Sunday, July 1, 2012

ጋዜጣና መጽሔቶቻችን ከሰኞ እስከ ሰኞ - አራት

(ከሰኔ 18፤ 2004 እስከ ሰኔ 24፤ 2004)

‹‹የኢሕአዴግ የስለላና የቁጥጥር መዋቅር ከ1 ለ 5 ወደ 1 ለ 11 አደገ›› የሚል ዜና ይዞ የወጣው ፍኖተ ነፃነት ነው፡፡ በዝርዝሩም ‹‹… ታማኝ ውስጥ አዋቂዎች እንደሚሉት ‹በቅርቡ ፖሊሶች፣ የመንደር ካድሬዎችና ደህንነቶችን የከተማውን ነዋሪ ቅጽ እያስሞሉ ናቸው፡፡ ከዚያም 1 ለ 11 በማደራጀት እያንዳንዱን የከተማ ነዋለሪ ለመቆጣጠር ታቅዷል፡፡›…››

* * *


ዕንቁ መጽሔት በለጠ ደምሴ ከተባለ ከፊል ከተሜ፣ ከፊል ገጠሬ ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ ስለራሱ እና ስለሚኖርበት ማሕበረሰብ ሥራ የማይሰራቸው በዓላት ሲናገር ‹‹…በ5 አቦን፣ በ7 ሥላሴን፣ በ12 ሚካኤልን፣ በ13 እግዚአብሔርአብን፣ በ16 ኪዳነ ምህረትን፣ በ19 ገብርኤልን፣ በ21 ማርያምን፣ በ23 ጊዮርጊስን፣ በ24 ተክለሃይማኖትን፣ በ27 መድኃኔዓለምን፣ በ29 ባለወልድ፣ በ30 ዮሐንስን አንሠራም፡፡…ቅዳሜ እና እሁድም አሉ፡፡ …›› ብሎ አስገራሚ ቃለ ምልልስ አድርጓል፡፡

* * *


ሪፖርተር ጋዜጣ ‹‹የመንግስት አመራሮች ለውጥን የመምራት ክህሎት አለማዳበራቸው ተገለጸ›› ባለበት የረቡዕ እትሙ ‹‹… የሲቪል ሰርቪስ ሚስትር አቶ ጁነዲን ሳዶ የመሥሪያ ቤታቸውን የአሥራ አንድ ወራት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት እንደገለጹት፣ በየደረጃው ያለው የበላይ አመራር … የለውጡ ባለቤትና መሪ እሱ መሆኑን መገንዘቡን ከተለያዩ እንቅስቃሴዎች መገንዘብ ቢቻልም፣ አሁንም ቁርጠኝነትና ለውጥን የመምት ክህሎቶች በተፈለገው ደረጃ አላዳበረም፡፡..›› ሲል ጽፏል፡፡

* * *


‹‹ኢትዮጵያ ከአሥር አደገኛ የአፍሪካ ሀገራት መካከል ተመደበች›› የሚል ዜና ይዞ የወጣው ሰንደቅ ጋዜጣ ነው፡፡ በዝርዝሩም ‹‹… ግሎባል ፒስ ኢንዴክስ …ሪፖርቱ ኢትዮጵያን ከአሥር አደገኛ የአፍሪካ ሀገራት ውስጥ መድቧታል፡፡ ድርጅቱ በጦነት ደመና ውስጥ ያሉ፣ በእርስ በርስ ጦርነት የሚታመሱ እና በተለያዩ አመጾች የሚናጡ አገራትን በዝርዝር ያስቀመጠ ሲሆን፤ ኢትዮጵያን በዚሁ ዝርዝር ውስጥ ለማካተት በምክንያትነት ያስቀመጠው ሰላምም ጦርነትም በማይባል ሁኔታ ውስጥ ያሉትን የኤርትራንና የኢትዮጵያን ሁኔታ በስጋትነት በማስቀመጥ ነው፡፡…›› ሲል አትቷል፡፡

* * *


‹‹የአእምሮ ክስረት፣ ሁሉም ነገር ሽብርተኝነት!›› ባሉት ጽሁፋቸው ፕ/ር መስፍን ወልደማርያም በፍትህ ጋዜጣ ላይ ‹‹… የምታገለው ለኢትዮጵያ ሰላምና ደኅንነት፣ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ነፃነትና እኩልነት፣ ለፍትሐዊ አስተዳደር፣ ለልማትና ለብልጽግና መሆኑ የማይገባቸው እስቲገባቸው ድረስ እንቀጥላለን፤ እነሱ እየተማሩ ወደኛ ይመጣሉ እንጂ እኛ ወደነሱ አንሄድም፡፡…›› ብለው ጽፈዋል፡፡

* * *


‹‹ደም ባለመዘጋጀቱ ቀዶ ህክምና የተቋረጠባት ሕፃን አረፈች›› የሚል ዜና እና የሕፃኗን ምስል ይዞ የወጣው ደግሞ አዲስ አድማስ ነው፡፡ በ‹አክሽን ፕላን ኢትዮጵያ› ስፖንሰር አድራጊነት በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ቀዶ ህክምና እየተደረገላት ሳለ ‹‹…. ከሕፃኗ የፈሰሰውን ደም የሚተካ ደም ሲፈለግ፤ የተገኘው ምላሽ አስደንጋጭ ነው… ደም የለም፡፡ … ግራ ተጋብተው የቆሙት አባት… አቶ ተስፋዬ … ነርሶቹን ስጠይቃቸው፤ ‹የምናውቀው ነገር የለም፤ ሃኪሙ የህፃኗን ጀርባ እንደከፈተ ጥሏት ሄደ› ሲሉ እንደመለሱላቸው… ጠቅሰዋል፡፡ ….›› ሲል ዘግቧል፡፡

* * *


‹‹Staring death in the eyes›› ባለው ዜናው THE Reporter በሕገወጥ መንገድ አገር የሚያቋርጡ ኢትዮጵያውያን ሞት የተለመደ ቢሆንም እንደባለፈው ማክሰኞች ግን ዘግናኝ እንደሌለ ተናግሯል፡፡ ከ100 በላይ ኢትዮጵያውያን ታንዛኒያ ውስጥ ተጥለው ሲገኙ 43 ሞተው፣ 72 ደግሞ ለሕይወት በሚያሰጋ ሁኔታ ውስጥ ሆነው እንደሆነ ዘግቧል፡፡ 11ዱ ብቻ ደግሞ ደህና በሚባል ይዘት ላይ ናቸው፡፡

* * *


ዞን ዘጠኝ አዲስጉዳይ በላከውና በታተመለት ጽሁፉ ላይ የሚኒስቴር ዲኤታ ሽመልስ ከማልን መግለጫ እንዲህ ሲል ገምግሞታል፡፡ ‹‹… ነገር ግን የርሳቸው ማስተባበያ ጊዜያዊ ማስታገሻ ወይስ እውነተኛው የመንግስት ዓላማ ብሎ ለማለት የሚከተሉትን ጉዳዮች መመልከት ያስፈልጋል፡፡ አንደኛ፤ የሚኒስቴሩ ድረገጽ ላይ VoIPን የሚያስተዋውቅበትን ገጽ በሌላ ጽሁፍ መተካቱ ለምን አስፈለገ? ሁለተኛ፤ አቶ ሽመልስ ከማል ከዚህ በፊት ‹‹ቪኦኤን ጃም አላደረግንም›› ብለው ካስተባበሉ በኋላ አቶ መለስ ‹‹አዎ፣ አድርገናል›› ማለታቸው የሚታወስ ሲሆን ይሄንኛው የአቶ ሽመልስ ቃል፣ የመንግስት ቃል መሆኑን እንዴት ማረጋገጥ ይቻለናል? ሦስተኛ፤ በ1994 የቴሌ ሴንተር አገልግሎት ፈቃድን በተመለከተ በወጣው መመሪያ አንቀጽ 13(2) ላይ VoIP (ከኮምፒዩተር ወደ ኮምፒዩተር የሚደረግ የድምጽ ግንኙነት ጨምሮ /ስካይፕን ያካትታል/) የተከለከለ ቢሆንም፣ ሚኒስትር ዲኤታው ‹‹እስካሁን አልተከለከለም፣ ወደፊትም አይከለከልም›› ዓይነት መግለጫ ማድረጋቸውን ተአማኒነት አጠራጣሪ አያደርገውም ወይ? አራተኛ፤ እርሳቸው ስካይፕ አይከለከልም ሲሉ ከረቂቅ አዋጁ አንጻር በሚኒስትሩ ከሚፈቀዱ ሶፍትዌሮች ዝርዝር ውስጥ ይገባል ማለታቸው ነው ወይስ ፈቃድ እየተጠየቀባቸው ከሚሰጡ አገልግሎቶች እንዳንዱ ይሆናል ማለታቸው ይሆን? …››

* * *


‹‹የትምህርት ፖሊሲው ምን እያፈራ ነው? ድንጋይ ጠራቢ ወይስ ባለሙያ?›› ባለው ሐተታው ሪፖርተር ጋዜጣ በእሁድ እትሙ ለተማረ ሰው ቦታ እንደሌለው፣ መማርም ትርፉ ድካም ነው የሚያሰኝ መርዶ አስነብቧል፡፡ ‹‹… ሰሞኑን የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የመንግሥትን ሥራ ሳይጠብቁ በግላቸው ሥራ ፈጣሪዎች ሆነዋል ያላቸው በአርዓያት የሚጠቀሱ የዩንቨርሲቲ ምሩቃንን በማስመልከት ያቀረበው ዘገባ ብዙዎችን አስደንግጧል፡፡… መንግስት ለፕሮፓጋንዳ ይጠቅመኛል ብሎ ባሰበው በዚህ ዝግጅት የዩኒቨርሲቲ ምሩቃን አንድ ያልተማረ ዜጋ ሊሠራው በሚችለው የድንጋይ ጠረባ ሥ ተሰማርተው ውጤታማ መሆናቸውን ገልጾልናል፡፡… የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ከዩንቨርሲቲ በዲግሪ የተመረቀና ማስተርስ ዲግሪውን እየተከታተለ ያለ አንድ ግለሰብ በድንጋይ ጠረባ ተሰማርቶ ስኬታማ መሆኑን ገልጾልናል፡፡… የአማራ ክልል ቴሌቪዥን ጣቢያም ከዩንቨርሲቲ በኢኮሚክስ የተመረቀ ወጣት፣ … በባዶ እግሩ በበሬ ሲያርስ አሳይቶናል፡፡ ይህንኑ ባሕላዊ የአስተራረስ ዘዴ የሚከተሉት ወጣቱ ምሩቅና ጓደኞቹም በአርዓያት ሊጠቀሱ የሚገባቸው ሥራ ፈጣሪዎች መሆናቸውን ጣቢያው  ሊያስረዳ ሞክሯል፡፡…››

ሌላም፣ ሌላም

  • ‹‹ወደ ትግሉ የገባሁት ቅድሚያ ራሴን ነፃ ለማውጣት ነው›› - ወ/ሮ ላቀች ደገፉ (ፍኖተ ነፃነት)

  • ከፍኖተ ነፃነት እስከ ፍትህ ከጋዜጠኞችና አምደኞች የታቀደው የእስር ዘመቻ - የኢሕአዴግ የቅድመ ምርጫ ዝግጅት? -  ፍኖተ ነፃነት

  • ኦላና ፖታሽ ከ1.2 ቢሊዮን ቶን በላይ የፖታሽ ክምችት ማግኘቱን አስታወቀ፤ በዓመት ከሁለት ቢሊዮን ዶላር በላይ የሚያወጣ ፖታሽ ለመሸጥ ታቅዷል፡፡ - ሪፖርተር (ረቡዕ)

  • ለሻይ ቅጠል ሰፊ መሬት የወሰደው የህንድ ኩባንያ ጣውላ ሲያመርት ተገኘ - ሪፖርተር (ረቡዕ)

  • የእንግሊዙ ዱዌት ግሩፕ ከዳሸን ቢራ ጋር መፈራረሙ ጥያቄ አስነሳ፤ አንድነት እና አረና ፓርቲዎች ስምምነቱ እንዳሳሰባቸው ገልፀዋል፡፡ ‹‹ዳሸን ቢራ የፓርቲ ንብረት አይደለም፤ ተቃዋሚዎች በሬ ወለደ ማውራት ልማዳቸው ነው፡፡›› አቶ ታደሰ ጥንቅሹ የጥት ዋና ሥራ አስፈፃሚ - ሰንደቅ

  • ‹‹በኢትዮጵያ ውስጥ ባሳተመው ዘገባ ወይም አየር ላይ ባዋለው ፕሮግራም ምክንያት የታሰረ አንድም ጋዜጠኛ የለም›› - አቶ ሽመልስ ከማል (ሰንደቅ)

  • New party vows to reconcile Meles and MengistuTHE Reporter

  • በመንግስት ትምህርት ቤት ከመጠቃለሉ ውሳኔ በስተጀርባ ምን አለ? - አዲስጉዳይ
    ‹‹…በአዲስ አበባ ከሚገኙ 117 የሕዝብ አንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ውስጥ ወደ መንግሰት የተዘዋወሩት 115 ናቸው፡፡……ሰፋ ተደርጎ ያልተነገረለት ነገር ግን በየዕለቱ እየናረ በመጣው ኑሮ ውድነት ሳቢያ ኪሱ የሳሳ ወላጅ ከክፍያ ነፃ ቢሆን ቢያንስ የልጁን ምሣ ለመቋጠር የሚያስችለው አቅም ያተርፋልና የሕዝብ ት/ቤት ወደ መንግስት መዞሩ ደስ አሠኝቶት ይሆናል፡፡ ለማንኛውም ግን ድህነትና የኑሮ ውድነት የት ድረስ ዘልቆ የከረሙ አሠራሮችን እያስለወጠ እንደሆነ ለማየት እነዚህ ውሣኔዎች ዋቢ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡››


ርዕሰ አንቀጾች

አህያውን ፈርቶ ዳውላውን

  • የኤርትራ ዜጎች ያለፍርድ ቤት እውቅና ይታሰራሉ - የኛ ፕሬስ

  • ኤርትራውያን ስደተኞ ተስፋ ስለቆረጡባት አገራቸው ይናገራሉ - አዲስ አድማስ

  • የኤርትራ መንግስት ተወቀሰ፣ ተከሰሰ - አዲስጉዳይ


ቀልድ ይመስል ዜና

  • ‹‹አብዮታዊት እናት ሀገር ወይም ሞት›› ዐውደ ርዕይ ነገ ይከፈታል - ሪፖርተር (ረቡዕ)
    ‹‹የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የሥነ ጥበብና ዲዛይን ትምህርት ቤት፣ ‹‹አብዮታዊት እናት ሀገር ወይም ሞት›› በሚል ርእስ ያዘጋው የሥዕል ዐወደ ርዕይ በተቋሙ ነገ ይከፈታል፡፡ በዘመነ ደርግ ከ1967 – 1983 ድረስ በተቋሙ ተማሪዎች የተሠሩ ልዩ ልዩ የሥነ ጥበብ ውጤቶች ለእይታ ይበቃሉ፡፡…››

2 comments:

  1. I would like to share with my colleagues so that they also get the opportunity to read such an informative blog.
    http://www.kitsonlinetrainings.com/scala-online-training.html
    http://www.kitsonlinetrainings.com/sccm-2012-online-training.html

    ReplyDelete
  2. I feel happy to find your post, excellent way of writing https://www.gotrainings.com/dell-boomi-online-training
    https://www.gotrainings.com/devops-online-training

    ReplyDelete