Thursday, December 6, 2012

ሕገ መንግስታዊነት


የፈረንሳዩ ንጉስ ልዊ  17ኛ የአምባገነንነት መገለጫ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ ስልጣኑን ሲያስረግጥም ‘I am the State’ በማለት ነው፡፡ አዎ ልዊ 17ኛ የአምባገነንነትን መጨረሻ ጫፍ አሳውቆናል፡፡ ‹ሀገር የእኔ፤ አኔም ሀገር› ብሎ ማወጁ ‹የፈለኩትን ማድረግ እችላለሁ፣ ፈላጩም ቆራጩም እኔ ነኝ!› እንዲል አደርጎታል፡፡
እንግዲህ በተለየዩ ሀገራት የመንግስት አካላትን ስልጣን በሕግ መገደብ አስፈላጊ የሆነት ዋነኛ ምክንያት እንዲሃ ያለውን ልቅ የስልጣን ምቾት ለማለዘብ ነው፡፡ ሕገ መንግስት ደግሞ ስልጣንን ለመገደብ ተብለው ከሚቀመጡ ገደቦች አንዱና ዋነኛው ነው፡፡ ግን ሕገ መንግስት መኖሩ ብቻ ባለስልጣኖችን ስርዓት ለማሲያዝ ይበቃልን?

ሕገ መንግስታዊነት ስንል

ሕገ መንግስታዊነት መነሻውም መድረሻውም ሕገ መንግስቱ ነው፡፡ የሕገ መንግስታዊት ፅንሰ ሀሳብም ከሕገ መንግስት ፅንሰ ሀሳብ ጋር አብሮ የዳበረ ሀሳብ ነው፡፡ Walton Hamilton የተባሉት የህግ ባለሙያ ሕገ መንግስታዊነትን ሲያብራሩ “Constitutionalism is the name given to trust which men to repose in the power of words engrossed on parchment to keep the government in order.” ማለትም ‹‹ሕገ መንግስታዊነት ሰዎች በፅሁፍ ለተቀመጡት እና መንግስትን ስርዓት ለሚያስገቡት ቃላቶች የሚሰጡት እምነት ነው፡፡›› በማለት ነው፡፡ በጥቅሉም ሕገ መንግስታዊነት ስንል ሕገ መንግስቱን ተግባራዊ ማድረገ ማለታችን ነው፡፡ ከዚህ መሰረታዊ ሀሳብም ሁለት አንኳር ጉዳዮችን ማውጣት እንችላለን፡

እምነት (Trust)

እምነት ሰዎች በሕገ መንግስቱ ተማምነው እና ሕገ መንግስቱን እንደ ድጋፍ አድርገው በስርዓቱ ውስጥ የሚኖሩበት ተስፋ ነው፡፡ ሰዎች ሕገ መንግስቱን የሚያከብሩት ሌሎችም እንደኔ ሕገ መንግስቱን ያከብሩታል፤ አናከብርም ቢሉ እንኳን መንግስት ይሄን አመኔታየን ያስከብርልኛል ብለው ነው፡፡ ከዚህም የተነሳ በሕገ መንግስቱ የተቀመጡት ቃላት በስርዓቱ ያላቸውን አመኔታና በሕግ መንግስቱ ላይ ያላቸውን መመካት ገላጭ ነው፡፡ ተበዳይ ‹ኧረ በሕግ አምላክ› ብሎ መብቱን ሲጠይቅ፤ በዳይ (መንግስትም ሆነ ግለሰብ) ሕግን አስታውሶ እራሱን ከተግባሩ ሲገታ፤ ይሄ ነው ዜጎች በሕጉ ላይ ያላቸው እምነት፡፡ ‹ሕጉን አምኝ› እንዲሉ፡፡

መንግስትን ልክ ማስገባትና መገደብ (Limited and Restrained Government)

ሌላው የሕገ መንግስታዊነት ዋነኛ ግብ እና ዓላማ፤ መንግስትን በሕግ በተሰጠው ማዕቀፍ ውስጥ እንዲንቀሳቀስ እና ከተሰተው የስልጣን ገደብ ውጭ ዝንፍ እንዳይል እንደ መቆጣጠሪያነት ማገልገሉ ነው፡፡ በዲሞክራሲያዊ አስተዳደር መንግስት የዜጎች ይሁንታ ውጤት እንደመሆኑ መጠን፤ ይሄ ይሁንታም በሕገ መንግስቱ የተገለፀ እና በሕገ መንግስታዊነት የሚተረጎም ነው፡፡ ዜጎች መንግሰታቸውን ሲያበጁ ያንተ ስለጣን እስከዚህ ነው፤ ከዚህ በላይ መጓዝ አትችልም ብለው በሕግ ለክተው ስልጣኑን ለመንግስት ይነግሩታል፤ መንግስትም በተሰመረለት ክበብ ውስጥ ይጫወታል፤ ያኔም ሕገ መንግስታዊነት አለ እንላለን፡፡ ስልጣኑ ተገድቦ ሕግን የሚተገብር መንግስትም (Limited Government) የዲሞክራሲያዊ ስርዓት ዋነኛ ምሰሶ ነው፡፡

ሕገ መንግስቱ ስለ ሕገ መንግስታዊነት

የማንኛውም ሀገር ሕገ መንግስት በመሰረታዊነት ባለ ሁለት ጫፍ (Double Edged) ነው፡፡ በአንድ በኩል ለዜጎች እና ለመንግስት መብት ይሰጣል፣ ግዴታም ይደነግጋል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ እነዚህ መብቶች እና ግዴታዎች እንዴት መሬት ይነካሉ፣ በማን ይፈፀማሉ ለሚሉት ጥያቄዎች ምላሽ ይሰጣሉ፡፡ እንግዲህ ሕገ መንግስታዊነትን በዚህ በሁለተኛው ጫፍ ላይ ቆሞ እናየዋለን ማለት ነው፡፡  

ሕገ መንግስት ያለ ሕገ መንግስታዊነት

ሕገ መንግስታዊነት ዘመናት በጨመሩ ቁጥር አብሮ እያደገ  የመጣ ሀሳብ ሲሆን አሁን ባለው መሰረታዊ መግባባትም ሕገ መንገግስታዊነት ማለት መንግስትን እንደ መገደቢያ መሳሪያ፣ የፈላጭ ቆራጭነት ተቃራኒ (The Antithesis of Authoritarianism) እንዲሁም የአሉታዊው አምባገነንነት አዎንታዊ ፀር ተደርጎ የሚወሰድ ሰፊ ሀሳብ ነው፡፡ አዎ ሕገ መንግስት የሕግ የበላይነት ዋነኛ መሰረት ነው፡፡ ነገር ግን ሕገ መንገስታዊነት በሌለበት ሕገ መንግስት ከወረቀት ላይ ነብርነት አይዘልም፤ አስፈላጊነቱም እዚህ ግባ የሚባል አይደለም፡፡ ለዚህ ጥሩ ማነፃፀሪያ የሚሆኑን የ1923ቱ የኢትዮጵያ ሕገ መንገስት እና የ1947ቱ የተሻሻለው ሕገ መንግስት ናቸው፡፡ የ1923ቱ ሕገ መንግስት በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኝው መሬቱም፣ ሕዝቡም ሕጉም የንጉሰ ነገስቱ ነው ብሎ ፍፁማዊ እኔ ሀገር ነኝን (I am the State) ይሰብካል፤ በሕግ መግዛት (Rule By Law) እንጅ ለሕግ መገዛት (Rule of Law) ፈፅሙ ያልተፈቀደ እንደሆነ ያስቀምጣል፡፡ ይሄ ሕገ መንግስት ወደ መሬት ወረደም አልወረደም ለዜጎች የሚያመጣው ለውጥ የለም፡፡
በሌላ በኩል የተሻሻለው 1947ቱ ሕገ መንግስት ደግሞ 20 የሚበልጡ አንቀፆችን፤ መምረጥ እና መመረጥን መብት ጨምሮ ለዜጎች የተሰጡ መብቶችን ለመደንገግ አውሏቸዋል፡፡ ነገር ግን የኢትዮጵያዊያን ህይወት መሻሻል አለመቻሉ ለንጉሱ ስርዓት ውድቀት ዋነኛ መነሻው ነበር፡፡ ለዚህም ዋነኛው ምክንያት ሕገ መንግስታዊነት አለመኖሩ ነው፡፡ እናም ሕገ መንግስታዊነት ከሌለ የሕገ መንግስት መኖር በህግ መግዛትን እንጅ ለሕግ መገዛትን አያመጣም፤ ጥቅሙም አይታይም፡፡  

ሕገ መንግስታዊነት ‘በልማታዊት’ ኢትዮጵያ

የአምሰተርዳሙ ነዋሪ እና በኢትዮጵያ ላይ እጅግ ብዙ ጥናቶችን እና ምርምሮችን ያደረጉት ፕሮፌሰር ጆን አብኒክ ‘Ethiopia Ethnicity and Constitutionalism in the Contemporary Ethiopia’ ባሉትና የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ሕገ መንግስት (የኢፌድሪ ሕገ መንግስት) ላይ ባተኮረው ፅሁፋቸው  “When reading the constitution it is also notable that how far the proclaimed text s removed from the actual practice of the political culture and social relations in.” በማለት ‹ሕገ መንግስት ወዲያ፤ ተግባር ወዲህን› ያዜሙልናል፡፡
እንደ ፕሮፌሰር ጆን አብኒክ ሁሉ በዛ ያሉ የምዕራብ የሰብዓዊ ተቋማት፣ የተለያዩ መንግስታት እንዲሁም የተለያዩ ኢትዮጵያዊያን ሕገ መንግስቱና እና መሬት ላይ ያለው እውነታ እጅግ ይለያያል እናም ኢህአዴግ በእጁ ያለውን ሕገ መንግስት ያክብር እያሉ ይማፀናሉ፡፡

ሕገ መንግስቱን ማን ያክብረው?

የኢፌድሪ ሕገ መንግስት አንዳንድ አካላት እንደ አፍራሽ ሰነድ ቢመለከቱም አለም ዓቀፍ የሰብዓዊ ስምምነቶችን ሙሉ ለሙሉ መቀበሉ፤ እንዲሁም ከአጠቃላይ ከአንቀፆቹ ሲሶ (30 አንቀፆች) ያህሉን ለዜጎች መብትን ለመዘርዘር እና ለመስጠት ማዋሉን ስንመለከት፤ ሀገሪቱ ዘመናዊ የሕገ መንግስት ስርዓት ውስጥ ከገባች ጊዜ ጀምሮ የዜጎችን መብት በተሻለ ደረጃ በመለገሱ  ረገድ ትልቅ እምርታን ያሳየ ሕገ መንግስት እንደሆነ እንድንረዳ ያደርገናል፡፡ ታዲያ ይህ ሁሉ መብት በሽ የሆነበት ሕገ መንግስት ምነው ተቃውሞ በዛበት; ብለን ስንጠይቅ፤  መልሳችን ‹ሕገ መንግስታዊነት› የሚል ነው፡፡

የኢፌድሪ ሕገ መንግስትም ሕገ መንግስታዊነት ወሳኝ እና ዋነኛ የስርዓት አካል አድርጎ በመውሰድ በተለያዩ አንቀፆቹ ሕገ መንግስቱ እንዲከበረና ሕገ መንገስታዊነት እንዲሰፍን ያስገድዳል፡፡
በጥቅሉ በአንቀፅ 9 ንዐስ ቁጥር 3 ላይ ‹‹ማንኛውም ዜጋ፣ የመንግስት አካላት፣ የፖለቲካ ድርጅቶች ሌሎች ማሕበራት እንዲሁም ባለስልጣኖቻቸው ሕገ መንግስቱን ማስከበርና ለሕግ ተገዥ የመሆን ሀላፊነት አለባቸው፡፡›› በማለት ሁሉም ዜጋ ላይ ግዴታን ይጥላል፡፡

እንዲሁም በተለየ ሁኔታ የተለያዩ አካላትን ሕገ መንግስታዊነት ይስን ዘንድ እንዲሰሩ ያስገድዳል አንቀፅ 13 ንዑስ ቁጥር 1 ላይ ‹‹በማንኛውም ደረጃ የሚገኙ የፌደራል መንግስትና እና የክልል ህግ አውጭ፣ ሕግ አስፈፃሚና የዳኝነት አካላት በዚህ ምዕራፍ (በሕገ መንግስቱ ምዕራፍ ሶስት የተካተቱትን መብቶች እና ግዴታዎችን ለማለት ነው) ድንጋጌዎች የማክበርና የማስከበር ኃላፊነትና ግዴታ አለባቸው፡፡››፣  አንቀፅ 51 ንዑስ ቁጥር 1 ላይ ‹‹የፌደራሉ መንግስት ሕገ መንግስቱን ይከላከላል፣ ይጠብቃል፡፡›› ብሎ ያስቀምጣል፡፡ አንቀፅ 74 ንዑስ ቁጥር  13 ላይ ‹‹ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሕገ መንግስቱን ያከብራል፤ ያስከብራል፡፡›› በማለት ጠቅላይ ሚኒስትሩን የሕገ መንግስታዊ ግዴታ ተወጭ ያደርገዋል እንዲሁም አንቀፅ 87 ንዑስ ቁጥር 4 ‹‹የመከላከያ ሰራዊቱ በማናቸውም ጊዜ ለሕገ መንግስቱ ተገዥ ይሆናል፡፡›› በማለት የመከላከያ ሰራዊቱ ለሕገ መንግስቱ በመገዛት ሕገ መንግስታዊነትን ያሰፍን ዘንድ ያስገድደዋል፡፡

እንግዲህ ሕገ መንግስታዊነት ይኖር ዘንድ አኒህ ሁሉ ግዴታዎች በሕገ መንግስቱ ተቀምጠው ነው፤ መንግስት ‹የምን ሕገ መንግስት› በማለት የመብት ጥሰቶች እና ኢ-ሕገመንግስዊነት አሰፍኗል ተብሎ እየተነገረ ያለው፡፡

ሕገ መንግስታዊነት እንደ አጀንዳ

ኢሕአዴግ ከምርጫ ዘጠና ሰባት ወዲህ በተቃዋሚው ጎራ ላይ ከለጠፋቸው ታፔላዎች አንዷ ‹የቫይማር ሪፐብሊክ (Weimar Republic) ናፍቆት› ትሰኛለች፡፡ በአጭሩ ሀሳቡ ከአንደኛው የአለም ጦርነት በኋላ የነአዶልፍ ሂትለር The Third Reich እስኪመሰረት ድረስ የነበረችው ጀርመንን ለማመላከት ሲሆን፤ ኢህአዴግ ሀሳቡን ሲያስቀምጥም ‹‹ተቃዎሚዎች እንደ ድህረ የመጀመሪያው የአለም ጦርነቷ የቫይማር ሪፐብሊክ ኢህአዴግን በማድከም ወደ ቫይማር ሪፐብሊክነት ቀይረው፤ በመጨረሻም ሒትለር የየቫይማር ሪፐብሊክን ግሩም ሕገ መንግስት ቀዳዶ እንደጣለው ሁሉ እነዚህ ተቃዋሚዎችም የኢፌድሪ ሕገ መንግስትን ቀዳደው ለመጣል የተዘጋጁ ናቸው›› እያለ በተለያዩ ሰነዶቹ ላይ ትችቶቹን ያቀርባል፡፡

ተቃዋሚው ጎራ ‹የሕገ መንግስት ይሻሻል› ጥያቄውን እንደ ያዘ ሕገ መንግስታዊነት እንዲሰፍን ቢተጋ ኢህአዴግን አጀንዳ ከማሳጣትም አልፎ ‹ሒትለር መጣብህ› ከሚል አለቅጥ የሚጮህ ኢህአዴግዊ ጅራፍ እራሱን ይጠብቃል፡፡ ለዜጎችም ቀላል እና የሕግ ጥልፍፎሽ ውስጥ የማያስገባ የመብት ጥያቄ መሆን ይችላል፤ ሕገ መንግስታዊነት ይስፈን - ሕገ መንግስቱ ይከበር እንደማለት፡፡

No comments:

Post a Comment