Saturday, May 30, 2015

ሥነ-ስርዓት! የአቤል ማስታወሻ ከቅሊንጦ

“they say that time heals all things,they say you can always forget;
but the smiles and the tears across the years
they twist my heart strings yet!”
― George Orwell1984
የመታሰሬ ምክንያት መናገሬ ነው ፡፡ መንግሰት በሬ ወለደ “ሽብር” የሚል ክስ ሳይመስርትብኝ በፊት ይጠይቀኝ የነበረው በማህበረሰብ ሚዲያ የምጽፍበትን የምናገርበት አላማ ነበር፡፡ አላማዬ ተፈጥሮአዊ የመናገር መብቴን ማከናወን አንደሆነ ስናገር ከዚህ ተጨማሪ ሌላ ምክንያት ያለኝ ይመስል የተረፈኝ ድብደባ ነበር ፡፡ በዚህ ሂደት ወትሮም ገመምተኛ የነበረውን ግራ ጆሮዬን አጥቻለሁ፡፡ የሚቆጨኝ ነገር የለም፡፡ የሚያስቆጭ ነገር ካለም መቆጨት ያለብኝ የመናገር ነጻነት ያለውና ያን ነጻነቱን የሚጠቀም ሰው ሆኜ በመፈጠሬ ነው ፡፡

አላማዬ መናገር ነው ፡፡ አላማዬ መማር መማማር፣ ግድየለሽነትን በእውቀት ማስወገድ ነው ፡፡ ይህ አላማዬ ከማንም ያልተቀበልኩት ሰው በመሆኔ ብቻ ያገኘሁት ነው፡፡ ይህንን መሰረታዊ የሰውነት መብቴን ማንም አንዲነፍገው አልፈቅድለትም ፡፡ የመንግሰት ሹመኛ ይሁን ተራ ግለሰብ ፣ ተቋም ይሁን ማህበረሰብ የመናገር መብቴን ልሰጠው አልደራደርም ፡፡
የምናገረው በአደባባይ ፣ በገዛ ቤቴ ፣ በማህበራዊ ሚዲያ በእስር ቤት በፍርድ ቤት በፓሊስ ወንጀል ምርመራ ክፍል በአጠቃላይ በአካባቢዬ ያለውን ግለሰብና ቡድን ሳላውክ በሃላፊነት ነገር ግን በማንኛውም ቦታ ነው ፡፡ ይህንን እነዳላደርግ ቁጣ ፣ ማስፈራሪያ፣ የማሰቃየት ተግባር እስርና ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ  መብቶች መከልከል አላገደኝም ለወደፊትም እንዲያግደኝ አይሆንም ፡፡
ጓደኞቼም ሆነ እኔ አሁን ያለንበትን እስር ማስወገድ እንድንችል ስደትና ሌሎች መንገዶች አንድንመለከት ሥርዓቱ በደህንነት ሰራተኞቹ ጥቆማ ሰጥቶን ነበር፡፡ የመጨረሻዋ ሰአት ስትቃረብ ከልብ የሆነ አእምሮን የሚፈታተን ውይይት አድርገን ነበር፡፡ ከመታሰራችን ቀናት ቀድሞ ሚያዝያ 15/2006 በገጻችን ዞን9 አንዳስነበብነው“ ተፈጥሮአዊና ህገ መንግሰታዊ መብታችንን ማስረከብ “ እጅግ ስለበዛብን የምንከፍለውን ዋጋ እና የስርአቱን ቂመኝነት እያወቅን መናገራችንን አንደምንቀጥል አውስተን ነበር፡፡

የተራዘመው የእስር ጊዜም ይሄንን አቋም አልለወጠውም፡፡ አሁንም መናገር አሁንም ሃሳቤን መግለጽ እፈልጋለሁ፡፡ ይህ ሰው ሆኖ የመወለድ መብት በምንም አይነት ላባክነው አልፈልግም፡፡ግንቦት 19/2007  በዋለው ችሎትም የተፈጸመውም ይሄ ነው፡፡ 

ይህንን ክስ የሚከታተል ሰው ሁሉ አንደሚያውቀው19ኛ ወንጀል ችሎት በቀረብንባቸው ጊዜያት ዳኞቹ ንጽህናችንን የምናረጋግጥበትን እድል የሚያጣብቡ ውሳኔዎቸን መወሰናቸው ፣ የራሳቸውን ውሳኔ መልሰው መካዳቸው ፣ አቃቤ ህግ በቸልተኝነት የፍትህ ሂደቱን አንዲያዘገይ መፍቀዳቸው ፣ ማረሚያ ቤት የሚደርሱብንን የመብት ረገጣዎች ሰምተው አጥጋቢ እርምጃ አለመውሰዳቸው ሳያንስ ከሁሉም የከፋው ደሞ ችሎት ውስጥ እነዳንናገርና ሃሳባችንን እንዳንገልጽ ማፈናቸው ነው ፡፡

ይህንን ተከትሎ መፍትሄ ይሆናል በማለት ሃሳባችንን በችሎት እንዳንገልጽ መታፈናችንን በመግለጽ የመሃል ዳኛው አንዲቀየሩ አቤቱታም አቅርበን ነበር፡፡ ፍርድ ቤቱ ጥያቄያችንን ውድቅ ቢያደርገውም መሃል ዳኛው በራሳቸው ፍቃድ ከእኛ ( ከነሶልያና ሽመልስ) የክስ መዝገብ ራሳቸው አግልያለው ብለው የነበረ ቢሆንም አሁንም ድረስ የሚሰየሙት ራሳቸው ናቸው :: ችሎቱም አንደተለመደው ለአቃቤ ህግ እንደፈቀደ ለእኛም ሆነ ለዳኞቹ ለራሳቸው የማይገቡ ነገሮች የሚናገርበት እኛም አንዳንዴ ካልሆነ በስተቀር እንዳንናገር የምንታፈንበት ሆኖ በኤሊ ፍጥነት እያዘገመ ነው ፡፡

ይህ መዘግየት አንደሚያሳስበን ዳኞቹ የተረዱ አይመስለኝም፡፡ በነጻነት ልናደርጋቸው የምንፈልጋቸው ነገሮች አንዳሉን ከሚወዱንና ከምንወዳቸው ሰዎች እስር ቤቱ አንደነጠለን ዘንግተውታል፡፡
የአገሪትዋን የማረሚያ ቤቶች ሁኔታ እና የማረሚያቤቶቹን የእስረኞች አያያዝ አያውቁት ይመስል፣ እኛ የተፈጠርንበትን የጉድ ዘመንና የምንተውንበት ወለፈንድ ድራማ አስገርሞን ፈገግ ማለታችንን አይተው እስሩ የተመቸን እየመሰላቸው በቀጠሮ ላይ ቀጠሮ መደራረባቸው አግባብ አለመሆኑን መናገር ነበረብኝ ፡፡ መታሰራችን ጤናማ መንፈሳችንን እያደከመ መሆኑን አቃቤ ህግ እስከዛሬ አለኝ ሲል ያልተደመጠውን በድንገት ያመጣውን አንድ ዶክመንተሪ ሲዲ (አንደኛ ተከሳሽ ሶልያና ሽመልስ ላይ የቀረበ) ለማየት ሃያ ቀናት መውሰዱ ፣ በአጭር ቀናት ውስጥ አይተው በፍጥነት ወደቀጣዩ የፍርድሂደት እንድንሄድ አንዲደርጉ ለመግለጽ በፍርድ ቤቱ ሥርአት መሰረት እጄን አውጥቼ አውጥቼ አሳየሁ። አንደተለመደው እነዳንናገር ዳኞቹ እቀባ በማድረግ የመሰማት እድላችንን ነፈጉን ፡፡ ለመናገር ፍቃድ ስንከለከል ሳይፈቀድልን መናገር ጀመርን ፡፡ “ የምጣዱ ሳለ የእንቅቡ ተንጣጣ” አንዲል ያገሬ ሰው ተበድለን በተናገርን “ስነስርአት አድርጉ” የሚል ትእዛዝ ከዳኞቹ መጣ፡፡ በዚህ ሰአት “እናንተ ራሳችሁ ሥነ-ስርዓት አድረጉ” በማለት ስርአት አልበኛ የሆነው የንጹሃን ዜጎችን መብት ለማፈን የተዘጋጁት እነሱ መሆናቸውን ተናግሬያለሁ፡፡ ይህንን ስናገር ስሜት ተጭኖኝ ይሆናል፡፡ ነገር ግን በዚያ ችሎት የሚፈጸመውን በደል ትውልድ እንዲረዳው ታሪክም መዝግቦ አንዲያቆየው መዘከር ነበረብኝ፡፡
ጦማሪ አቤል ዋበላ

ሥነስርዓት ምን እንደሆነ አውቃለሁ፡፡ ወላጆቼ በገባቸው መጠን ጥብቅ በሆነ ስነስርዓት አሳድገውኛል፡፡ ይህ ታላቅን ብቻ ሳይሆን ታናሽንም ማክበር አንደሚገባ ሥነ-ስርዓትና ደንቦችን መጣስ አንደማይገባ ይጨምራል፡፡ ( በሁለት አመት የዞን9ሥራቸንም ለማንኛውም የአገሪቷንህግ ሳንጥስ ህጋዊ ሆነን የቆየነው ለዚያምጭምር ነው ) ነገር ግን መታፈንን በጻጋ መቀበልና በደልን መሸከምን አይጨምርም፡፡ የማንም ሰብአዊ መብት ተሟጋች ወይም ነጸ አውጪአይደለሁም ፡፡ የግለሰብ መብቴ ሲነካ ግን ዝም ማለት አልወድም ፡፡ በተለይም ደግሞ ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብቴ አንዲከለከልአልፈልግም ፡፡ ስለዚህም ይህንነ ከዚህ በፌት ላደረገ ፣ ከአሁን በማድረግ ላይ ያለ ፣ ወደፌትም ለማድረግ የሚያስብን ሁሉ አስጠነቅቃለሁ………….ሥነ-ስርዓት !!

2 comments:

  1. የማንም ሰብአዊ መብት ተሟጋች ወይም ነጸ አውጪአይደለሁም ፡፡ የግለሰብ መብቴ ሲነካ ግን ዝም ማለት አልወድም ፡፡ በተለይም ደግሞ ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብቴ አንዲከለከልአልፈልግም ፡፡ ስለዚህም ይህንነ ከዚህ በፌት ላደረገ ፣ ከአሁን በማድረግ ላይ ያለ ፣ ወደፌትም ለማድረግ የሚያስብን ሁሉ አስጠነቅቃለሁ………….ሥነ-ስርዓት !!

    ReplyDelete
    Replies
    1. Your right is given by creater or God government doesn't give you your rights

      Delete