Tuesday, September 1, 2015

‹‹ ጨዋ›› ነዎት ‹‹ባለጌ››?

በፍቃዱ ዘ ኃይሉ
ሐምሌ 27/2007 ለኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች እና ቀናኢ ፍትሕ ለሆኑ ሰዎች በሙሉ የመርዶ ቀን ነበር፡፡ ስለ ሠላማዊነታቸው የተመለከታቸው በሙሉ የፈረደላቸው፣ ባንድ ወቅት መንግስትም በወኪሉ በኩል ሲደራደራቸው የነበሩ፣ ለሦስት ዓመታት ያክል በሕግ የበላይነት አምነው ችሎት ፊት የሠላማዊነታቸውን ማስረጃ ሲደረድሩ የቆዩት የሙስሊሞች ጉዳይ መፍትሄ አፈላላጊ ‹‹ኮሚቴዎች›› (በተለምዶ የሚጠሩበት ስማቸው) እስከ 22 ዓመት የሚድረስ የጽኑ እስራት ፍርድ ተጣለባቸው፡፡ ይህንን ዜና የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢብኮ) ከ7፡30 የቀን ዜና እወጃ ጀምሮ ሲለፍፈው ነበር፡፡ ከዜናው ጋር በማነፃፀሪያነት የቀረበው ሌላ ዜና ግን ግቡን ስላልመታ ይመስላል ማታ አልተደገመም፡፡ ይህንኛው ዜና በተመሳሳይ አንቀፅ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ስለተፈረደባቸው ሰዎች ነው፡፡ እነዚህኞቹ መሣሪያ ታጥቀው የተወሰኑ ሰዎችን ገድለዋል፡፡ሆኖም እንደ ኢብኮ ዘገባ ‹‹የቅጣት ማቅለያ በማስገባታቸው›› 14 ዓመት ተፈርዶባቸዋል፡፡ ዜናዎቹን ያዳመጡ ሰዎች ግን ማነፃፀር የቻሉት የሠላማዊነት ቅጣት መክበዱን ነው፡፡

ፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ"Military and militarism in Africa: the case of Ethiopia" ባሰኙት ጥናታቸው ላይእንዲህ ይላሉ፡-

‹‹በመካከለኛውዘመን እንዳየነው [ጨዋ] ማለት መሣሪያ ታጣቂ ማለት ነበር፡፡ ኋላ ላይ ግን ትርጉሙ ተለውጦ መልካም ፀባይ ያለው ማለት ሆነ፡፡በተመሳሳይ፣ የቃሉ ተቃራኒ የሆነው ‹‹ባለጌ›› የሚለው ቃልም የሚወክለው ጭሰኛውን (ማለትም መሣሪያ የማይታጠቀውን) ነበር፡፡ አሁንየዚህም ቃል ትርጉም ተለውጦ መጥፎ ፀባይ ያለው ማለት ሆኗል፡፡›› (እራሴው እንደተረጎምኩት)

እንግዲህ ኢሕአዴግም የሚያስበው በቀደመው ዘመን የ‹ጨዋ› እና ‹ባለጌ› ትርጉም ነው ማለት ነው፤ ለእርሱ መሳሪያ ከታጠቀ ይልቅ ሠላማዊ ይባልግበታል፡፡ (‹ይባልግበታል› በአሁኑ ትርጉም!) ስለዚህ አቀጣጡም በዚያው መሠረት መሆኑን መግቢያ አንቀፁ ያመለክታል፡፡
የአሁኒቱ ኢትዮጵያ ገዢዎች (‹አመራሮች› አላልኩም፤ አይመጥናቸውም) የመንግስትን ስልጣን ከተቆጣጠሩበት ጊዜ አንስቶ እስከ አሁን (ለሁለት ዐሥርት ዓመታት) ሠላማዊ ትግሎችን በፅኑ ተቃውመዋለል፡፡ እንዲያውም ‹‹የሚችለን ካለ በትጥቅ ትግል ይሞክረን››የሚል መፈክር በተደጋጋሚ አስደምጠዋል፡፡ ዓላማቸው ግልፅ ነው፡፡ ያዋጣናል፣ እናሸንፍበታለን የሚሉትን የትግል ሜዳ እየመረጡ ነው፡፡የኢሕአዴግ ተቃዋሚዎችስ? ገዢው በመረጠላቸው ሜዳ (battlefield) ቢገጠሙት ይሻላል ወይስ ሰላማዊነትን የሙጥኝ ቢሉ? የትኛው ያዋጣል? የትኛው ይቀላል? ከሕዋሐት ምን መማር ይቻላል? አምባገነኖች እንዴት ሥልጣን ላይ ይሰነብታሉ?
ለነዚህ ጥያቄዎች መልስ ከመፈለጌ በፊት ነገሩ ሁሉ ለለውጥ ነው እና በዚህ ፅሁፍ ውስጥ ‹ለውጥ› የሚባለውን ነገርልበይን፡፡ ‹ለውጥ› ማለት በዚህ አገባቡ ‹ወደ ሕዝባዊት፣ ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ የሚደረገው ሽግግር› ነው፡፡

Why Not Violence?

አመፃዊ የትግል ስልት ያዋጣል?
ሠላማዊ ያልሆነ ትግል በሙሉ የትጥቅ ትግል አይደለም፡፡ አመፃዊ የሚለውን ቃል የተጠቀምኩት ከትጥቅ ትግል ወዲያ ሰላማዊ የማይባሉ ስልቶችንም እንዲያካትትልኝ ስለፈለኩ ነው፡፡ በዚህ መስፈርት አመፃዊ ትግል በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ፣ ከአገሪቱ ታሪካዊ ሁነትም፣ ከዓለም አቀፍ ተሞክሮዎችም በመነሳት ያዋጣል ወይ የሚልውን እንጠይቃለን፡፡ ለዚህ ጥያቄ በዚህ ጽሑፍ ሰጥቼ የማልፈው ጉዳይ በተነሳ ቁጥር የሚመጡልኝን መልሶች ነው፡፡


     1ኛ- የዴሞክራሲ መንገድነት

 ዴሞክራሲ በየትኛውም መመዘኛ መንገድ እንጂ መድረሻ አይደለም፡፡ ይህም ማለት አንድ አገር የሆነ የጊዜ ነጥብ ላይ ‹ዴሞክራሲያዊ ሆነ፤ በቃ አበቃ! › የሚባልበት ፈሊጥ የለም፡፡ዴሞክራሲያዊነት ማለት ሁሉንም ሕዝባዊ ጥያቄዎች በዴሞክራሲያዊ መንገድ (በብዙኃን አመራርና ሕዳጣን መብት ጥበቃ፣ በሕግ የበላይነት፣ በወቅታዊ እና ነፃ ምርጫ . . .) መፍታት መቻል ነው፡፡ ይህ የማይቆም፣ መድረሻ የሌለው ጉዞ ነው፡፡ የአመፃ ትግል ዴሞክራሲን ማምጣት አልሞ ሲደረግ ከመነሻው ዴሚክራሲን እንደመድረሻ ስለሚቆጥረው ስህተት ይሆናል፡፡ በአካሄድም ቢሆን አመፃዊ ዴሞክራሲያዊነት ስለማይኖር ምናልባት ነባሪውን ፍፁማዊ አምባገነን በለዘብተኛ አምባገነን (Benevolent dictatorship) መተካት ካልቻለ በቀር አመፃ ለዴሞክራሲ መንገዱን እንደሚከፍት ዋስትና አይሰጥም፡፡
    2ኛ- ‹‹ውሻ ወደትፋቱ ይመለሳል››
ምንም እንኳን ነፃ አውጪዎች በብረት ነጻነትን፣ በእኛ ጉዳይ ዴሞክራሲን እናመጣለን ብለው ቢሸፍቱም - የሚያውቁትም፣ የሚለምዱትም የብረት (አፈሙዝ) ሕግን ነውና - በዓለም እንደታየው መጀመሪያ ላይ ዴሞክራሲያዊነትን ለማስመሰል ቢሞክሩም ቆይተው ግን በብረት ስልጣናቸውን ማቆማቸው የተለመደ እውነት ነው፡፡ ቀደም ሲል የጠቀስነው የባሕሩ ዘውዴ ጥናት እንዲህ ይላል፡-
‹‹.. . ሥልጣን የራሱ የሆነ የማይሻር አመክንዮ አለው፤ ለአብዮታዊ ዲስኩር አያጎበድድም፡፡ ስለዚህ በሕዝባዊ ድጋፍ ተመርኩዞ በአፍሪካ ግዙፍ ከሆኑት ወታደራዊ ሠራዊቶች አንዱን የደመሰሰው እሕአዴግ የራሱን ሥልጣን ለማስጠበቅ መልሶ ወታደራዊ ኃይል ላይ መንጠላጠሉ የሚያስገርም አይደለም፡፡ . . . ››    
በዚህ ረገድም ስናስበው አመፃዊ ትግል እኛ ‹ለውጥ› የምንለውን እንደሚያመጣልን ዋስትና መስጠት አይቻልም፡፡
   3ኛ- ‹‹እኛ›› እና ‹‹እነርሱ›› እንሆናለን
አመፃዊ ትግል (በተለይ የትጥቅ ትግል) አንድን ሕዝብ ቢያንስ ለሁለት ይከፍለዋል፡፡ (እንደ ሶሪያ አይነቶቹ ከዚያም በላይ ከፋፍለውት አሳይተውናል፡፡) ስለዚህ በትግሉ ወቅት የወገን እና የጠላት እየተባሉ የሚፈረጁ የአንድ ሕዝብ ሁለት ክፍሎች፣ከትግሉ በኋላም በዚያው ዓይን መተያየታቸው አይቀሬ ነው፡፡ ለዚህ ጥሩ ምሳሌ የሚሆነው አሁንም በገዢዎቹ የሕዋኃት ልሒቃንና ደጋፊዎቹመካከልና በሌሎች ኢትዮጵውያን መካከል ያለው ልዩነት (ያውም ከ 24 ዓመት በኋላ) የሁለትዮሽ ነው፡፡ ቂም የያዘ እና ያስያዘ ሁለት ወገን ካለ፣ ቂመኛው መልሶ ስለሚሸፍት እንደመጀመሪያው ሁሉ ‹ንጉስ ያለ ለውጥ› እንደጉልቻ እያቀያየረ ይሄዳል፡፡ ዴሞክራሲ መሠረታዊ ሕዝባዊ ስምምነት (consensus) ስለሚጠይቅ አመፃዊ ትግል ዴሞክራሲን እንደማያስገኝ ይህም አንድ ማሳያ ነው፡፡
   4ኛ- ለፍቶ መና
ሕዋኃት የዱር ትግሉን ጨርሶ ቤተመንግስት ሲገባ ከገጠሙት ፈተናዎች አንዱ ‹‹ታጋዮቹን ምን ላድርጋቸው?›› የሚለው ነው፡፡ 17 አመት ሙሉ በዱር በገደሉ ሲዋደቁ ከርመው የስልጣን በትሩን ሲጨብጡ፣ የተለያዩ የመንግስት ኃላፊነት ቦታዎችን በሙያ ብቃት ብቻ ለመሾም (አላሰቡም እንጂ) ቢያስቡም ለትግሉ ስኬት የመማርና የሙያ ልምድ የማካበት እድላቸውን ያባከኑትን ሰዎች ‹‹አፍንጫችሁን ላሱ›› ሊሏቸው አይችሉም፡፡ ምንም እንኳን ታጋዮቹ የሚታገሉት ለዓላማ (cause) ነው ቢባልም፣ድል ሲቀናቸው የአላማው ፍሬ የመጀመሪያው ተቋዳሽ ለመሆን ከመጓጓት አይተርፉም፡፡ ሰው ናቸውና፡፡ ስለሆነም በወታደራዊ አስተዳደር(ማለትም ማዕከላዊነት እና ከላይ ወደታች የትዕዛዝ መሥመር በሚሠራ የአስተዳደር ዘዬ) የሰለጠኑ ሰዎች ከወረዳ እሰከ ጠቅላይ ሚንስትር ቢሮ ሲገቡ ዴሞክራሲን (ከታች ወደላይ የሚወሰንበትን አሰራር) ያመጣሉ ብሎ መጠበቅ አይቻልም፡፡ ያውም ደግሞ በዴሞክራሲያዊ መንገድ የኃላፊነት ቦታዎችን እንዲይዙ ለምርጫ ቢቀርቡ በዕውቀትና ልምድ ማነስ ስለማይመረጡ ከታገሉለት ስርዓት ጋር ቅራኔ ውስጥ በመግባት እንደማያጨናግፉት ምንም ዋስትና የለም፡፡ ይህም አመፃዊ ትግልን ለዴሞክራሲ እንዳይመች ያደርገዋል፡፡
  5ኛ- ዴሞክራሲን ይኖሩለታል እንጂ አይሞቱለትም!
ሕውኃቶች ለ 17 ዓመት ሲታገሉ፣ 60ሺ ነፍስ መስዋዕት ሲያደርጉና ከዚያ በላይ ሲገድሉ፣ተስፋ ያደርጉ የነበሩት እንደ ሃይማኖት ያመልኩት የነበረውን ማርክሳዊ-ሌኒናዊ ርዕዮተ አለም ነበር፡፡ ትግሉ ድል ሲቀናው ግን የታገሉለትርዕዮተ ዓለም ‹‹አለፈበት››፡፡ በዓለም እንደ መንግስት ፀንቶ ለመኖር ‹‹ነጭ ካፒታሊዝም››ን መቀበል ነበረባቸው፡፡ እንደ ገብሩ አስራት ንግግር ‹አልባንያ፣ አልባንያ እየተባለች እንደ ሞዴል የተጠራችው አገር ትግሉ ሳይጠናቀቅ ብትንትኗ ወጣ›፡፡ ሕወኃትም የሞተለትን እና የገደለለትን ስርዐት ንቆ ‹‹የዘመኑን›› ያዘ፡፡ እንግዲህ የአመፃ ትግልን ከሚያስፈሩ ምክንያቶች አንዱ ይህ ነው፡፡ ምናልባት ለሚለወጥ ርዕዮተ ዓለም መልሶ የማይገኝ የሰው ልጅ ነፍስ መስዋዕት ማድረግ ይጠይቃል፡፡ ለሰዎች አንፃራዊ ሰላም እና ደህንነት ሲባልመሞት የውም በገፍ-ምክንያታዊ አይደለም፡፡
በለውጥ ትግል አለሞች ሁሌም ጠርዘኛ (radical) እና መሐከለኛ (moderate) አቋሞችን ይዘው የሚንቀሳቀሱ ሰዎች አሉ፡፡አመፃዊም ሆነ ሠላማዊ ትግሎችን የሚከተሉት ሰዎች እንደ ጠርዘኛ የሚቆጥሯቸው አሉ፡፡ ራሳቸውን አማካይ ብለው ይጠራሉ፡፡ የሚሰጡትም ምክንያት ሠላማዊውም ሆነ አመፃዊው ትግል ለየብቻ መቆም አይችልም የሚል ነው፡፡ በኃይል ስልጣኑን የያዙ ሰዎች ከሠላማዊዎች ጋር መደራደር እና ለለውጥ ፈቃደኞች የሚሆኑት አማፂዎቹን በመፍራት ነው ይላሉ፡፡ ይህንን እንስማማበት ቢባል የአማፂዎችን ሚና ወስዶ የሚጫወተው ማን ነው? በግሌ እኔ የምኖርለት እንጂ የምሞትለት ግብ የለኝም፡፡ አመፃዊ ትግል ደግሞ ለመግደልም ብቻ ሳይሆን ለመሞትም መዘጋጀትን የጠይቃል፡፡ በበኩሌ እኔ የማልገባበትን የትግል መሥመር ሌሎች እንዲገቡበት የምመክርበት ሞራል የለኝም፡፡ እንዲያውም እስከ መሞት በሚደርስ ወኔ የሚታገሉ ሰዎች ካሉ ለሠላማዊ ሜዳ ይበልጥ ውጤታማ መሆን ይችለላሉ ብዬ አምናለሁ፡፡
በሠላማዊ እና በአመፃዊ ትግሎች መካከል ያለው ልዩነት የሕይወትና የሞት ያክል ነው፡፡በሠላማዊ ትግል ትልቁ ፈተና እስር ነው፡፡ አልፎ፣አልፎ ሞት የሚከሰትባቸው ሠላማዊ ትግሎች ቢኖሩም የአመፃዊ ትግሎችን የክል እልቂት የሚያስከትሉ አይደሉም፡፡ ጌታቸው ማሩ ‹ደርግን ለአመፃ ትግል መጋበዙ ይብስ አረመኔ ያደርገዋል› የሚል ስጋት እንደነበረው ሕይወት ተፈራ ‹‹Tower in the sky›› ላይ ገልፃዋለች፡፡ ስጋቱ አልቀረም፤ ለኢሕአፓ የነጭ ሽብር ምላሽ ደርግ በቀይ ሽብር አገሩን አጠበው፡፡ ትግሉ በሁለት ገዳዮች መካከል ስለነበር ኃያሉ ገዳይ አሸንፎ ወጣ፡፡ በድኅረ ምርጫ 97ም የቅንጅት መሪዎች (በተለይ እነ ልደቱ) ስለ ጆርጂያና ዩክሬን የቀለም አብዮት የቀሰቀሱትን ሕዝብ እንዴት ሰላማዊ መሆን እንዳለበት ስላልነገሩት፣ በድንጋይ ውርወራ እና ጎማ በማቃጠል ብሶቱን ገለፀ፤ አጋጣሚው ግን ለኢሕአዴግ ሕዝባዊ ብሶቱን ለማፈን ብቻ ሳይሆን ለዘለቄታውም እንዳይደገም እድሉን እንዲዘጋ መንገድ ጠረገለት፡፡ አሁንም የትጥቅ ትግል እንቅስቃሴች አሉ፡፡ በተለይ በኦነግ፣ ኦብነግ እና ግንቦት ሰባት ስም የተጨፈለቁ ሰላማዊ ታጋዮችን ቁጥር ወሕኒ ቤቱ ይቁጠረው፡፡ እንግዲህ መደራደሪያ ይሆናል የተባለው የአመፃ ትግልም ሠላማዊውን ለማደናቀፊያ እያዋሉ ነው ማለት ነው፡፡
አመፃዊው ትግል ውስጥ (በተለይ በትጥቅ ትግሉ) ሌላም ፈታኝ ጉዳይ አለ፡፡ ሕዋሓት ለድል የበቃው ‹‹የሻቢያ የትሮይ ፈረስ ሆኖ ነው›› የሚሉ አሉ፡፡ ሕዋሓት ጫካ እያለ የማይደራደርባቸው ከነበሩ አቋሞቹ ውስጥ ‹‹የኤርትራ ጉዳይ የቅኝ ግዛት ነው፤ እና የሚፈታው በነፃነት [መገንጠል] ነው›› የሚለው አንዱ ነበር፡፡ ሻቢያ ያን ሕልሙን በሕዋሓት አሳክቷል፤አሁን ደግሞ የኢትዮጵያ አማፂዎች ወዳጅ ሆኗል፡፡ ሻቢያን እንደ ኢትዮጵያ ወዳጅ መቁጠር የሚቻልበት መስፈርት አይታየኝም፡፡ አዲሶቹ አማፂዎችም እንደ ሕዋሓት የሻቢያ የሌላ አጀንዳ የትሮይ ፈረስ እንዳይሆኑ እሰጋለሁ፡፡  
...ይቀጥላል፡፡

No comments:

Post a Comment