Saturday, May 10, 2014

የዞን 9 ጦማሪያን ሁለተኛ ክስ ላይ ያለኝ የህግ አስተያየት -1-

በእዮብ መሳፍንት
  1. በህቡዕ መደራጀት
በህቡዕ መደራጀት ወንጀል ነው???
በኢፌድሪ ህገ መንግስት አንቀፅ 31
“ማንኛውም ሰው ለማንኛውም አላማ የመደራጀት መብት አለው፡፡ ሆኖም አግባብ ያለውን ህግ በመጣስ ወይም ህገመንግስታዊ ስርአቱን በህገወጥ መንገድ ለማፍረስ የተመሰረቱ ወይም የተጠቀሱትን ተግባራት የሚያራምዱ ድርጅቶች የተከለከሉ ይሆናሉ”
 ይላል፡፡ ከዚህ አንቀፅ በግልፅ እንደምንረዳው በህቡዕም ሆነ በግልፅ መደራጀት መብት ነው፡፡ መደራጀት የሚከለከለው “ህግ በመጣስ ወይም ህገመንግስታዊ ስርአቱን በህገወጥ መንገድ ለማፍረስ” ከሆነ ብቻ ነው፡፡
ስለሆነም “ፖሊስ” (በተግባር ከሳሹ ኢሃዲግ ቢሆንም) በዞን 9 ጦማሪያን ላይ ባቀረበው ክስ በህቡዕ መደራጀትን በራሱ ወንጀል ለማስመሰል መሞከሩ ከህግ አግባብ ውጪ ብቻ ሳይሆን ህገመንግስቱን የሻረና የናደ ተግባር ነው፡፡ አላማውም ማንኛውንም መደራጀት ማስፈራራትና ሰዎችን ከመደራጀት እንዲቆጠቡ ማድረግ እንደሆነ ግልፅ ነው፡፡ ሲጀመር ዞን9 የጦማሪያን ስብስብ እንጂ ህጋዊ ሰውነት ያለው የተደራጀ አካል ወይም ድርጅት አይደለም፡፡ ለዚህም ነው አቃቤ ህግ ዞን 9ን በቀጥታ ሊከሰው ያልቻለው (በህግ መሰረት ህጋዊ ሰውነት የሌለውን አካል መክሰስ ስለማይቻል)፡፡ መሰባሰብን እና መደራጀትን በቅድሚያ መለየት ያስፈልጋል፡፡ ሁሉም ስብስብ መደራጀት አይደለም፡፡
ከዚህ በፊት በልጆቹ ላይ ፖሊስ መስርቶት የነበረውን “ራሱን የሰብአዊ መብት ተሟጋች ብሎ ከሚጠራ ድርጅት ጋር አብሮ መስራት” የሚለው ክስ እንደማያዋጣ እንደገባው ሁሉ አሁንም ይሄኛው ክስ አያዋጣም፡፡

      2.    ሁለተኛው የክሱ ነጥብ “ከሽብርተኛ ቡድን ጋር አብሮ መስራት”
ይህ ሽብርተኛ የተባለው ቡድን የትኛው እንደሆነ ባይገለፅም በኢትጲያ ውስጥ ሽብርተኛ የተባሉት ግንቦት 7፣ ኦነግ፤ ኦብነግ እና አልቃይዳ ብቻ ናቸው፡፡ ስለዚህም ልጆቹ ከነዚህ ድርጅቶች ከአንዱ ጋር ሰርተዋል ብሎ ፖሊስ ካመነ ማስረጃ ሊኖረው ይገባል መለት ነው፡፡ ስለዚህም ማስረጃ ላሰባስብ በሚል ፖሊስ ተጨማሪ ጊዜ መጠየቁ አስቂኝ ነው፡፡ መጀመሪያ አስሮ ማስረጃ ማሰባሰብ ማለት ወንጀል መፈብረክ እንጂ ወንጀልን መክሰስ ዐያደለም፡፡
ከነዚህ ከላይ ከጠቀስኳቸው ድርጅቶች ውስጥ አንደኛው የውጭ ሀገር ድርጅት ሌሎቹ ሁለቱ ደግሞ ብሄር ተኮር ድርጅቶች ስለሆኑ ፖሊስ ሊል ያሰበው ምናልባት ግንቦት 7ን ሊሆን ይችላል ወይም ባለፈው ክስ “ራሱን የሰብአዊ መብት ተሟጋች ብሎ ከሚጠራ ድርጅት” ያሉትን ድርጅት ደረጃውን ወደ አሸባሪ ድርጅት ከፍ አርገውት ሊሆን ይችላል፡፡ እኔ በግሌ ልጆቹ በብሎጋቸው የፃፉት ሰላምን፤ አንድነትን፤ ፍቅርን፤ የሰባዊ መብት መከበርን፤ ዶሞክራሲን እንጂ አንድም ቀን ሽብርን ሲፅፉ አይቼ አላውቅም፡፡ እነዚህ ነገሮች ሽብር ከተባሉም ሽብር መልካም ነገር እንጂ መጥፎ ነገር አይደለም፡፡
ስለዚህም እጠይቃለሁ የዞን 9 ጦማሪያን ወንጀል ሰርተዋል ብዬ አላምንምና ባስቸኳይ ይፈቱ፡፡ Zone9
‪#‎freezone9bloggers‬

No comments:

Post a Comment