Monday, October 19, 2015

የማእከላዊ ምርመራ የማሰቃየት ምርመራ መዘዝ - በጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ ላይ

የ2007 አገር አቀፍ ምርጫ መቃረብን ተከትሎ መስዋእት ከሆኑት  የዞን ዘጠኝ ጦማር አባላት ውስጥ የሽብር ክሱ ወደ ወንጀል ክስ ተቀይሮ ዛሬም በግፍ እስር በብቸኝነት የሚገኘው በፍቃዱ ዘ ኃይሉ አመጽ ለመቀስቀስ አስበህ ነው የጻፍከው የተባለውን ጽሁፍ እንዲከላከል ተወስኖበታል፡፡ ይህ የአመጽ መቀስቀስ የተባለው ጽሁፍ ራሱን ሳይሆን የበፍቃዱን የማእከላዊ ምርመራ ቃል ብቻ የተመለከተው ፍርድ ቤቱ ቃሉን ብቻ መሰረት በማድረግ ይከላከል በማለት የማእላዊ ምርመራን በማሰቃየት ውስጥ የተሰጠ ቃል ተቀብሎታል ማለት ነው ?

በአስገዳጅ ሁኔታ የተገኘ ማስረጃ እንደማስረጃ አይቆጠርም የሚለው የሕጎች ሁሉ የበላይ ነው የሚገባለው እና በፍቃዱ ከጓዶቹ ጋር ሆኖ ይከበር! ሲል የነበረው ሕገ-መንግስቱ አንቀፅ 19.5 እንዲህ ይላል

‹‹የተያዙ ሰዎች በራሳቸው ላይ  በማስረጃነት ሊቀርብ የሚችልየእምነት ቃል እንዲሰጡ ወይም ማናቸውንም ማስረጃ እንዲያምኑ አይገደዱም፡፡ በማስገደድ የተገኘ ማስረጃ ተቀባይነትአይኖረውም፡፡››

ከወራት በፊት የጦማርያኑን እስር አንደኛ ዓመት አስመልክቶ የመብት ጥሰቶችን ዞን ዘጠኝ ጦማር ባስታወሰበት ወቅት በበፍቃዱ የደረሰበት የማሰቃየት ወንጀል እንዲህ ገልጾት ነበር ፡፡

‹‹ማዕከላዊ ምርመራ በቆየሁባቸው ቀናት ከእሁድ በስተቀር ጠዋት ከሰአትማታ እየተጠራሁ በዛቻ በአጸያፊ ስድብ ጭካኔ የተሞላበት ግርፊያ ጥፊና እርግጫ አንዲሁም ከአቅሜ በላይ የሆነ ስፓርት እየሰራሁቃሌን እንድሰጥ ተገድጃለሁ፡፡ የተያዝክበትን ድብቅ አጀንዳ ንገረን በማለት ራሴን እንድወነጅል ተገድጃለሁ፡፡
  1. መርማሪው በመጀመሪያ ቀን ምርመራ በጥፊ መማታት የጀመረ ሲሆን እያንዳንዱን ጥያቄ ከጠየቀኝ በኋላ በጥፊ ይመታኝ ነበር
  2. የዞን9 ዓላማ ጠይቆኝ ስነግረው ድብቁን አውጣ በማለት መሬት ላይ አንድቀመጥ እና ያደረኩትን ነጠላ ጫማ እንዳወልቅ አዞኝ በኮምፒውተር ገመድ እግሬን መግረፍ ጀመረ፡፡ በተጨማሪም በሆዴአንተኛ በማዘዝ እና እግሬን አጥፌ ከፍ አንዳደርገው በማድረግ ውስጥ እግሬን ገርፎኛል፣ግርፊያው ውስጥ እግሬን ሲለበልበኝ ነበር ፡፡
  3. ድብቁን አጀንዳህን ካልተናገርክ ነገ እዘለዝልሃለሁ በሚል አስፈራርቶኛል፡፡
  4. ድምጽ እንዲያፍን ሆኖ ወደተሰራው የስብሰባ አዳራሽ ተወስጄ በጥፌ እየደበደቡኝ የዞን9አላማ ተናገር ተብዬ ተደብድቤያለሁ፡፡ ስቃዬ ሲበዛብኝም የፈጠራ ታሪክ እንዳወራ ተገድጃለሁ፡፡ እኔ የምጽፈው ኢትዮጵያ ውስጥ አብዬት ለማስነሳት ነው ብዬ እንድፈርምም አስገድደውኛል››
  5. በምርመራ ወቅት እጄ በካቴና እነደታሰረ ለሰአታት ቁጭ ብድግ አንድል ተገድጃለሁ፡፡
  6. መርማሪው በአንድ ወቅት አራት የዞን9 አባላት ሆናችሁ ስለአላማው የተወያያችሁትን በቃል መስጫው ክስ ላይ ልጽፍ ነው ሲለኝ አንደዛ አይነት ውይይት ማድረጋችንን አላስታውስም ስለው እንዴት አታስታውስም ብሎ በጥፊ መማታት ጀመረ። በተደጋጋሚ ከመደብደብም በላይ እስክስታስታውስ እዚሁ ታድራታለህ በማለት ድብደባው በመቀጠሉ አስታውሳለሁ ብዬ ተገላገልኩ ፡፡ የሰጠሁት ቃል ላይም እንደፈለገው አድርጎ ጻፈው፡፡  እኔም በድብደባ ብዛት መርማሪው አለ ብሎየጻፈውን ፈርሜያለሁ ፡፡
  7. ዞን9 ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት የሌለው ከሆነ ይህንን ህዝብ አንዴት ነው ነጻ የምታወጡት በሚል ሲጠይቁኝ የነጻ አውጪነት ሚና የለንም ስላቸው ከወንበሬአንድነሳ አዘዙኝ፡ ከዚያም በቆምኩበት ግራ ብብቴን እና እጄን በአንድ እጁ አንዳልወድቅ ወጥሮ ይዞ በእግሩ ጭኔን በሃይል ደበደበኝ ፡፡ ከድብደባው በማስከተል ደግሞእግሬ መሃል እግሩን በማስገባት ወደግራ እና ወደቀኝ በመምታት ተዘርጥጬ እንድቆይ በማድረግ እጄን ወደላይ አድርጌ እግሬ ግራና ቀኝ ተዘርጥጦ ( በተ<a></a>ለምዶ ስፕሊት ሚባለው) በግራ እና ከቀኝ በመደብደብ እጄን ወደላይ አድርጌ እነድመረመር ተደርጌያለሁ፡፡ከዚህ ምርመራ በኋላ ለሁለት ቀን እያነከሰኩ ነበር፡፡››
በፍቃዱ ሃሳቡን በነጻነት በመግለጹ ብቻ እንደወንጀለኛ ተቆጥሮ እስካሁንለ542 ቀናት አግባብ ባልሆነ እስር ላይ ይገኛል፣ በዚህ ሁኔታ የተሰጠ ቃል ተቀባይነት ማግኘት ስለማይገባው በፍቃዱ ሃይሉእሮብ ከቤተሰቡ ጋር ሊቀላቀል ይገባል ፡፡

No comments:

Post a Comment