ይችላል፡፡ የሕግ የበላይነት የመንግስትን ማንአለብኝነት ስለሚገታው ለዴሞክራሲ ማበብ ትልቅ ሚና ይጫወታል፡፡

ሌላው የauthoritarianism (ስልጣን በጥቂት ሰዎች እጅ ሲከማችና መሪዎች የሕግ ማዕቀፍ ሳይጣልባቸው የፈለጉትን የሚያደርጉበት ስርዓት) መገለጫ የራሳቸው ልዕልና ያላቸው መንግስታዊ ያልሆኑ ማኅበራት እንዲኖሩ አይፈቅድም፡፡

መደምደሚያ
በዚህ ጽሑፍ መግቢያ ላይ ሦስት የዴሞክራሲ መርሖችን አንስተን ነበር፡፡ ሀ. ግላዊ ኃላፊነት፣ ለ. በሕዝብ በጎ ፈቃድ ላይ የተመሠረተ መንግስት እንዲሁም ሐ. የሕሊና ነጻነት ናቸው፡፡

እነኚህ ሦስት የዴሞክራሲ ብሒሎች ሰፋ ያሉና የተወሳሰቡ ሐሳቦችን ያቀፉ በመሆናቸው በአንድ የመጽሔት አምድ ላይ አጠቃላይ ይዘታቸውን እና የያዙትን እንደምታ ማቅረብ ያስቸግራል፡፡ ሆኖምግን በነዚህ ሐሳቦች ዙሪያ ከአገራችን ጋ በቀጥታ በተያያዘ ጉዳይ አንድ ሁለት ነጥቦቸን አንስተን ጽሑፋችንን እናጠቃልላለን፡፡

እያንዳንዱ ግለሰብ የራሱን ሕይወት የመምራት መብት አለው ሲባል፣ መንግስት ሕጋዊ ካልሆነ በቀር ጣልቃ የመግባት መብት እንደሌለው መታወቅ አለበት፡፡ ሆኖም ግን በኢትዮጵያ ገዢው ፓርቲ ገበሬውን ‹‹በዓመት ይህን ያክል ቀን በነጻ የአካባቢ ጥበቃ ሥራ ላይ መሳተፍ አለባችሁ፡፡ እምቢ ካላችሁ የገንዘብ ቅጣት ይከተላል፡፡›› እየተባለ ገበሬው በግዴታው የግል እርሻ ሥራውን በመተው ተራራ ሲቆፍር እንዲውል ተደርጓል፡፡

እንዲህ ዓይነት ድርጊት ላይ የሕግና የሞራል ጥያቄዎችን ማንሳት ይቻላል፡፡ አንደኛ ገበሬው ለሚመጣው ትውልድ ጠቀሜታ ሲባል የተወሰነ ጊዜውን መስዋዕት አድርጎ ተከፋይ ባልሆነበት የጉልበት ሥራ ላይ እንዲሰማራ ማስገደዱ ችግር የሚሆነው አገሪቱ የገበሬዎች ብቻ ሳትሆን የሁላችንም ስለሆነች መስዋዕትነት መክፈል ካስፈለገ ሁላችንም መክፈል አለብን እንጂ ገበሬው ብቻ ተመርጦ ሳይከፈለው መሥራት አለበት የሚል እምነት የለኝም፡፡ እንደመንግስት ሪፖርት ከሆነ 26 ሚሊየን ገበሬ በዚህ የጉልበት ሥራ ላይ ተሰማርቶ ከ8 ቢሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያለው ገቢ በጉልበት መልክ መንግስት አግኝቷል፡፡

ምናልባት እዚህ ላይ ቆም ብለን ነገሩን ስናገናዝብ በአብዮት ጊዜ ‹‹መሬት ላራሹ›› የሚለው ጥሪ ያስተጋባው ገበሬው አርሶ የላቡን ዋጋ አላገኘም በሚል ነበር፡፡ አሁንም እንደትላንቱ ‹‹መሬት ላራሹ›› እንደተባለ ‹‹ሒሳብ ለላቡ›› ብለን የምንጠይቅበት ጊዜ ላይ የደረስን ይመስለኛል፡፡

በሕዝብ በጎ ፈቃድ ላይ የተመሰረተ መንግስት ጽንሰ-ሐሳብን በተመለከተ ኢሕአዴግ የርዕዮተ ዓለም ውድድር እንዳይኖር ከማድረጉም ባሻገር መሬትን እና የከተማ ቤትን እንደፖለቲካ መሳሪያ በመጠቀም የሕዝብን መልካም ፈቃድ ለማግኘት የሚያደርገው የማያልቅ እንቅስቃሴ ነው፡፡ በመሠረቱ ‹ሕዝባዊ ፈቃድ› ወይም ስምምነት የሚባለው ቃል እንደ አንድ ዴሞክራቲክ መርሕ ሲታይ ‹‹ዜጎች የፈለጉትን እንዲመርጡ ልዕልና አላቸው›› ከሚል መሠረተ ሐሳብ የፈለቀ ነው፡፡

ሆኖም ግን በአገራችን የገጠር መሬትን እና የከተማ ቤትና ቦታን ይዞታን ተቆጣጥሮ የዜጎችን የፍላጎቶቻቸውን የመወሰንና የመበየን አቅማቸውን በእጅጉ አዳክሞታል፡፡ በመሆኑም ይህ ሁኔታ ምርጫ ላይ ትልቅ ተፅዕኖ ያሳርፋል፡፡

ለማጠቃለልም በእኔ እምነት ኢሕአዴግ ሕገ መንግስት አርቅቆ ሕገመንግስታዊነትን ሳይሆን በሁሉም መስክ ፍፁማዊ የበላይነትን የተጎናፀፈ ስርዓት ነው፡፡

-----
ይህ ጽሑፍ በአዲስጉዳይ መጽሔት ቅጽ 6 ቁጥር 134 የተስተናገደ ነው፡፡

No comments:

Post a Comment