Thursday, August 9, 2012

ሎሚ ሽታ… መጽሐፍ አንደ ፊልም

ሶሊያ ሽመልስ
መጀመሪያ ይህንን ጽሁፍ ለመጻፍ ስነሳ ሙሉ ለሙሉ የፊልም ተመልካች አስተያየት ብቻ እንሆነ ይቆጠርልኝ፡፡ ባለሞያነት ሲያልፍም አይነካካኝ! ባይሆን የጥበብ አፍቃሪ ዕይታ ነገር ነው በሉና ውሰዱልኝ፡፡

የአማርኛ ፊልሞች ላይ ተስፋ ከቆረጥኩ ከራርሜለሁ፡፡ ታዲያ አንድ ከሃገር ገባ ወጣ የሚል ጥበብን በምንም ሁኔታ የሚያደንቅ ወዳጄ (እየተበሳጨም ቢሆን) እግሩ ወጥቶ በገባ ቁጥር የአገርኛ ፊልሞችን አብሬው እንዳይ ይጋብዘኛል፡፡ የእርሱን ጨዋታ ፍለጋም የፊልሞቻችንን ለውጥ ለማየትም ያህል በርሱ ግብዣ ክፍተት ልክ ነው አማርኛ ፊልሞችን የማየው፡፡ ታዲያ እነርሱም አይቀየሩም፣ እኔም አልቀየርም፤ እበሳጫለሁ፣ ያበሳጩኛል፤ ጓደኛዬን ተነጫንጬበት ቆይታችን ያበቃል፡፡ ተመሳሳይ ሁነቶችን በተመሳሳይ ስሜቶች እያስተናገድን እንደጋግማለን፡፡ እርሱ ፊልሙ ጥሩ ጎን ባይኖረው እንኳን ፈልጎ (ምንም ጥሩ ጎን የሌለው ፊልም የሚሰራባቸው አገራት መካከል መቼም ዋነኞቹ ነን፡፡ ይህንንም እንግዲህ እንደለመድነው፤ ከዓለም አንደኛ ምናምን ብለን ገጽታ ለምን አንገነባበትም?)  ይሔንን እንደዛ ቢያደርጉት እኮ ጥሩ ፊልም ይሆን ነበር፣ ትንሽ አክቲንጉን እያለ… ማጽናኛ ቢጤ ሊነግረኝ ይሞክራል፡፡ በዚህ የአገርኛ ፊልሞች ብስጭቴ ነበር ከወራት በፊት የአዳም ረታ እቴሜቴ ልቦለድ ወደ ፊልም እየተቀየረ እንደሆነ የሰማሁት፡፡ እውነቱን ልናገርና ከፋኝ! አዳም ምን ነክቶት ነው ለፊልም አሳልፎ የሚሰጠን ያውም እቴሜቴን ብዬ ለጥቂቶች ነግሬያለሁ፡፡ ኧረ እንደውም በፊስቡክ ላይ ራሱ ስጋቴን አስቀምጬ ነበር!

(ስለ አዳም ሌላ ቀን እናወራ ይሆናል ስለ እቴሜቴ ግን ዝም ብዬ አላልፍም፡፡ ከኢ-ፓለቲካዊ ንባብ ከራቅኩ ቆይቻለሁ፡፡ እንደውም ትቼዋለሁ ማለት ይቀላል፡፡ አዳም ረታ ሲሆን ግን ሁሉም ነገር ሌላ ይሆናል፡፡ በጽሑፉ፣ በፊልሙ፣ በመጽሐፉ፣ በቲያትሩ በሁሉም ቦታ የሚታየውን አገራዊ ዝቅጠት ለማረሳሳት የቀረልኝ ብቸኛ ማጽናኛ ነው፡፡ እቴሜቴ ደሞ የብዙዎቻችን (በተለይ የሴቶቹ) ታሪክ በዘመን፣ በዓይነት እና በሰፈር ተከፋፍሎ የተቀመጠበት ምርጥ ሥራው ነው፡፡ ሆ…… ስለእኔ ነው እንዴ የሚያወራው አስብሎኛል፡፡ ያውም ብዙ ጊዜ! ይህንን የምንጊዜም ምርጥ መጽሐፍ ነው አዳም ለሐበሻ ፊልም ሠሪ የሰጠብኝ ብዬ ነበር የተከፋሁት!)

ምሳጤ 1-ፓስተሩ
በዚያው የፊልሙን መሰራት በሰማሁ ሰሞን ፖስተሩን አየሁት፡፡ በእኔ ህይወት ቀዳዳ ብትገባ አገርህን ታያታለህ -የምስራቅ ንግግር የፊልሙ ፖስተር ላይ ይታያል፤ ረጋ አልኩኝ፡፡ ተመስገን! ቢያንስ ቢያንስ ቁም ነገር እንዲሆን ታስቧል ማለት ነው የሚል መረጋጋት ተሰማኝ፡፡ የፖስተሩ ገፅታ በሚገባ የተሰራ እና የመጽሐፉን መንፈስ ያልለቀቀ መሆኑ አረጋጋኝ፡፡ ሌላው የምርቃቱ ዜና ባለፉት ሳምንታት እስኪመጣ ድረስ ‹ምን አድርሰውት ይሆን፣ ምስራቅን እንዴት አደረጓት ይሆን? ወይ ጉድ እንዴት ነው አሁኑን እና ጥንቱን የሚያገናኙት?› አልፎ አልፎ የሚመጡብኝ ጥያቄዎች ነበሩ፡፡ እውነቱን ለመናገር የሚቆረጡ እና ከታሪኩ የሚወጡ ገጸ ባህሪያት እንደሚኖሩ ሁሉ ጠርጥሬ ነበር፡፡

ምሳጤ 2- ምርቃቱ
ባለሞያዎቹ አስበውበት ይሁን ሳይችሉ ቀርተው (በምረቃው ወቅት የቲያትር ቤቶችን ትብብር አለማሳየት የማርቪክ ፊልም ፕሮዳክሽን ማናጀር ወ/ት ፊቨን ጠቅሳው አልፋለች) ምረቃው የተጋነነለት እና የአሰልቺው “በመላው ኢትዮጵያ በሁሉም ቲያትር ቤቶች በተመሳሳይ ሰዐት” በሚሉ ከፊልሙ ስኬት በላይ የምርቃቱ ስኬት የሚያሳስባቸው ፊልሞች ዓይነት አልነበረም፡፡ ተመስገን ነው! ለቧልት ፊልሞች ምርቃት የምናባክነውን ረዥም ሰዐት በዚህ ፊልም ምረቃ ወቅት አልነበረም፡፡ በእርግጥ ጥቂት ቸልተኝነት እና የማስተባበር ችግሮች ይታዩበት የነበረው ይህ የብሔራዊ ቲያትሩ የመጀመሪያ ቀን የምረቃ ሥነ ስርአት እንደ ሌሎቹ ፊልሞች ዓይነት ፊልም መጠበቅ እንደማይገባ ከሚናገሩ ማሳያዎች አንዱ ነበር፡፡

በስነ-ስርአቱ ላይ ደረጀ ኃይሌ መድረኩን የመራ ሲሆን የፊልሙን መነሻ ልቦለድ ጸሐፊ የአዳም ረታን ስራዎች ዝርዝር በንባብ ለተመልካቹ አሰምቷል፡፡ የፊልሙ ዳይሬክተር እና ስክሪፕት ጸሐፊ እንዲሁም የፕሮዳክሽን ካምፓኒው ማናጀር ምስጋናቸውን ለማቅረብ ወደ መድረኩ ብቅ ብለው ነበር፡፡ ማስተባበር የጎደለውን መድረክ ይበልጥ አጋልጠውት ተሰናበቱን እንጂ፡፡ ማናጀር ፊቨን በጽሁፍ እና በንግግር መሃል ባለ በፍርሃት በተሞላ የንግግር ሙከራዋ የቲያተር ቤቶችን ወቀሳ ጀምራ አቋርጣዋለች፡፡ የገንዘብ እጥረት እንዳላጋጠማቸው እና ከ700 ሺኅ  ብር በላይ ለፊልሙ ማዋላቸውን ነግራን ከመድረክ ስትሰናበት ደረጀ ኃይሌ ታታሪ ሠራተኛ ስለሆነች ነው ንግግር ያልቻለችው ብሎ አስተባብሎላታል፤ (ምክንያቱ እና ንጽጽሩ ባይጥምም)፡፡ አብርሃም (የፊልሙ ዳይሬክተር እና ስክሪፕት ጸሐፊ) ድጋፍ ያደረጉ ሰዎችን እና  አዳም ረታን በስክሪፕት ሥራው ወቅት ላደረገለት ትብብር አመስግኗል፡፡ የፊልም አስመራቂ በማይመስል ቸልተኛ የአለባበስ ስነ ስርአት መድረክ ላይ የተገኘውን የአብሃምን አለባበስ ሳይ ምናለበት እስቲ ታዳሚውን ማክበሩን እና ማስታወሱን ለማሳየት ያህል በስነ ስርዓት ቢለብስ አስብሎኛል፡፡ እንግዳ ክቡር ነው፤ የእኛ ጥሩ ሆኖ መታየት የአክብሮታችን መገለጫ እንጂ ራሳችንን ከፍ ከፍ ማድረጊያ ተደርጎ ሊቆጠር አይገባም፡፡ (እንደዚያ ተብሎ ከታሰበ!)

ከሞላ ጎደል ባልተጋነነ የምረቃ ስነ ስርዓት እና በአዳም ረታ መልዕክት ፊልሙ ተጀመረ፡፡ አዳም በመልክቱ ሥራችን መማሪያችን ይሁን ብሎ ለባለሞያዎቹ እንኳን ደስ ያላችሁ መልእክቱን አስተላፏል፡፡

ምሳጤ 3 -የፊልም ስክሪፕቱ
አብሃም እጁ ይባረክ እና መጽሐፉን ወደ ስክሪፕት ለመቀየር የሚነሳ ማንኛውም ሰው ከዚህ በተሻለ መልኩ ሊያደርገው አይችልም ነበር እስክል ድረስ በአሳማኝ ሁኔታ ነው ከመጽሐፉ ወደ ፊልም ያሻገረን፡፡ ድሮ እና ዘንድሮን እያፈራረቀ ባሳየበት ትረካ የታደሰን ውልደት እና ዕድገትን እና የታደሰን ትዳር በተራ በተራ በምርጥ የስክሪፕት አጻጻፍ አሳይቶናል፡፡ እውነቱን ለመናገር በመጽሐፉ የነበረችው የታደሰ የረዥም ጊዜ ፍቅረኛ ሴተኛ አዳሪዋ (ጸሐይ) ካለ መኖርዋ ውጪ ላላየው እችል ይሆን ብላችሁ የምትሰጉለት የመጽሐፉ ክፍል የለም፡፡

ሎሚ ሽታ ከነአጃቢዋ ሁላገርሽ፣ ታደሰ ከነዝምታው፤ እናቱ ምስራቅ ከነምሬቷ፤ አስናቀ ከነማጭበርበሩ ሁሉም ነፍስ ዘርተው የፊልም ገጸ ባሕሪይ ሆነው አሉ፡፡ የፊል መቼት ያለምንም ማምታታት በጥራት ተሰራ ሲሆን በተራዎቹ ፊልሞቻችን ላይ እንደተለመደው ዓይነት የታሪክ ወጥነት ማጣት (ታሪክ አለን ስላሉን እንጂ ትልቁ ችግራችንማ ታሪክ ያለው ፊልም ማጣት ነው) በዚህ ፊልም ይህ ችግር ፈጽሞ አይታይም፡፡

ትወና እና ዳይሬክቲንግ
ሎሚ ሽታ የተዋናዮች ምርጫው ብዙም የሚያስከፋ አይደለም፡፡ሁሉም ፊልም ላይ የሚታዩትን እና እነሱ ከሌሉበት ፊልም የለም ብለው ከሚያስቡ የተራ ፊልሞቻችን ከዋክብት ሎሚሽታ ነጻ ነው፡፡ ተመሳሳይ እና አለመቻሉን የማያውቅ ተዋናይ የሰለቻችሁ ሎሚ ሽታን እዩት ግልግል ነው! አልፎ አልፎ ከሚያጋጥሙ የትወና ብቃት ችግሮች ውጪ በተለይ የመጽሐፉን ገጸ ባሕሪያት በሕያውነት ለማረጋገጥ እና አንባቢ ተመልካችን ላለማሳዘን እንደተጨነቁ መናገር ይቻላል፡፡ በተለይ የምስራቅን (የታደሰን እናት) እና የሁላገርሽን ገጸ ባህሪይ የተጫወቱት ተዋንያን እንደሚችሉ አሳምነውኛል፡፡ የጥንቱን የቀይ ሽብር ነጭ ሽብር ዘመን ወደ ፊልሙ የተቀላቀሉበት መንገድ የተገነጠለ (ያልተዋሀደ) ቢመስልም ያን ያህል ተመልካችን አያስቀይምም፡፡
የአስናቀ ቤት ከላይ የታደሰ ቤት ከታች የታደሰ አሮጌ መኪና የሎሚሽታ ጠይምነት ቤቱ እና የታደሰ እሳት ወይ አበባ… ሁሉም እንደሳላችሁት አሉ፡፡ ዕድሜ ለጠንካራው ፕሮዳክሽን ይሁንና  ከቤቴ በላይ ቁራ ሰፍሮም… ሳይቀር በታደሰ ቤት ጣራ ላይ ቁራው ቆሞ ይገኛል፡፡

ኮስታራው ሎሚ ሽታ
ፊልሙ ኮስታራ ነው፡፡ ኮስታራ ፊልም በናፈቀን በዚህ የቧልት ዘመን የተገኘ ጠንካራ ፊልም ሆኖ እንዲወጣ መፍቀዳቸው ባለሞያዎቹን ያስመሰግናቸዋል፡፡ ለነገሩ ሎሚ ሽታን ሲመርጡ ጉዳዩን አስበውበት እንደሆነ ያስታውቃል፡፡ ቢሆንም ተመልካችን ሳይንቁ ገበያን ሳያሳድዱ ፊልሙን በይዘቱ ብቻ እንዲታይ መፍቀዳቸው ከዘመኑ የፊልም መንፈስ የራቀ ነውና ዘመኑን ለተጋፈጣችሁ የፊልሙ አባላት ሙገሳዩ በዚሁ አጋጣሚ ይድረሳችሁ፡፡ ሎሚ ሽታ በተለያዩ የፊልም ባለሞያዊ ምዘና ቢለካ ሙሉ ፊልም ላይሆን ይችላል፡፡ ከመጽሐፍ እንደመምጣቱ ግን በዚህ ገበያን በቧልት ብቻ ለማግኘት በሚሮጥበት ዘመን እንደ መምጣቱ ግን ተሳክቶለታል፡፡ ዘመኑን ተጋፍቶ አዲስ ነገርን ሞክሮ ለዚያውም በጥሩ አፈጻጸም ለዓይናችን በቅቷልና ተሳክቶለታል፡፡ ከጥበብ ከዚህ በላይ ምን ይፈለጋል? እነ አብርሃም ከበረቱ ወይም ለሌሎች አርአያ ከሆኑ እነከአድማስ ባሻገርን፣ እነሰመመንን፣ እነሰንሰለትን… በፊልሞቻችን እናይ ይሆናል፡፡ ሎሚሽታም የቧልት ፊልምና  የስኬት ማማ ተደርጎ መቆጠር የሚያቆምበት ዘመን መጀመሪያ ሆኖ ሊቆጠር ይችል ይሆናል! ማን ያውቃል?

No comments:

Post a Comment