Saturday, October 15, 2016

ሰ.መ.ጉ. 25ኛ ዓመቱን እያከበረ ነው፤ የዜጎች ድጋፍ ያስፈልገዋል!

(በፍቃዱ ዘ. ኃይሉ)

በአገራችን ብቸኛው ሰብኣዊ መብት ላይ አተኩሮ የሚሠራው መንግሥታዊ ያልሆነ የሰብኣዊ መብቶች ጉባኤ (ሰ.መ.ጉ.) ከተመሠረተ 25 ዓመታት ሞሉት፡፡ ቀድሞ የኢትዮጵያ ይባል የነበረው ኢ.ሰ.መ.ጉ. በበጀት እጦት ምክንያት በ3 ክልሎች ብቻ ጽሕፈት ቤቶች ስለነበሩት ሰ.መ.ጉ. ለመባል ተገዶ ከርሟል፡፡ ይሁን እንጂ በቅርቡ ለማገገም እያደረገ ባለው ጥረት የጽሕፈት ቤቶቹን ቁጥር 6 አድርሶ የቀድሞ ሥሙን ለማስመለስ እና ሥራውንም በአገሪቱ ክልሎች በሙሉ ለማድረስ እየሞከረ ነው፡፡ የተቋሙ ዋና ዳይሬክተር አቶ ብፅአት ተረፈ ዛሬ (ቅዳሜ፣ ጥቅምት 5፣ 2009) ከወጣው አዲስ አድማስ ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ እንደገለጹት፣ ‹በተለይ ከምርጫ 97 ጋር በተያያዘ በርካታ ባለሙያዎቻቸውና መረጃዎቻቸው ልክ ሕገ መንግሥቱን በኃይል ለመናድ የተንቀሳቀሱ በማስመሰል በመነገሩ፣ ተቋሙን ጥለው እንዲሰደዱ በማድረግ ተዳክመው ቆይተዋል፡፡ ሌላው በ2001 የወጣው የበጎ አድራጎት ድርጅቶች አዋጅ ተፅዕኖ አሳርፎባቸዋል፡፡ በተለይ በጀት ከውጭ አለማግኘታቸው ጽ/ቤቶቻቸውን እንዲዘጉና በርካታ ሠራተኞቻቸውን እንዲቀንሱ አድርጓቸዋል፡፡›


ሰ.መ.ጉ. አሁን መልሶ አቅም በመገንባት ላይ ሲሆን፣ አገሪቱ አሁን ካለችበት ወቅታዊ ፈተና አንፃር፣ ይህ አገር በቀል ተቋም የሰብኣዊ መብት ጥሰቶችን በመመዝገብ፣ ይፋ በማድረግም ይሁን እንዲከበሩ ውትወታ በማድረግ የተቻለውን ሁሉ እንዲያደርግ የዜጎችን የገንዘብ፣ የዕውቀት እና የመረጃ ድጋፍ ከመቼውም ጊዜ በላይ ይፈልጋል፡፡ ሰ.መ.ጉ. ባለፈው እሁድ (መስከረም 29፣ 2009) በአዲስ አበባ ይህንኑ አስመልክቶ ‹የእግር መንገድ ጉዞ› ለማድረግ አቅዶ የነበረ ቢሆንም ከአዲስ አበባ መስተዳደር ይሁንታ ሊያገኝ አልቻለም፡፡

ዋና ዳይሬክተሩ በአሁኑ ወቅት ያለውን የሰብኣዊ መብቶች ጥሰቶች መመዝገብን አስመልክተው በተጠቀሰው ቃለ ምልልሳቸው ሲናገሩ፣ “ከዚህ በፊት በኦሮሚያ ተቃውሞ ምክንያት የደረሰውን የሰብኣዊ መብት ጥሰት ከ340 ወረዳዎች 33 ወረዳዎችን መርጠን የመጀመሪያ ዙር ሪፖርት አውጥተናል፡፡ ቀጥሎም በሁለተኛ ዙር 24 ወረዳዎችን አጣርተን ሪፖርት አድርገናል፡፡ በአማራ ክልል ከወልቃይት ጋር በተያያዘ በጎንደር፣ ደብረ ታቦር፣ ደብረ ማርቆስ፣ ባሕር ዳር እና በሌሎች ቦታዎች ላይ ማጣራት አድርገናል፡፡ ችግሩ እነዚህን ሪፖርቶች እያቀናጀን ሳለ ኮንሶ ችግር ተፈጠረ፤ የኮንሶን ስናጣራ የኢሬቻ ችግር መጣ፣ የኢሬቻ ስንል የጌድኦ መጣ፡፡ በጣም ተቸግረናል፤ ከአቅማችን በላይ ሆኗል” ብለዋል፡፡

ሰ.መ.ጉ. ባለፉት 25 ዓመታት 36 መደበኛና እና 141 ልዩ የሰብኣዊ መብት ጥሰት መግለጫዎችን አውጥቷል፡፡

በዚህ ወሳኝ ጊዜ ሰ.መ.ጉ. ሥራውን አጠናክሮ ለመቀጠል ይችል ዘንድ “ሁሉም ሰብኣዊ መብቶች ለሁሉም” በሚል መሪ ቃል የገቢ ማሰባሰቢያ ዘመቻ እያደረገ ይገኛል፡፡ ለገቢ ማሰባሰቢያ እንደ አማራጭ የቀረቡት፣ መኪና ላይ እና ሌሎች ቁሳቁሶች ላይ የሚለጠፉ ስቲከሮችን (በ10 ብር)፣ ቲ-ሸርቶች (በ150 ብር) እና ጥቅምት 13፣ 2009 በደሳለኝ ሆቴል የሚዘጋጅ የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት (ባለ 500፣ 1,000 እና 1,500 ብር የምሳ ኩፖኖች) ናቸው፡፡

ከነዚህ አማራጮች ውጪ በገንዘብ መርዳት ለሚፈልጉም፣ በሚከተለው የተቋሙ የባንክ አካውንት ማስተላለፍ ይችላሉ፡

ዘመን ባንክ
(አዲስ አበባ ዋና ቅርንጫፍ)
አካውንት ቁጥር፣ 1032410005964026


ወይም 
ሰ.መ.ጉ.ን በተለየ መንገድ መርዳት የሚፈልጉ:
በስልክ ቁጥር +251115517704 ወይም +251115514489 በመደወል፣ 
ወይም
info1hrco@gmail.com ላይ ኢሜይል በማድረግ፣ 
ወይም 
ድረገጻቸውን www.ehrco.org ን በመጎብኘት ልያገኟቸው እንደሚችሉ ገልጸዋል፡፡ 


የሰመጉ አርማ

ሰመጉ ያዘጋጃቸው የመግቢያ ትኬቶች

የሰመጉ ስያሜና አርማ ያለባቸው ቲሸርቶች

No comments:

Post a Comment