Tuesday, August 28, 2012

ከመለስ በኋላ!



በአዲስ አበባ ዪኒቨርስቲ የፍልሰፍና መምህር እና ከጥቂት የአደባባይ ምሁራን አንዱ የሆነውን ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋን አነጋግረን  ስለወቅቱ ማሕበራዊ እና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ዙሪያ የተለያዩ  ሐሳቦችን ማቅረባችን ይታወሳል፡፡አሁን ደግሞ የአቶ መለስን ‘ድንገተኛ!?’ ሞት  ተከትሎ በድኀረ-መለስ  አትዮጵያና በሌሎች ተያያዥ ጉዳየች ዙሪያ እንደተለመደው ገዢ ሐሳቦቹን ሰጥቶናል፡፡ መልካም ንባብ

የመርዶው ሕዝባዊ ምላሽ

እንደሚታወቀው ለሀያ አንድ አመታት በሙሉ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥኑን መስኮት አጣበው ይዘውት የነበሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ መለስ ዜናዊ ናቸው፡፡እንዲሁም በከፍተኛ ሁኔታ ተክለ ስብዕናቸውና ስራቸውን በሚዲያው ሲገነባላቸው የቆዩት ጠቅላይ ሚኒስተር በድንገት የህይወታቸውን ህልፈት ህዝቡ ሲሰማ  ድንጋጤና ሀዘን ፈጠሮበታል፡፡ይህንንም የህዝብ  ሀዘን በሁለት አቅጣጫ ልናየው እንችላለን፡፡ የመጀመሪያው አስከሬናቸው ከውጭ ሀገር በገባበት ምሽት ከተጠበቀው በላይ ህዝብ ወጥቶ ብሶቱን እና ሀዘኑን ገልጿል፡፡ ምናልባትም ህዝብ ላሳየው የሐዘን ጎርፍ አንድ ወሳኝ የሆነ ነገር መገንዘብ የምንችለው ህዝቡ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ፓርቲው ከሚያራምደው የጎሳና የነገድ ፖለቲካ ውጪ እንደአንድ ኢትዮጵያዊና እንደግለሰብ አይቶ እንዳዘነላቸው መረዳት አያስቸግርም፡፡ በተጨማሪም  እሳቸው በህይወት እያሉ ለያይተው ያዩት ህዝብ ሲሞቱ ግን እርስ በርስ ሳይለያይ በህይወት እያሉ ያላያያዙትን ህዝብ በሞታቸው ሊያያይዙት ችለዋል፡፡

በሁለተኛ ደረጃ እየተመለከትን ያለነው የህዝቡን ስሜት ለፖለቲካ ግብአታቸው ለመጠቀም ስትራቴጂ ነደፈው ፣ በተደራጀ መልኩ እንቅሰቃሴ ውስጥ መግባታቸውን ነው፡፡ ከዚህም አኳያ መንግስት ሊያደርግ የሚፈልገው አቶ መለስ ኖረም አልኖረም ህዝቡ የስርዐቱን መቀጠል እንደፈለገና ተቀባይነትም እንዲኖረው ማድረግ ነው፡፡ ይህንንም ለመተግበር በብሔራዊ የቀብር ስነ ስርዓት አስፈጻሚ ኮሚቴ ስም የህዝቡን ስሜት ወደፈለጉት አቅጣጫ ተቆጣጥሮ ለማዞር የሚያስችል ኮሚቴ ተቋቋሞ በስራ ላይ እያየነው ነው ፡፡ በመሆኑም መልስ አዘል ጥያቄ በማቅረብ ህዝቡ እንዲናገር በማደረግ ፣ በየሰፈሩ ድንኳን በመትከል ፣ በካዴሬዎች አማካኝነት በየመስሪያ ቤቱ መመሪያ በመስጠት ወዘተ… የህዝቡን ስሜት ለፖለቲካ ግብዐት እየተጠቀሙበት ይገኛል፡፡ለማጠቃለልም ብዙ ሀዘንተኞች የተጀመረው ፕሮጀክት ከፍጽሜ  እንዲደርስ በርግጥ ቢጠይቁ የመንግስት ኮሚቴ እንደተመኘው  የኢህአዴግን ስርዓት ቅጥያ ሲጠይቁ አልተደመጡም ፡፡ ምን አልባትም ህዝቡ በፕሮጀክት እና በስርዐት መካከል ያለውን ልዩነት የተረዳ ይመስላል፡፡

የስልጣን ሽግግር

የደህረ መለስ መንግስት ምን አይነት የፖለቲካ መንገድ እንደሚይዝ ከመተንተናችን በፊት  ወደኃላ መለስ ብለን ከቅርብ ታሪካችን እና ከፖለቲካ አንጻር ጥቂት በእንበል፡፡



ሀ. ከታሪክ ማህደር

ዶ/ር ሌቪንን “Wax and Gold” በተሰኘው መጽሐፍ ገጽ 152 ላይ  እንዲህ ይላል፡፡

“Successors to the throne were not determined according to fixed rule like primogeniture. Membership in the Solomonian line was normally a prerequisite……Usually however there were several legitimate candidates for the position and the absence of fixed procedures for choosing among the meant that the death of an emperor was often a time of confusion and political improvisation.” 

“የመንበሩ ወራሾች በተደነገገ ቋሚ መመሪያ አልነበረም የሚወሰኑት፡፡ በሰለሞናዊ ስርወ መንግስት መስመር ውስጥ አባል መሆን በጥቅሉ እንደቅድመ ሁኔታ የተቀመጠ ነው… በተለምዶ፣ ምንም እንኳን ቦታውን የሚመጥኑ ብዙ ሕጋዊ(ሰለሞናዊ) እጩዎች ቢኖሩም፣ አንዱን ለመምረጥ የሚያስችል ውሱን መስፈርት ባለመኖሩ የንጉሠነገሥት ሞት ሁልጊዜም ውዥንብር እና ፖለቲካዊ ፈጠራን/ውሳኔን ይጠይቃል፡፡” (ትርጉም የዞን ዘጠኝ)



በኢትዮጵያ የቅርብ ጊዜ ታሪክ ሰላማዊና ሕጋዊ የሆነ የስልጣን ሽግግር በአብዛኛው ተካሄዶ አያውቅም፡፡ እንደ ዕውቁ ሶሾሎጂስት አገላለጽ ይህም የሆነበት ምክንያት

  •   አንደኛ የስልጣን ሽግግር ህጉ በደንብ አለመቀመጡ
  •  ሁለተኛ ስልጣን ለመያዝ (ዘውድ ለመጫን)  የሰለሞናዊ ስርወ-መንግስት የግዴታ ተወላጅ  መሆንና
  •   በአንድ ጊዜ  ከሰለሞናዊው ስርወ መንግስት ተወላጅ የሚሆኑ ብዙ ተወዳዳሪዎች ለቦታው ብቁ ሆነው መገኘታቸው፤



በመሆኑም ወደ ኢህአዴግ ዘወር በምንልበት ጊዜ ከላይ የጠቀስናቸው ታሪካዊ ክፍተቶች ዛሬም እንደትላንቱ ኢህአዴግም የዘረጋው ስርዓት አልተሻገራቸውም፡፡ ይህንንም ስንል  በሕገ መንግስቱ ላይ በግልጽ የሰፈረ   ቋሚ የስልጣን ሽግግር ህግ የለም፡፡ በተጨማሪም ትላንት ዘውድ ለመጫን የሰለሞናዊው የዘር ሀረግ አስፈላጊ እንደነበረው አሁን ደግሞ ስልጣን ለመጨበጥ የኢህአዴግ አመራር መሆን የግድ ነው፡፡በመሆኑም ለሰለሞናዊው የሽግግር ጥያቄም ሆነ ለአሁኑ ጊዜ በርካታ ተቀራራቢ ዕጩዎች ወይም ተወዳዳሪዎች መኖራቸው ሽግግሩን ውስብስብ እና አስቸጋሪ አድርጎታል፡፡

ለ. ከፓለቲካ ዳራ


አሁን ለተነሳው የሽግግር ጥያቄ መልስ ለማግኘት የጠቅላይ  ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ አመራር ምን አይነት  መልክ የያዘ ነበር የሚለውን ማወቅ ይገባናል፤ምክንያቱም በየትኛውም የዓለማችን ክፍል እንደሚታየው የስርዓቱ ዲሞክራሲያዊ ወይንም ኢ-ዲሞክራሲያዊ መሆን  በስልጣን ሽግግሩም ላይ ወሳኝ ሚና ይጫወታል፡፡ ምንአልባት ይህንን ዐሳብ የበለጠ ለማብራራት የሀኛያው ክፍለ ዘመን የፓለቲካ ፍልስፍና መምህርት ከነበረችው ሐና አረንት  (Hanna Arendt) ትንሸ እንውሰድ፡፡

እንደ ሐና አረንት አመላካከት የዴሞክራሲያዊ ስርዓት አገዛዝ የ’ስልጣን መርህ’(authority principle) ሲከተል  ኢ-ዲሞክራሲያዊ አገዛዝ በአንጻሩ ደግሞ በ’መሪ መርህ’ (leadership principle) ይተዳደራል፡፡ በ’ስልጣን መርሕ’ የስልጣን ተዋረዱና ክፍፍሉ  በሀገሪቱ ህግ በዝርዘርና በግልጽ ተለይቶ ይቀመጣል፡፡በሌላ በኩል በ’መሪ መርሕ’  የሚታዳደሩ ሀገሮች ግን ይህን በተመለከተ የስልጣን ተዋረድ የላቸውም፡፡ ስልጣኑ ተጠቃሎ በመሪው እጅ ይገኛል፡፡ከመሪው ቀጥሎ ሁለተኛ የሚባል ለይስሙላ ይቀመጣል እንጂ መሪው አንድ ነገር ቢሆን በሁለተኛ ደረጃ የተሰየመው ሰው ይተካዋል ማለት አይደለም ፡፡ ለማጠቃለል የሀና አረንት አቀራረብ የሚያስተምረን ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ማለት ከ’መሪ መርህ’ ወደ ‘ስልጣን መርህ’ መሸጋገር  ማለት ነው ፡፡ በኢትዮጵያ ሀገ መንግስታዊ ሰርዓት ሲዘረጋ ይህ ታስቦ ቢሆንም የዲሞክሪያሲያችን ጨቅላነት የመሪዉን ጫንቃ መሸከም ስላቀታት ዴሞክራሲው በአጭሩ ተቀጭቶ በ’መሪ መርህ’ ለመመራት በቅተናል፡፡



ድኅረ መለስ ዜናዊ ኢትዮጵያ (Post; Capital ‘P’ or Small ‘p’)

የእንግሊዘኛውን ‘post’ የሚለውን ቃል ለሁለት ከፍለን ብንመለከተው ለትንተናችን አመች ይሆናል፡፡  ካፒታል ‘ፒ’ እና ስሞል ‘ፒ’ ብለን እንከፍለዋለን፡፡ ካፒታል ‘ፒ’ ተጠቅመን ድህረ(Post) ስንል consequential  መሰረታዊ የለውጥ ሂደቶችን  የካተተ ማለት ሲሆን ባንጸሩ ስሞል ‘ፒ’  ስንጠቀም ደግሞ መሰረታዊ ያልሆነና ፋይዳ ያለው ለውጥና ሽግግር የማይታይበት ሆኖ እናገኛዋለን፡፡  ለምሳሌ በአረብ ሀገራት በቅርቡ የተነሳው አብዮት  መሰረታዊ የስርዓት ለውጥ ስላስከተለ ካፒታል ‘ፒ’   ነው፡፡በሌላ በኩል  ከአንዋር ሳዳት ወደ  ሙባረክ  የነበረው ሽግግር ግን ምንም የስርዓት ለውጥ ስላልታየበት  ስሞል ‘ፒ’  ነው ፡፡


ከሁሉ አስቀድሞ ከላይ በትንሹ ልንጠቅሰው እንዳሰብነው አሁን አመራር ላይ ያሉት ባለስልጣናት የድህረ መለስን ስርዓት እንዳለ እንዲቀጥል እና ሽግግሩም ስሞል ፒ’  እንዲሆን ይፈልጋሉ፡፡ለዚህም ነው አስቀድመው “የፓርላማ አባላቱን በአስቸኳይ ሰብስበን አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝን ከጊዜያዊ ጠቅላይ ሚኒስቴርነት  ወደ ቋሚ ጠቅላይ ሚኒስቴርነት እንለውጣለን” የሚል ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡት፡፡

መንግስት እንዳሰበው የስርዓቱ ሕልውና በምንም መልኩ ጥያቄ ውስጥ የገባ እንዳልሆነ በየጊዜው የሚነግረን ቢሆንም ብዙ የአደጋ ቀጠናዎች እንዳሉ ግን እየተገነዘብን ከላይ ወደ አነሳነው  ወደ  አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ መመረጥ ፖለቲካ አንድምታ ላይ እንመለስ፡፡

ከአቶ ኃይለ ማርያም ምርጫ ዙሪያ ሁለት ጥያቄዎች ማንሳት እንችላለን፡፡ አንደኛ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ የኢህአዴግ መሪዎች ‘የስልጣናችን ምንጭ (legitimacy) የሚፈልቀው  በትጥቅ ትግሉ ውስጥ በከፈልነው መስዋዕትነትን’  ሲሉ ቆይተው በዚህ ጎዳና ያላለፈ ሰው መምረጣቸው ፤ ሁለተኛ  ደግሞ ሌሎች አንጋፋ ፓርቲዎች እያሉ ኢህአዴግ አዲስ አበባን ከተቆጣጠረ በኃላ የተመሰረተ ፓርቲ አባል መሆናቸው ስለሳቸው ሳይሆን በግንባሩ የፖለቲካ ህይወት  ወሳኝ  ሚናን ስለሚጫወቱት አካሎች የሚነግረን ነገር አለ፡፡


ይህንን ለመረዳት ከሁለት ዓመት በፊት ከኢህአዴግ ከፍተኛ አመራር መካከል አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ እንዴት የምክትል ጠቅላይ ሚኒስቴርነትን ሹመት እንዳገኙ ማስታወስ ይገባናል፡፡ በዚህ ወቅት ፓርቲው  በመተካካት ጥያቄ እና በጠቅላይ ሚኒስቴሩ ጤና መቃወስ ምክንያት ተወጥሮ ነበር፡፡በዚህም ጊዜ በጣም የሚያስገርመውና የሚያስደምመው የህወሓት ልሂቃን ሁለት አማራጭ ይዘው ቀረቡ፡፡አንደኛ በአገሪቱ ላይ ዴሞክራሲ እንዳይቀጭጭ ከተፈለገ እና እኛ የምንወክለው የሕዝብ ቁጥር አነስተኛ ስለሆነ የጠቅላይ ሚኒስቴሩን ቦታ  ከብአዴን እና ኦህዴድ ብንመርጥ የግንባራችንን የሀይል ሚዛን ሲለሚያዛባው  በኛ በኩል ተቀባይነት የለውም የሚል ዐሳብ አቀረቡ፡፡ሁለተኛ የጠቅላይ ሚኒስቴሩን ጽ/ቤት ለሶስት ወይንም ለሁለት በመክፈል የስልጣን ክምችቱን( premiership ) ብናሰራጨው የተሻለ ይሆናል አሉ፡፡በመሆኑም የመጀመሪያው ዐሳብ በግንባሩ ተቀባይነት በማግኘቱ ከሁለቱ ብዙኃን ፖርቲ ውጪ የሆነ ሰው በምክትል ጠቅላይ ሚኒስቴርነት ለመምረጥ በቅተዋል፡፡  ሁለተኛው አማራጭ ደግሞ ሀገሪቱን ለሌሎች ስጋቶች ስለሚያጋልጣት ተቀባይነት አላገኘም፡፡

አሁን ለጊዜው የሀገሪቱ የፖለቲካ አቅጣጫ ወይም የሽግግር ሁኔታ ካፒታል ‘ፒ’ ወይንም ስሞል ‘ፒ’ ይሆናል ለማለት አስቸጋሪ ቢሆንም በዚህ ጉዳይ ላይ ተጽእኖ የሚፈጥሩ አራት ዐበይት  ወቅታዊ ጉዳዮች አሉ፡፡

  1. የአቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የፖለቲካ ደረጃ አጠያያቂነት በራሳቸው አመራር እንዳይሄዱ ሰርዓቱ የማይፈቅድላቸው በመሆኑ
  2. የኦሮሚያ ክልል ፕሬዘዳንት አቶ አለማየሁ አቶምሳ ቦታ በህመም ምክንያት ክፍተት በመፍጠሩ እና ከዚህም ጋር ተያይዞ የሚነሳው ውዝግብ
  3. በኢትዮጵያ ሙስሊሞች እና በመንግስት መካከል የተነሳው ውዝግብ እልባት አለማግኘት
  4. የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ህልፈት ተከትሎ ቀጣዩን ፓትርያርክ የመምረጥ ሂደት 


መደምደሚያ

እንደሚታወቀው ኢህአዴግን የሚያዋቅሩት የፖለቲካ ድርጅቶች ሁሉም እኩል  ናቸው ቢባልም በኦርዌሊያን (George Orwell) አነጋገር “ሁሉም ፓርቲዎች እኩል ናቸው አንዳንድ ፓርቲዎች ግን የበለጠ እኩል ናቸው” እንዳለው ልክ ከጠቅላይ ሚኒሰቴር ጽ/ቤት ባለነሰ የህወሓት ሊቀመንበር ቦታ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ህይወት ላይ ወሳኝ ሚና እንደሚኖረው አጠያያቂ አይደለም፡፡ ይሄ ፓርቲ የበላይነት እና የገዢ ስፍራውን ለረጅም ጊዜ ማስቀጠል ይፈልጋል፡፡ ይሄንን ለመተግበር አሁን ለማደረግ እንደተፈለገው  ከሌላ (ማለትም ብዙኃን ቁጥር ከሌለው)ፓርቲ በመሾም አሊያም ከራሱ ፓርቲ ሰው መልምሎ በማቅረብ በምንም መልኩ የስልጣን ባለቤትነቱን ለማረጋገጥ ይፈልጋል፡፡


1 comment:

  1. In order to determine whether or not we are on the verge of a Post-Meles era, I think we should first be clear about the defining term itself: Meles. We indeed need to presume, at least provisionally, as to what Meles was an embodiment of a
    nd take him then as a concept rather than a person (so as to speak of “a Meles”—and this in no way to belittle him but for the sake of analysis). For instance if we were to accept him as the incarnation of “lemata” (development), envisioning a Post-Meles era would amount to wishing “tefata” (destruction) of the country. On the other hand if we conceive of him as the incarnation of “beherata” (ethno-nationality), to imagine a Post-Meles era would mean to predict the restoration of Ethiopia and Ethiopianity…

    Dr. Dagnachew: How about the role of the Opposition? It sounds, perhaps against your will, as if you want to just ignore them! And ignorance is… So please keep them in mind whenever you analyze issues of national significance such as this.

    ReplyDelete