Wednesday, July 30, 2014

የዞን ዘጠኝ ጦማርያንና ጋዜጠኞችን ክስ አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ



አገራችን ኢትዮጵያ በጥሩ ልትጠራባቸው የምትችላቸው ጉዳዮች እንዳሉ ሆነው በድህነት በሰብዓዊ መብት አያያዝ፣ በሙስና እና ሃሳብን ነጻነት በመግለጽ መብት የተለመዱ የምናፍርባቸው ጉዳዩች ሆነው መቀጠላቸው እሙን ነው፡፡ ሃሰብን በነጻነት መግለጽን አስመልክቶ ሶስት ወራትን ከፈጀ ምርመራ በኋላ በብዙ የፓሊስ ድብብቆሽ ሂደት የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ላይ ባለፈው አርብ ክስ መመስረቱም አብሮ ይታወሳል

ጓደኞቻችን ከታሰሩ ጊዜ ጀምሮ መንግሰት ያቀረበውን ውንጀላ አስመልክቶ በተለያየ ወቅት ሃሳባችንን ለመግለጽ አስበን ምናልባት የምንሰጠው ሃሳብ አሁንም በመንግሰት እጅ የሚገኙት ጓደኞቻችን ላይ ሊኖረው የሚችለውን ተጽእኖ በመፍራት እነዲሁም ለመንግሰት እድሉን በመስጠት ኦፌሻል ክሱን እስክናይ ድረስ በጠቅላላ ሃሳቦች ላይ አስተያየት ከመስጠት ውጨ ብዙም ሳንል ቆይተናል፡፡ አሁን ግን ክሱ አንድ የዞን 9 ጦማሪን ጨምሮ በይፋ በመመስቱ እነዲሁም በክሱ ላይ ተጠቀሱት ክሶች አንዳቸውም እውነት ባለመሆናቸው ክሱን አስመልክቶ ዘርዘር ያለ ማብራሪያ መስጠት እነዳለብን ተሰምቶናል፡፡

  ክሱ በአጭሩ

በአስሩ ተከሳሾች ላይ የተጠቀሱት የክስ አይነቶች ሁለት ሲሆኑ አንዱ የሽብር ተግባርን ማቀድ ማሴር ማነሳሳትና መፈጸም ሲሆን (የጸረ ሽብር ህጉ አንቀጽ አራት) ሁለተኛው ህገ መንግሰታዊ ስርአቱን በሃይል መናድ( የወንጀለኛ መቅጫ ህጉ አንቀጽ 238) የሚሉ ናቸው ፡። ክሱ ላይ በፓርላማ በሽብተኝነት ላይ ከተፈረጁ ድርጅቶች ቀጥታ ትእዛዝ በመቀበል በህቡእ በመደራጀት የሽብር ተግባር ላይ መሰማራት እና የመሳሰሉት ክሶች በዝርዝር ቀርበዋል፡፡ ከሶቹ ሲጠቃለሉ

1. ከግንቦት ሰባት ጋር እና ከኦነግ ጋር ግንኙነት መፍጠር ትእዛዝ መቀበል
2. ስሙ ባልተጠቀሰ የህቡእ መደራጀት እና ስራ ክፍፍል መፍጠር
3. Security in a boxን ጨምሮ ስልጠና መውሰድ
4. አመጽ ቡድኖችን ማደራጀትና አመጽ ማነሳሳት  የሚሉት ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡

ከግንቦት ሰባት ጋር እና ከኦነግ ጋር ግንኙነት መፍጠር ትእዛዝ መቀበል
ከዚህ በፊትም እነደተናገርነው  ማንኛቸውም የዞን9 ጦማርያን በፓርላማ በሽብር ከተፈረጁ ወገኖች ጋር ምንም ግንኙነት የለንም፡፡  ብዙ  የዞን9 ነዋሪያንንም አንደሚረዱት አብዛኛዎቹ የዞን9 ጦማርያን እነዚህ አካላት ላይ በሚያደርጉት ከፍተኛ ትችት እየታወቁ ጉዳዩን ከሽብርተኛ ድርጅቶች ጋር ለማያያዝ መሞከር ፣መንግስት የፈረጃቸውን ድርጅቶች እነደፈለገ ማንንም ሰው ለመክሰስ አንደሚጠቀምበት ከማሳየት ባለፈ ትርጉም የማይኖረው ነው፡፡ ለማጠቃለል ያህል ማንኛቸውም የዞን9 አባላት አገር ውስጥም ሆነ ውጪ አገር ያለ የፓለቲካ ደርጅት አባላት አይደሉም፡፡ ይህንን የሚያሳይ መረጃም መንግሰት ለማቅረብ አንደማይችልም አናውቃለን፡፡ ( የማስረጃ ዝርዝር ላይ ወደታች የምንመለስበት ይሆናል)

ስሙ ባልተጠቀሰ የህቡእ መደራጀት እና ስራ ክፍፍል መፍጠር
በክሱ ላይ ስሙ ያልተጠቀሰ የህቡእ ሽብር ድርጅት በመመስረት ተከሰናል፡፡ በመሰረቱ መንግስት ዞን9 የሚለውን ስም አንድም ቦታ በክሱ ላይ ለመጠቀም ያልፈለገው የጦማርያኑን ቡድን ይበልጥ ታዋቂ እነዳይሆን ለማድረግ አንደሆነ አንገምታለን፡፡ ይህ አስቂኝ ክስ አንድም ቦታ ላይ የዞን9 ስም ባያነሳም በደፈናው በህቡዕ መደራጀት ብሎ ከሶናል፡፡ በመሰረቱ መንግሰት እኛን ለማግኘት ምንም አይነት የደህንነት ስራ እነዳላስፈለገው አናውቃለን፣. ምክንያቱም ሁሉም የዞን ፱ ጦማርያን ስማቸውና ፎቶአቸውን ማስቀመጣቸው ቋሚ የምንስማማበት እሴት ስለነበር ነው፡፡ የምንጽፈው ነገር በተናጠል ሃላፊነትን አንድንወስድ አንዲሁም ሌሎችን ሃሳብ መግለጽን ለማበረታታት በማሰብ በአደባባይ  እነዲታይ የወሰነውን የጦማርያንን ስብስብ ‹‹ህቡዕ›› ብሎ መጥራት ማንን ለማሞኘት አንደሆነ ግልጽ አይደለም፡፡ ዞን፱ ድብቅ እነዳልሆነ እያንዳንዱ ጽሁፍም በተናጠል ሃላፊነቱን የሚወስድ ጸሃፊ የቡድን ጽሁፎች ሲሆኑ ደሞ የቡድን ሃላፌነት አንደምወስድ ማንም የጦማራችን አንባቢ ያውቀዋል፡፡ መንግስት የዞን፱ አይነት ጦማሮችንም ሆኑ የአንተርኔት አንቅስቃሴዎቸን የሚመዘግብበት አሰራር አለመኖሩ ደሞ የእኛ ጥፋት ተብሎ ሊቆጠር አይችልም፡፡ተሰብስቦ መጦመርን የሚከለክል ምንም አይነት የህግ ክልከላም የለም፡፡ በመሆኑም ተሰብስበን መጻፋችን  ራሳችንን ገልጸን ሃሳባችንን መግለጻችን የጣስነው ምንም ሕግ የለም፡፡ፓሊስም ሆነ መንግሰት ሶስት ወር በፈጀ ምርመራው ህቡዕን ትርጉም ትርጉም በሚገባ አለማወቁም ጉዳዩን አስተዛዛቢ ባስ ሲልም መሳለቂያ ያደርገዋል፡።  

Security in a boxን ጨምሮ ስልጠና መውሰድ

Security in a box ኢንተርኔት ላይ የሚገኝ የኢንተርኔት አንቅስቃሴን በጥንቃቄ ለማድረግ የሚረዳ ኦፕን ሶርስ የስልጠና ማንዋል ሲሆን ይህንን ስልጠና መውሰድ በምንም መልኩ ወንጀል ሊሆን አይችልም፡፡ ይህ የስልጠና ማንዋል ለማንኛውም የሰብአዊ መብትና ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት የሚያሳስባቸው ሰዎች አንዲያገኙት ሆኖ የተዘጋጅ  ፍሮንት ላየን ዲፌንደርስ እና ታክቲካል ቴክ የተባሉ አለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተቋማት ያዘጋጁት ስልጠና ነው፡፡ በመሰረቱ ይህንን ስልጠና ወንጀል አድርጎ ከማቅረብ በፊት ጎግል ላይ አስገብቶ መፈለግና ውጤቱን ማየት ከአንደዚህ አይነት አሳፋሪ ክስ ያድን ነበር፡፡ ይህ በበጎ መልኩ አንረዳው ካልን የፍትህ አካላቱ ከቴክኖሎጂ ጋር ያላቸውን ከፍተኛ ርቀት የሚያሳይና መንግሰትም በሰፊውና በቅንጅት ሊሰራበት የሚገባ ክፍተት ሲሆን ከዚያ ባለፈ ካየነው ደሞ መንግሰት እሱ የማያውቀውን ማንኛውንም ነገር ያለምንም የህግ ክልከላ  ወንጀል ብሎ ለመፈረጅ ያለውን ጉጉት ያሳያል ያ በራሱ ደሞ መንግስትን ራሱን ህገ ወጥ እነደሚያደርገው ያለምንም የህግ እውቀት ማሰብ ብቻ ለሚችል ሰው የሚገለጥ ሀቅ ነው፡፡
በዚህ አጋጣሚ ወንጀል ተብለው የተለያዩ ስልጠናዎች በሚል የተጠቀሱት የኮምኒኬሽን ስልጠና የስትራቴጂክ ስልጠና የአድቮኬሲ ስልጠና የመሳሰሉት መሆናቸውን ለመጥቀስ አንወዳለን፡፡ በመሰረቱ በተለያዩ ድርጅቶች ግብዣ ስልጠና መውሰድና የሰብአዊ መብት ፎረሞች ላይ መገኘትን ወንጀል የሚያደርግ ህግ አለመኖሩን መንቀሳቀስም የዜጎች ሰብአዊ መብት መሆኑን ለአቃቢ ህግ ህግና ፓሊስ ካላወቁ ማን ሊያውቅ ነው ??

የተደራጁት የአመጽ ቡድኖችን ማደራጀት  እና 48 ሺህ ብር ለአመጽ ማከፋፈል
መንግሰት የአመጽ ቡድኖችን ማደራጀት በሚል ያቀረበውን ክስ ለመመለስ ያህል አንድ ጥያቄ ብቻ አንጠይቃለን? የታሉ የተደራጁት ቡድኖች?  ምንም የተደራጀ ቡድን በሌለበት ይህንን ክስ ማቅረብ በፍትህ ስርአቱ ማፌዝ ካልሆነ በስተቀር ሌላ ምን ይባላል? በ48 ሺህ ብር የአመጽ ማነሳሳት ክሱን ከብሩ ማነስ በላይ ይበልጥ አስቂኝ የሚያደርገው የማስረጃው ዝርዝር ላይ ያለው ማስረጃ እና ክሱ የተለያዩ መሆናቸው ነው፡፡ ክሱ 48,000 ብር ከውጪ በመቀበል በማለት በደፈናው ላኪውን ሳይጠቅስ ያለፈው እና ለሽብር ተግባር የተባለው አርቲክል 19 ከተባለ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ለታሰሩ ጋዜጠኞች ቤተሰቦች የሚደረግ ድጋፍ ሲሆን በወቅቱ ጦማሪ ናትናኤል ፈለቀ ባንክ ስለሚሰራ ተቀብሎ ለጋዜጠኛ ርዩት አለሙ ቤተሰቦች እስር ቤት መመላለሻ ተብሎ የተሰጠ ድጋፍ ነው፡፡
የተያያዘው የባንክ ደረሰኝም ያንን የሚያሳይ ሲሆን ክሱ ላይ በይፋ መጥቀስ ያልተፈለገው ለምን ይሆን? (ጦማርያኑ እና ጋዜጠኞቹን መታሰር ተከትሎ መንግስት ፋይል የከፈተበትን ከሰብአዊ መብት ተቋማት ነን ከሚሉ ድርጅቶች የሃሳብና የገንዘብ ድጋፍ በመቀበል ሶሻል ሚዲያን በመጠቀም አመጽ ማነሳሳት የሚለውን ክስ ተከትሎ የተባበሩት መንግሰታት የሰብአዊ መብት ጉባኤ ከአለም አቀፍ ተቋማት ጋር በጋራ መስራት ወንጀል ሊሆን አይገባም በሚል ርእስ እስሩን የሚያወግዝ መግለጫ ማውጣቱ ይታወሳል)

ማስረጃው ሲገመገም
እስካሁን በእጃችን የደረሰውን የማስረጃ ዝርዝር በሶሰት ከፍለን ማየት አንችላለን ፡፡ ከማስረጃ ዝርዝሩ ውስጥ አብዛኛውን ቦታ የሚይዘው በተለያየ ወቅት የተጻፉ የጦማርያኑ ጽሁፎች ሲሆኑ ጋዜጠኞቹ ላይ ደሞ ጭራሽ የመረጃ ዝርዝር ለማቅረብም አልተቻለም፡፡(አቃቤ ህግ የሁሉንም የበይነ መረብ ዘመቻዎች መግለጫ እና እቅድ እንደማስረጃ አቅርቧል)  በሁለተኛ ደረጃ የቀረቡት የተለያዩ የጉዞ ትኬቶች አለም አቀፍ ስብሰባ ማስታወሻዎች አንዲሁም ፕረዘንቴሽኖች  ሲሆኑ ሁሉም ጦማርያኑ ያደረጓቸው አለም አቀፍ ጉዞዎችን የሚያሳዩ የተሳተፉባቸው ሰብአዊ መብትና ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት የተመለከቱ የአፍሪካ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን እና የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ጉባኤ የተደረጉ ጉዞዎችን ናቸው፡፡
በማስረጃ ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱት የሽብር ተግባር የተደረጉ ጉዞዎች ተብለው መሆኑ ይበልጥ ክሱን አሳፋሪ ያደርገዋል፡፡ መንግሰት ጉዞዎቹ የተደረጉትም ሆነ የስልጠና ግብዣዎቹ የመጡት ከአለም አቀፍ መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት አንደሆነ እያወቀና እና ማስረጃው ላይም በግልጽ እየታየ የሽብር ቡድኞች ብሎ ግንቦት ሰባትና ኦነግን ጣልቃ ማስገባቱ አስገራሚ ነው፡፡ (የፍርድ ሂደቱ ላይ እነዚህ ተቋማት ጋር የተደረጉ ግንኙነቶቸን አንዴት ብለው በፓርላማ ከተፈረጁ የሽብር ተቋማት ጋር እነደሚያገናኛቸው አብረን የምናየው ይሆናል)  በሶስተኛ ደረጃ የተቀመጡት ከ2005 ዓ.ም ጀምሮ የተደረጉ የስልክ ልውውጦች ሲሆኑ በፍርድ ቤት ሂደቱ ውስጥ በዝርዝር የምናያቸው ይሆናል፡፡  በመጨረሻም ተከሳሽ ቤት ተገኘ የተባለውና ፓሊሶች ራሳቸው ያመጡት ከግንቦት ሰባት ጋር የተገናኙ ዶክመንቶች እና የአባላት መጽሄት ሲሆን በፍተሻው ወቅት ፓሊሶች ራሳቸው ፍሪጅ በስተጀርባ አገኘን ብለው በፍተሻ ወቅት ከፍተኛ አለመግባባት ተፈጥሮ የራሳቸውን ምስክሮች ብቻ አስፈርመው መሄዳቸውን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

እንዲሁም ፓሊስ 18 የሰው ማስረጃ ለማሰማት የስም ዝርዝር ማስገባቱን እና የስም ዝርዝሩም እጃችን ላይ የሚገኝ ቢሆንም ከፍርድ ቤት ለሚመጣው የፍርድ ውጤት ሳይሆን በአጠቃላይ የፍትህ ስርአትን ማክበር ሃላፊነት ስላለብን ብቻ እዚህ ጽሁፍ ውስጥ ላለማካተት ወስነናል፡፡

እንደማጠቃለያ
የዞን፱ ጦማርያን ከዚህ በፊትም በተለያየ ወቅት አንደተናገርነው የመንግሰት ይህን ሁሉ ጊዜ ወስዶ ይዞ የመጣው ማስረጃ የአደባበይ ጽሁፎች እና በተለያየ ወቅት የተደረጉ የአደባባይ ሁነቶች( public events) ጥርቅም መሆኑ የክሱን ፓለቲካዊነት ያረጋገጠ ነው፡፡ ጦማርያኑ የፍርድ ቤት ስርአቱን የተለያዩ አለም አቀፍ የወንጀል ስነስርዓት ደረጃን በጠበቀ መልኩ ህጉን አክብረው የሚከታተሉ ሲሆን እኛም ሂደቱን በተቻለ መጠን ለዞን ፱ ነዋሪያን ለማሳየት ለማሳወቅ የምንጥር መሆኑን ለማሳወቅ አንወዳለን፡፡ በተደጋጋሚ ተፈትኖ የወደቀው የአገራችን ፍርድ ቤት እና የፍትህ ስርአት ገለልተኝነት ይህንን እድል በመጠቀም ራሱን ለማሻሻል መፍቀዱን እነዲያሳይና ፍርድ ቤቱ ማስረጃዎቹን አይቶ ክሱን እነዲዘጋ ጥሪ እያደረግን ይህንን በማድረግ የአገሪቱን የፍትህ ሂደት አንድ ደረጃ የማራመዱን እድል ዳኞች እንዲጠቀሙበት መንግስትን ከወራት በፌት የሰራውን ስህተት ለማስተካከል እድሉ ዛሬም ያልመሸ መሆኑን ለማስታወስ አንወዳለን፡፡

የታሰራችሁ ጦማርያንን እና ጋዜጠኛ ወዳጆቻችን ለከፈላችሁት መስዋእትነት ውለታችሁ አለብን፡፡ እንኮራባችኋለን!!  




ማስረጃ ተብለው የቀረቡ ሰነዶች ለፈገግታ ያህል
ዞን ዘጠኝ ላይ የታተሙ ጽሁፎች

  1. ነጻነትና ዳቦ - በናትናኤል ፈለቀ
  2. ሳንሱር ዋጋ ያስከፍላል - በናትናኤል ፈለቀ
  3. ስደትና ፍቅር - በሰለሞን አብርሃም(ከአውሮጳ)
  4. ዋኤል ጎኒሞ ኢትዮጵያዊ ቢሆን ኖሮ ….? - በበፍቃዱ ሃይሉ
  5. ልማታዊ ጋዜጠኝነት ወይስ ይሁንታን ማምረት? - በእንዳልካቸው ሃይለሚካኤል
  6. እኛና ሶማልያ - በናትናኤል ፈለቀ
  7. ድምፃችን ይሰማ - በእንዳልካቸው ሃይለሚካኤልና እና በፍቃዱ ሃይሉ
  8. እንዴት እንደመጥ - በማህሌት ፋንታሁን
  9. የመለስ ውርስ እና ራዕይ - በሶሊያና ሽመልስ
  10. የቅድመ ምርመራ ቅድመ ምርምራ - በማህሌት ፋንታሁን
  11. ትግራይና ሕዋሐት ምንና ምን ናቸው ? -በበፍቃዱ ሃይሉ
  12. ህግ ምርኩዝ ነው ዱላ በዘላለም ክብረት

ከበፍቃዱ ብሎግ(www.befeqe.com) የተገኙ

  1. ከ21 አመት በኋላ ዴሞክራሲ ሲሰላ
  2. ኢትዮጵያ ውስጥ የመንግስት መመሪያ በማክበር መሥራት ይቻላል?
  3. አብዮት ወረት ነው
  4. የእህአዴግ ‹‹ትርፍ›› እና ኪሳራ
  5. የኢትዮጵያ መንግስት መጠላቱን የሚያሳብቁ ምልክቶች
  6. ከእከሌን አሰሩት እስከ እከሌን አገዱት
  7. ሰማኒያ ሚሊዮን እስከምንደርስ እንታገላለን
  8. “ድር ቢያብር” ለአምባገነኖች ምናቸው ነው ?
ከሌሎች ብዙ ዝርዝሮች በጥቂቱ

  1. “ኢትዮጵያዊ ማንነት ከሌለ ትግሬያዊ ማንነት የለም” – (በአብርሃ ደስታ ጽሑፍ ከፌስቡክ የተወሰደ) /በበፍቃዱ ቤት የተገኘ/
  2. “መንግስት የለም ወይ ?” የምንና ምን አይነት መንግስት(የመስፍን ነጋሽ ጽሑፍ ከፌስቡክ የተወሰደ ) /በበፍቃዱ ቤት የተገኘ/
  3. የሁለተኛው ዘመቻ ዕቅድ ( ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት አሁኑኑ)
  4. የ2ኛው ዘመቻ ጋዜጣዊ መግለጫ (ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት አሁኑኑ)
  5. ዳዊት ሰለሞን ስለአዲሱ የጋዜጠኞች ፎረም ፕሬዚዳንት ፌስቡክ  ላይ የፃፈው እና አጥናፍ ለበፍቄ ኢሜል የደረገለት ጽሑፍ
  6.  “ፍርሃታችን የት ያደርሰናል ?” በሚል በኤልያስ ገብሩ ተጽፎ በፍቄ ላፕቶፕ ውስጥ የተገኘ(ለዕንቁ መጽሄት ተዘጋጅቶ ያልታተመ ጽሑፍ)
  7. የ3ኛው ዘመቻ ጋዜጣዊ መግለጫ ( ዴሞክራሲን በተግባር እናውል የሰላማዊ ሰልፍ መብታቸን ይመለስ)
  8. “ሰልፍና ሰይፍ ” በሚል በበፍቄ ተጽፎ ነገር ግን ያልታተመ ጽሁፍ ከላፕቶፑ
  9. የ1ኛው ዘመቻ ጋዜጣዊ መግለጫ(draft ሕገ መንግሰቱ ይከበር)
  10. የ4ኛው ዘመቻ ዕቅድ( ኑ ኢትዪጲያዊ ህልም አብረን እናልም)
  11. ጋዜጠኛ አስማማው ለድምፃችን ይሰማ የፌስቡክ ገጽ ያዘጋጀቸው ጥያቄዎች ከኢሜሉ (ለአዲስ ጉዳይ መጽሄት)
  12. ስለ ዞን 9 ዘመቻዎች globalvoicseonline.org ላይ የታተሙ ጽሑፎች
  13. በናትናኤል በኩል ለርዕዮት ዓለሙ ቤተሰቦች ከ Article 19 የተላከ 48,170.25(ብር) የዌስተርን ዩኒየን ኮፒ
  14.  “የተቃውሞ ሰልፉ ዕድሎች እና ተግዳሮቶች” በሚል አዲስ ጉዳይ ላይ የታተመ ጽሁፍ (draft)
  15. ማሒ ስለ ርዕዮት ዓለሙ እና ስለ አዲስ ዘመን “አዝማሚያ ጥናት ” በቀልድ የጻፈችው ጽሑፍ፡፡
  16. የዞን 9 ወደፌት ለመስራት የታቀዱ ሶስት ፕሮጄክት ፕሮፓዛሎች ( ምርጫ 2007 ሪፓርት የማድረግ ስራ፣ የኢትዮጲያ የነጻነት ኢንዴክስ ማዘጋጃት ስራ ፣ ገጠሪቷ ኢትዮጲያ ላይ ለመስራት የታሰበ ዶክመንተሪ እቅድ)
  17. እና ሌሎችም ትርኪሚርኪዎች (ለምሳሌ የዳንኤል ብርሃነ ጽሑፍ፣ የናቲ የ10ኛ ክፍል ግጥም)
#Ethiopia #FreeZone9Bloggers #FreeEdom #FreeTesfalem #FreeAsmamaw #FreeAllPoliticalPrisoners

Tuesday, July 29, 2014

የኢትዮጲያዊነት ውርስና ቅርስ ማኅበረሰብ በሰሜን አሜሪካ ለዞን9 ጦማርያን ሽልማት አበረከተ

#Ethiopia #FreeZone9Bloggers #FreeEdom #FreeTesfalem #FreeAsemamaw 

የኢትዮጲያዊነት ውርስና ቅርስ ማኅበረሰብ በሰሜን አሜሪካ ለዞን9 ጦማርያን ሽልማት አበረከተ 

በሰሜን አሜሪካ የሚገኘው ኢትዮጲያዊነት ውርስና ቅርስ ማኅበረሰብ በእስር ለሚገኙት የዞን 9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ያልተዘመረላቸው ጀግኖች በሚል በአራተኛው አመታዊ ክብረ በአል ላይ ሽልማትን አበርክቶላቸዋል፡ 

 
በየአመቱ በሚደረገው በዚህ ክብረ በአል መዝጊያ ስነስርአት ላይ የማህበሩ የቦርድ ሰብሳቢ አቶ አበበ የዞን9 ጦማርያን ከፍተኛ መስዋእትነትን የሚከፈልበትን ሃሳብን አገር ውስጥ ሆኖ እውነትን የመናገርን ሃላፌነት ወስደው እየከፈሉት ላሉት መስዋእትነት እውቅና መስጠት ማስፈለጉን ተናግረዋል።


ይህ ያልተነገረላቸው ጀግኖች በሚለው ምድብ የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች እውቅና የተሰጣቸው ሲሆን ከዚያ በተጨማሪ ሁለት ተሸላሚዎች ከአገረ አሜሪካን ሽልማት ወስደዋል፡፡

የዞን9 ጦማርያን በታሰሩ ጦማሪ ጓደኞቻችን እና ጋዜጠኞችን ስም ለተሰጠው እውቅና ሽልማት ከፍ ያለ ምስጋና እናቀርባለን፡፡