Saturday, July 11, 2015

የዞን 9 ጦማርያንን እና ጋዜጠኞችን አስመልክቶ የተሰጠ አጭር መግለጫ

የዞን ዘጠኝ ጦማርያን ሁለት አባላት እና ሶስት ጓደኞቻችንን መፈታት በመልካም ጎኑ የምንቀበለው ነው፤ ኢፍትሃዊ የሆነውን መታሰራቸውን፣ የስማቸውን መጥፋት ለአካላዊ እና ስነልቦናዊ ጉዳት መዳረጋቸው ፣ ከትምህርት እና ከሥራቸው መስተጓጎላቸው በቤተሰብ እና በወዳጆቻቸው ላይ የደረሰው እንግልት፣ በቸልታ የሚታለፍ ጉዳይ ባይሆንም ከ10 ተከሳሾች መካከል የአምስቱን ክስ መቋረጥ አዎንታዊ እርምጃ ጅምር ነውና ይበልጥ ሊበረታታ ይገባል፡፡ በተመሳሳይ ክስ የቀረበባቸው ቀሪ የዞን ዘጠኝ አባላት ማለትም ሶልያና ሽመልስ ( በሌለችበት) ፣ በፍቃዱ ኃይሉ፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ አቤል ዋበላ እና አጥናፍ ብርሃኔ ከሌሎች ጓደኞቻቸው ተነጥለው እስካሁን መታሰራቸው እና ክሳቸውም አንደሚቀጥል መስማታችን ጉዳዬ አሁንም እጅግ በጣም አሳሳቢ እንደሆነ ያሳያል፡፡
የአምስቱ ክሳቸው የተቋረጠው ጓደኞቻችን ክስ በእርስ ከሚገኙት ጋር ተመሳሳይ በመሆኑ ቀሪ አራት ታሳሪ ጦማርያንን በእስር ለማቆየት የሚሰጥ ማንኛውም ምክንያት ተቀባይነት አይኖረውም፡፡ እኛም በአምስቱ ወዳጆቻችን መፈታት ደስታችንን እየገለጽን አራቱ ቀሪ ጦማርያን እስኪፈቱ ድረስ የዞን9 ጦማርያን ይፈቱ የሚለው ጥያቄያቸን ተጠናክሮ ይቀጥላል፡፡ 
ይህ መልካም ጅምር አገራችን ጠባብ የፓለቲካ ምህዳር እና ዴሞክራሲያዊ መብቶች መታፈናቸውን እንዲቀይር ተጨማሪ የፓለቲካ እና የህሊና እስረኞችን በመፍታት አንዲጠናከር እየጠየቅን ከዚህ የአገሪቱን መልካም ስም ከሚያጠፉ ድርጊቶች መንግስት ራሱን ቆጥቦ ሁሉም ዜጋ የየራሱን አስተዋጽኦ እንዲያበረክት በሩ ክፍት ይሆን ዘንድ አሁንም ማንኳኳታችንን ይቀጥላል፡፡ ለዞን9 ጦማርያን እና ወዳጅ ጋዜጠኛ ቤተሰቦች ጓደኞች እና አጋርነታችን ስታሳዩን ለከረማችሁ ብዙዎች በዚህ አጋጣሚ ከፍተኛ ምስጋናችንን እናቀርባለን ፡፡

የሽብር ክስ የቀረበባቸው እና የተፈቱትም ሆነ አሁንም ክሳቸው ይቀጥላል ተብሎ በእስር የሚገኙ ጓደኞቻችን ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ ሕገ መንግስታዊ መብታቸውን በመጠቀማቸው ብቻ ለእስር የተዳረጉ መሆናቸው ይታወሳል፡፡

አሁንም ስለሚያገባን እንጦምራለን፡፡
ዞን9

No comments:

Post a Comment