Wednesday, July 4, 2012

GTP የት አደረሰን?

በናትናኤል ፈለቀ

የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ የሁለተኛው የ5 ዓመት የልማት ስልታዊ እቅድ (Plan for Accelerated Development to End Poverty, PASDEP) ጊዜ ገደብ መገባደዱን ተከትሎ በፈረንጆቹ አቆጣጠር በኖቬንበር ወር 2010 ዓም የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትን ይሁንታ ካገኘ በኋላ ነበር የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክሪያሲያዊ ሪፐብሊክ መንግስት ሦስተኛ የ5 ዓመት ስልታዊ ዕቅድ ሆኖ መተግበር የጀመረው:: የትግበራው ዋነኛ ግብ የተጀመረው በሁለተኛው የ5 ዓመት የልማት ስልታዊ ዕቅድ አተገባበር ላይ ለተከታታይ ዓመታት ኢኮኖሚው ያስመዘገበውን ፈጣን ባለሁለት አሃዝ እድገት በማስቀጠል የኢንደስትሪው ዘርፍ የኢኮኖሚውን መሪነት ሚና ከግብርና የሚረከብበትን ቅድመ ሁኔታ ማመቻቸት  ነበር::

ይህ ዕቅድ ይፋ ከሆነበት ጊዜ አንስቶ ከየአቅጣጫው የተቃውሞ ትችቶችን ለማስተናገድ ተገዷል:: ዕቅዱ ላይ የሚቀርቡት ትችቶች በዋነኛነት የሚያጠነጥኑት በሁለት አንኳር ጉዳዮች ላይ የነበረ ሲሆን የመጀመሪያው የትችቶች ማጠንጠኛ የመንግስትን ቅጥ ያጣ ጉጉነት የተመለከተ ሲሆን መደገፊያ መከራከሪያውም ዕቅዱ ውስጥ እንደሚተገበሩ የታቀዱትን ተግባራትን ለመከወን የሚያስፈልገውን ያህል ገንዘብ ለማግኘት እንደሚያስቸግርና ዕቅዱ የመንግስትን የመፈፀም አቅም በእጅጉ አጋኖ ያቀረበ ነው የሚል ነበር፡፡ ሁለተኛው ትችት ሆኖ የቀረበው ደግሞ የዕቅዱ አተገባበር ከፍተኛ የሆነ የመንግስት ወጪ ስለሚፈልግ ቀድሞውንም ቢሆን ለቁጥጥር ላስቸገረው ምጥቀ ግዥበት (Hyper Inflation) በዕንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ይሆናል ከሚለው ፍራቻ ነበር፡፡

የአንድ አመት አፈፃፀም ሪፖርቱ ይፋ ሲሆን ሁለቱም ትችቶች ተገቢ እንደነበሩ አስተጋብቷል፡፡  መጀመሪያውንም ቢሆን ለመተግበር የገንዘብ እጥረት ያጋጥመዋል የተባለለት ዕቅድ በአውሮፓ ሀገራት የተፈጠረው የምጣኔ-ሃብት ቀውስ ባስከተለው የፍላጎት መቀዛቀዝ ምክንያት ከውጭ ንግድ የምናገኘው ገቢ ላይ ቀጥተኛ የሆነ ተፅዕኖ ያሳደረ ሲሆን በተያያዥነትም መንግስት ከአውሮፓ አጋሮቼ አገኘዋለሁ ብሎ ያሰበውን ብድር በቀላሉ እንዳያገኝ እንቅፋት ሆኗል፡፡ ሌላው የገንዘብ ምንጭ የሆነው የአገር ውስጥ ተቀማጭም ቢሆን እ.አ.አ በ2010 አገሪቷ ውስጥ ባሉት የንግድ ባንኮች ከተሰበሰበው አጠቃላይ ተቀማጭ የ42.5 በመቶ አመርቂ የሚባል እድገት ቢያሳይም የዓለም ባንክ የኢትዮጵያ ዲያሬክተር ጉያንግ ዚሄ ቼን እንደሚሉት ከሆነ ከአጠቃላይ ያገሪቷ ዓመታዊ ምርት (GDP) ጋር ሲነፃፀር ግን ከ5 በመቶ አካባቢ ከፍ አላደረገውም (መንግስት ይህንን ቁጥር 8.8 በመቶ ደርሷል ይላል)፡፡

ይህንንም የገንዘብ እጥረት ለመሙላት መንግስት ሊወስዳቸው ካሰባቸው እርምጃዎች አንዱ የሆነው የፕሮጀክቶችን ጥራት በመቀነስ የሚፈጁትን ወጪ የመቀነስ ስልት ሌላ ትችት ለመጋበዝ ቅርብ ነው፡፡ሌላኛው አማራጭ ቀጥተኛ የሆነ የውጭ መዋዕለ ነዋይ ፍሰት (FDI) ሲሆን ይህኛውም አማራጭ ከትችቶች የፀዳ አይደለም፡፡ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ መንግስት በስፋት እየሰራበት ያለው ሰፋፊ የእርሻ መሬት ከኢሲያ ለሚመጡ ባለሃብቶች የማከፋፈል ሂደት ዘላቂ እና የአካባቢው ነዋሪዎችን ማዕከል ያደረገ ልማት የማምጣት አቅሙ እና የባለሃብቶቹ ፍላጎት በጥርጣሬ ነው የሚታዩት፡፡ ከዚህም አልፎ እርምጃው የመሬት ወረራ (Land Grab) ነው እና ነዋሪዎችን አላግባብና ያለበቂ ካሳ ያፈናቅላል የሚሉት ክሶች ከየቦታው እየበረቱ ነው፡፡

የዋጋ ግዥበትንም በተመለከተ ለመንግስት የሚያኮራ ውጤት አልተገኘም፡፡ የዋጋ ግዥበቱ ማሻቀብ ከጀመረበት ከ6 ዓመታት ወዲህ ከፍተኛ ተብለው ከተመዘገቡት የዋጋ ግሽበት መጠኖች አንዱ (40.6 በመቶ) የተመዘገበው ዕቅዱ መተግበር ከተጀመረ በኋላ ባለው ነሐሴ ወር ነበር፡፡ የዋጋ ግሽበቱን በዋነኛነት የሚመራው የእህል (ምግብ ነክ) ዋጋ መሆኑ ደግሞ ትልቁ በትር ያረፈው ከእጅ ወደ አፍ የሚኖረው ደሃ ላይ መሆኑን ይነግረናል፡፡

[caption id="attachment_154" align="alignnone" width="466"] ምንጭ፤ የኢኮኖሚስት ኢንተለጀንስ ዩኒት የ2012 ሀገራዊ ሪፖርት[/caption]

እንደ ዓለም አቀፍ ተቋማት ትንበያ ከሆነ በሂደት የመቀነስ አዝማሚያ እያሳየ ያለው የዋጋ ግሽበት ወደ አንድ አሃዝ የሚወርድበት ጊዜ ከ2005 የኢትዮጵያ በጀት ዓመት ሦስተኛ ሩብ አመት ቀድሞ እንደማይሆን እየገለፁ ሲሆን መንግስት በበኩሉ በመጀመሪያው እና በሁለተኛው ሩብ ዓመት የሽግግር ወቅት የዋጋ ግሽበቱ ባለ አንድ አሃዝ እንደሚሆን እየሞገተ ነው፡፡

ትራንስፎርሜሽኑስ ምን ደረሰ? 

የሀገሪቷን ኢኮኖሚ ኋላ ቀር ከሆነው ግብርና ላይ ያለውን ጥገኝነት ወደ ኢንደስትሪው ዘርፍ ለማሸጋገር የሚደረገው ጥረት ከታቀደለት ፍጥነት በላይ (በ15 በመቶ) እያደገ ቢሆንም ኢኮኖሚውን ከግብርናው ተቀብሎ ለመምራት ግን ገና ብዙ ርቀት ይቀረዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት ሀገራችን በዕቅዱ የመጀመሪያ ዓመት አስመዘገበችው እያለ ያለውን የ11.4 በመቶ እድገት በፊት አውራሪነት የሚመራው የኢንደስትሪው የኢኮኖሚ ዘርፍ ከአጠቃላይ የሀገሪቱ ዓመታዊ ምርት ጋር ሲነፃፀር ያለው ድርሻ ግን እጅግ አነስተኛ ነው (13.4 በመቶ)፡፡

ማሕበራዊ ዘርፎችስ?

ዕቅዱ መተግበር ከተጀመረ ወዲህ የከተማ ሥራ አጥነት ከነበረበት 18.9 በመቶ ወደ 18 በመቶ የወረደ ሲሆን ይህም በከተሞች አካባቢ እየተካሄደ የሚገኘው ሰፊ የግንባታ ሥራ ውጤት ነው፡፡ መንግስት እንደሚለው ከሆነ ደግሞ የሥራ አጥ ቁጥር መቀነሱ በየከተሞቹ ለወጣቶች እያደረገው ያለው ልዩ ልዩ የማደራጀት እና የገንዘብ ድጋፎችን ተከትሎ የመጣ ውጤት ነው፡፡

የነፍስ ወከፍ ዓመታዊ ገቢ ወደ 392 የአሜሪካን ዶላር ማደግን ተከትሎ የፍፁም ድህነት መለኪያም እ.አ.አ 2004/5 ከነበረበት 38.7 በመቶ ወደ 29.6 በመቶ ወርዷል፡፡ ይህም ማለት ከአጠቃላይ የሀገሪቷ ዜጎች ውስጥ 29.6 በመቶ የሚሆኑት አሁንም በፍፁም ድህነት አረንቋ ውስጥ ይገኛሉ ማለት ነው፤ ለዛውም ቁጥሩን ያለጥያቄ ለማመን ከመረጥን፡፡

[caption id="attachment_155" align="alignnone" width="471"] ምንጭ፤ የGTP አመታዊ ሪፖርት                            (a) - Actual[/caption]

ዕቅዱ መተግበር በተጀመረበት ዓመት በአጠቃላይ 20 ሚሊየን የሚጠጉ ዜጎች ትምህርት ቤት ገብተው መማር የቻሉ ሲሆን ከነዚህም መካከል 43.5 በመቶው ሴቶች ናቸው፡፡ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ያልተጣራ ሽፋን 96.4 በመቶ የደረሰ ሲሆን የሁለተኛ ደረጃ የመጀመሪያ ዑደት ሽፋን (9-10) 41.6 በመቶ ያደገ ሲሆን  በሁለተኛ ዑደት (11-12) የሴቶች ተሳትፎ ወደ 42.2 በመቶ ከፍ ብሏል፡፡ የመንግስት ዩንቨርሲቲዎችንም ቁጥር 32 ለማድረስ ጥረት የተደረገ ሲሆን የመጀመሪያ ዲግሪ ተማሪዎችን የመቀበል አቅም ወደ 75,348 የሁለተኛ ዲግሪና ከዛ በላይ የሚማሩ ተማሪዎችን የመቀበል አቅም ደግሞ ወደ 6,300 አድጓል፡፡ ሪፖርቱ ስለ ትምህርት ጥራት ያለው ነገር የለም፡፡

በጤና ረገድ የገጠር ኤክስቴንሽን ጤና ባለሙያዎች ቁጥር 34,382 የደረሰ ሲሆን ከወሊድ ጋር በተያያዘ ህመም ምክንያት ህይወታቸውን የሚያጡ እናቶች ቁጥር (Maternal Mortality Rate) ከአንድ ሺህ (እርጉዝ/የወለዱ) እናቶች መካከል 470 ደርሷል፡፡ እንደተወለዱ የሚሞቱ ህፃናት (Infant Mortality Rate) ቁጥርንም ከአንድ ሺህ አዲስ የተወለዱ ህፃናት መካከል 59 ሞት ደርሷል፡፡

በጤና እና በተለይ ደግሞ በትምህርት ማዳረስ ላይ የተገኙት ውጤቶች እ.አ.አ ለ2015 በዘርፉ የታቀዱትን የምዕተ ዓመቱ የልማት ግቦችን (MDG) ኢትዮጵያ ልታሳካ እንደምትችል አመላካች ናቸው፡፡

የቁጥር ጨዋታ?

የኢትዮጵያ መንግስት ፈፀምኩ ብሎ የሚዘግባቸውን ክንውኖች በጥርጣሬ የሚመለከቱት ወገኖች ጥቂት አይደሉም፡፡ ለኢትዮጵያ መንግስት የብድርና የእርዳታ እጃቸውን የሚዘረጉትን ትልልቅ ድርጅቶች ጨምሮ አማራጭ የመረጃ ምንጭ ያላቸው ዜጎች መንግስት ሆን ብሎ በቁጥር ጨዋታ ያስመዘገባቸውን ክንውኖች የማጋነን አባዜ እንዳለበት በመጥቀስ የመንግስትን ሪፖርት የጎሪጥ ነው የሚያዩት፡፡

[caption id="attachment_156" align="alignnone" width="473"] የኢትዮጲያ መንግስት እና የኢኮኖሚስት ኢንተለጀንስ ዩኒት የሚቀጥሉት ስድስት ዓመታት የኪኮኖሚ እድገት ትንበያ መካከል ያለው ልዩነት[/caption]

1 comment: