Thursday, August 16, 2012

ተቃዋሚውን ማን ገደለው?



ባለፈው ሳምንት ማነው ተቃዋሚው በሚል ርዕስ የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ፓርቲ መንደር የቆበትን አፋፍ፣ እንዲሁም ለሞት የበቃበትን ጉዞ ለማየት ሞክረናል፡፡ ዛሬ ካለፈው ፅሁፍ የቀጠለውን እና የተቃዋሚው ጎራ አሁን ላለበት የመቃብር ህይወት ያበቁትን ጉዳዮች በወፍ በረር እናያለን፡፡

ተቃዋሚው ሞቷል ወይስ አለሞተም? ተብሎ ክርክር ቢነሳ አልሞተም ብሎ ለማረጋገጥ እና የህያዉን ተቃዋሚ ቋሚ አካል ማሳየት እጅግ ፈታኝ ነው፡፡ በተለይም አሁን ባለንበት የኢትዮጵያ የፖለቲካ ምህዳር አንፃር፡፡ ስለዚህም አዎ ነብሱን ይማረውና ተቃዋሚውማ ሞቷል ማለትን መርጫለው፡፡ አልአዛርን ይሆናል አይሆንም በቀጣዮቹ ጊዜያት በሚከሰቱት ክስተቶች እና በድኑ በሚሰጠው ምላሽ ይወሰናል፡፡ እናም ለዛሬ ተቃዋሚውን ማን ገደለው; በማለት እንጠይቃለን፡፡ ዋነኛ ተጠርጣሪዎችንም እንመረምራለን:: የግድያው ተካፋዮችን አንድ ባንድ ለማየት እንሞክር፡፡


የሰው ልጅ ራሳቸውን ከሚያጠፉ እንስሳት አንዱ እና ዋነኛው ነው፡፡ የሰው ልጅ ራሱን ማጥፋቱ ያልተፈታ ከባድ እንቆቅልሽ ነው፡፡ ለምን ሰው ራሱን ይጠላል? ራሱንስ እንዴት ይገድላል? የሚለው ጥያቄ ዘመናትን ተሻግሮ እሰከ አሁን ድረስ  ቁርጥ ያለ ምላሽ ባያገኝም መነሻው ይሄ ነው እየተባለ መገመቱ  ግን አልቀረም፡፡ በዋነኛነትም በዘር የሚወረስ ራስን ማጥፋት (Biological Factors)፣ በስነልቦና ችግር የሚመጣ ራስን ማጥፋት ( Psychological Factors) እንዲሁም በማህበረሰባዊ ችግሮች ምክንያት የሚከሰት ራስን ማጥፋት (Sociological Factors) ይጠቀሳሉ፡፡

ታዲያ የኢትዮጵያ ተቃዋሚ የሞተው ራሱን አጥፍቶ ይሆን? ካጠፋስ በየትኛው ምክንያት ይሆን ራሱን ያጠፋው? በሶስቱ መነሻዋች እንመልከተው እስኪ፡፡

በዘር የወረሰው ራስን የማጥፋት አባዜ ((Biological Reasons)፣) በኢትዮጵያ የፓርቲ ፖለቲካ ከተጀመረ ግማሽ ምዕተ ዓመት እንኳን ያልሞላው ሲሆን ፓርቲ በመመስረት ወደ ፖለቲካው የገቡት ፖለቲከኞች በቀይ ሽብር- ነጭ ሽብር ተጠምደው አንዱ አንዱን ሲያሳድድ የተሸነፍው ራሱን ደብቆ መኖር ሲከብደው ራሱን ከሀገር በማሰደድ ፖለቲካዊ ራስን ማጥፋት ፈፅሟል፡፡ ይሄ ራስን የማጥፋት አባዜ ዛሬ ላለው ተቃዋሚ ከቀዳሚዎቹ በዘር ውርስ ተላልፎ እራሱን አጥፍቶ ይሆን?

በስነ ልቦና ችግር የሚመጣ ራስን የማጥፋት አባዜ (Psychological Reasons)፡ ሳይኮአናሊስቱ ሲግመንድ ፍሮይድራስን ማጥፋት ዋነኛው መነሻው የበዛ ራስን መጥላት (Self Hate)ነው ይለናል፡፡ ከፍሮይድ ተከትለው የመጡ ሳይኮሎጂስቶችም የፍሮይድን ሀሳብ በማጠናከር ሰው ከራሱ ጋር የሚፈጥረው ፀብ በሞት አሸናፊነት ይጠናቀቃል ይሉናል፡፡ የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ምናልባትም ራሱን አጥፍቶ ከሆነ ራስን መጥላት ምክንያት ሊሆን ይችላልን? ‹‹ለዚህ ሁሉ ዓመታት ታግየ ምንም ውጤት ማምጣት ካልቻልኩ መኖሬ ምን ሊረባ? እኔስ ለምን ቆሜ እሄዳለው?›› በማለት ራስን ማጥፋት እንደ ግለ ሂስ ቆጥሮት ይሆን?

በማህበረሰባዊ ችግሮች ምክንያት የሚከሰት ራስን ማጥፋት (Sociological Factors)፡ ፈረንሳዊው የስነ-ህብረተሰብ ሊቅ ኤሚል ዱርክሄም በህብረተሰቡ ውስጥ ተቀባይነት ማጣት እንደሁም የግንኙነት መላለት ሰዎችን ወደ ራስን ማጥፋት ይመራቸዋል በማለት ራስን ማጥፋት ማህበረሰባዊ ምክንያት አለው ይላል፡፡ ታዲያ የኢትዮጵያ ተቃዋሚስ ህብረተሰቡ አልተቀበለኝም ብሎ ራሱን አጥፍቶ ይሆን? ወይስ የአባላት እና የደጋፊዎች ቁጥር ማነስ ህብረተሰቡ ለኔ ያለውን ጥላቻ ያሳያል ብሎ ራሱን አጠፋ ይሆን?

የቤተ መንግስቱ ገዳይ (Cold Blooded Murderer from the Palace)

ራሱን አጥፍቶ ሊሆን ይችላል ከሚለው ጥርጣሬያችን በማስከተል የሚቀርበው ሌላው ተጠርጣሪ ደግሞ መኖሪያውን ከወደ ቤተመንግስት ያደረገ ነው፡፡ እንደሚታወቀው ይህ ተጠርጣሪ ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ በስልጣን ላይ የቆየ ሲሆን በህግም የብዝሃ-ፓርቲ አስተዳደርን (Multi Party System) የፈቀደ ተጠርጣሪ ነው፡፡ ነገር ግን ሁለት ሀገር ዓቀፍ ምርጫዋችን ያለምንም ችግር ከ98 በመቶ በላይ ድምፆችን በማምጣት ለማሸነፍ የቻለ ሲሆን ሶስተኛው ላይ ግን ችግር ገጥሞት ነበር፡፡ ‹‹እባካችሁ ተጠናክራችው ግጠሙኝ፣ የሚፎካከረኝ አጣሁ እኮ›› ሲል የነበረው ተጠርጣሪ ሳያስበው ህዝቡ ለተቃዋሚዎች የሰጠው ድምፅ አስበርግጎት አለማቀፍ ተቋማት ሳይቀሩ ‹‹አፍረሀል›› ቢሉትም ‹‹እንደተለመደው በሰፊ ድምፅ ማሸነፍ ባልችልም አሁንም ድሉ የኔ ነው›› በማለት ስልጣኑን አልለቅም አለ፡፡

አይ እኛ ነን አሸናፊዎቹ ያሉትን ተቃዋሚዎችም ክፉኛ አቁስሎ ለአአልጋ ቁራኛ፣ ለደዌ ዳኛ አብቅቷቸዋል፡፡ ይባስ ብሎም በቁስል ላይ እንጨት እየሰደደ አንዳንዴም በርበሬ እየነሰነሰ ስቃያቸውን በማባባስ ስልጣኑን ለማራዘም ሞክሯል፡፡ በመጨረሻም አዳዲስ ህጎችን በማውጣት የተቃዋሚውን ግብዓተ መሬት እየሳቀ ከፈፀመ በኋላ አራተኛውን ሀገራዊ ምርጫ 99.6 % ድምጽ በማምጣት ‹‹አሸንፌአለሁ›› በማለት ‹‹ቧልት›› አሰምቷል፡፡

ለዚህም ማሰረጃ የሚሆኑት ሰነዶች ተጠርጣሪው ሟችን የሚያጥላሉ ፅሁፎችን በተደጋጋሚ በልሳኑ እንዲሁም በመንግስት ሚዲያዎች ሲያሰማ የነበረ መሆኑ፣ ምንጮቻቸው ከሰለጠኑት ሀገራት ነው በማለት የተለያዩ አፋኝ ህጎችን ማውጣቱ፣ በተደደጋጋሚ ሲያደርጋቸው የነበሩት ተግባራት በጥቅሉ ሲታዩ ተቃዋሚውን የገደለው የአራት ኪሎው ተጠርጣሪ ይሆን እንዴ? ያስብለናል፡፡

ቅጥር ነብሰ ገዳይ (Mercenary)

ይሄ ተጠርጣሪ ቅጥረኛ በአንድ ወይም በሌላ መንገድ ከአራት ኪሎ ተጠርጣሪ ጋር ግንኙነት እንዳለው የሚጠረጠር ነው፡፡ ለመጠርጠሩ ዋነኛ ምክንያት የሆነው ደግሞ ከሟች (ተቃዋሚው) ጋር አብሮ አደግ ከመሆኑም በተጨማሪ አብረው የሚበሉና አብረው የሚጠጡ ጓዶች የነበሩ ሲሆን፡፡ ከጥቂት ጊዜያት ወዲህ ግን ከቤተመንግስቱ ተጠርጣሪ ጋር በፍቅር ክንፍ ብሏል፡፡ ይሄም በዋነኛነት ሟች ከሞተ ከጥቂት ጊዜያት በኋላ መሆኑ ጥርጣሬያችን ከፍ እንዲል ያደረገዋል፡፡

ለመሆኑ ይህ ተጠርጣሪ ምን ቢያገኝ ነው ወንድሙን የገደለው? ያልን እንደሆን በዋነኛነት የሚቀመጠው ሆድ አደርነት (Opportunism) ነው፡፡ ይሄን እንድንል ያስቻለን ደግሞ ተጠርጣሪው ሟች ከሞተ በኋላ የተለያዩ ንብረቶችን በግሉ ማፍራት የጀመረ ሲሆን በተለያዩ ጊዜያትም ሟችን የሀገሪቱ ዋነኛ ችግር መነሻ አድርጎ ለማቅረብ ሲሞክር ታይቷል፣ በተጨማሪም ሟች የነበረባቸውን ፓርቲዎች ለማፍረስ ከውስጥ ሌላ ‹‹አንጃ›› በመምራት ሟችን በቀን መርዞ እንደገደለው ይጠረጠራል፡፡

ሌላው እና ቅጥረኛ ገዳዩ የሟች አብሮ አደግ እንደሆነ እድንጠረጥር የሚያደርገን ጉዳይ ሟች ከሞተ በኋላ በሞቱ ደስተኛ የነበረ ሲሆን ከገዳይ ቀጣሪም ጋር አብረው መዋል እና ማደር ጀምረው ነበር፡፡ ይባስ ብሎም ‹‹ሟች መሞቱ ትክክለኛ ነገር ነው›› እያለ መግልጫ ሲሰጥ ነበር፡፡ ለህዝቡም እኔ እውነተኛ መሪህ አለሁልህ እያለ ህዝቡ ሟችን በቅጡ እንዳይቀብረው አድርጓል የሚል ጥርጣሬ አለ፡፡ እውን ተቃዋሚው የተገደለው በአብሮ አደግ ጓዱ ይሆን?

ባህል እንደ ተጠርጣሪ

ተቃዋሚውን ገድለውታል ተብለው ከሚጠረጠሩ አካላት አንዱ የህዝቡ ባህል በአጠቃላይ እንዲሁም የህዝቡ የፖለቲካ ባህል በተለይ ነው፡፡

በመጀመሪያ ደረጃ ይሄን እንድንል ያስቻለን ህዝቡ ተቃዋሚዎች ስልጣን ቶሎ ይዘው መብቱን እንዲያስከብሩለት ከመመኝት ውጭ አብሮ በመርዳት፣ አይዟችሁ በማለት፣ በአባልነት በመሳተፍ ወ.ዘ.ተ ሲደግፋቸው ብዙም አለመታየቱ ነው፡፡ ይሄም ድርጊት የህዝቡ ባህል ተቃዋሚውን በቸልተኝነት ገድሎታል እንድንል ያደርገናል፡፡ 

ሌላው የህዝቡ ባህል ለሟች መሞት ዋነኛውን ድርሻ አበርክቷል እንድንል የሚያደርገን ጉዳይ ተጠርጣሪው በተረቶቹ እንዲሁም በወጎቹ ለሟች መሞት ምክንያት የሚሆኑ ነገሮችን ሲናገር መኖሩ ነው ለምሳሌ ‹‹ሁሉንም ወይም ምንም›› በማለት የብቸኝነት መንገድን እንደ ብቸኛ አማራጭ በማየት ተቃዋሚውግማሽ እንዳይመኝ እና በጋራ እንዳይሰራ አድርጎታል የሚል ጥርጣሬ አለ፡፡

በተጨማሪም የህዝቡ ባህል ‹‹ተባበሩ ወይም ተሰባበሩ›› በማለት አንድ አይነት አቋም የሌላቸውን ተቃዋሚዎች አንድ ላይ ለማድረግ ሞክሮ እንደገደላቸው ይጠረጠራል ይሄም ተግባር አንዳንዴ እንጨትን ከብረት ጋር ለማቅለጥ እንደ መሞከር ነው፡፡ ስለዚህም እውን ተቃዋሚውን የገደለው ባህሉ ይሆን?

ሌሎች ተጠርጣሪዎች

ከላይ ከተጠቀሱት ተጠርጣሪ ገዳዮች በተጨማሪ ሌሎቻ ተጠርጣሪዎችንም ማንሳት ይቻላል ለምሳሌ ሚዲትራኒያንን አቋርጦ የመጣው ባለ ሰማያዊ አይን ተጠርጣሪ አንዱ ነው ይህ ተጠርጣሪ ቤተመንግስት ካለው ተጠርጣሪ ገዳይ ጋር ‹‹ሽብርተኝነትን መዋጋት›› የሚል ውል ተዋውሎ ለሌሎች ነገሮች ትኩረት ባለመስተጠት እና የቤተመንግስቱን ተጠርጣሪ በገንዘብ በመደገፍ ለተቃዋሚው ሞት ተጠያቂ ሊሆን ይችላል፡፡ እውን ይሄ ባለ ሰማያዊ አይን ተጠርጣሪ ተቃዋሚውን ገድሎታልን?

ሌላው ገዳይ ሊሆን የሚችችለው ተጠርጣሪይ በቀዳሚ ነገስታት ሀገሪቱ ‹‹ጥቁር ውሻ ውለጅ›› የሚል ርግማን መረገሟ ሊሆን ይችላል የሚል ኢ-ሳይሳዊ መላ ምትም ይመታል፡፡ እውን እርማኑ ተቃዋሚውን ገድሎት ይሆን?

በአጠቃላይ ተቃዋሚውን ከላይ ከተዘረዘሩት ሀይላት አንዱ ገድሎታል ወይም ራሱን አጥፍቷል ማለት እንችላለን፡፡ የገዳዩን ማንነት የሚገልፀውን ውሳኔ ለማየት ደግሞ በጉጉት እንናፍቃለን፡፡

1 comment:

  1. አይገልም ልብ የለውም!አይሞትም ነፍስ የለውም!ሞተ ካሉት ለቅሶ ይቀመጣል።!

    ReplyDelete