Thursday, May 28, 2015

የጦማርያኑ እና የጋዜጠኞቹ የሃያ ዘጠነኛ የፍርድ ቤት ውሎ

ከትላንትና ወዲያ በምሰክሮች እና ሲዲ ውዝግብ በይደር ተቀጥሮ የነበረው የነሶልያና ሽመልስ የክስ መዝግብ የፍርድ ቤት ውሎ ትላንትናም በተለያዬ ድራማዎች ታጅቦ ለግንቦት 25 እና ለሰኔ 8 ተቀጥሯል፡፡
የፍርድ ቤቱ ብይን
ፍርድ ቤቱ በ29ኛ ቀጠሮው ተጨማሪ ምስክሮችን ለመስማት እና ሲዲ ማስረጃዎች ላይ ብይን ለመስጠት የነበረ ሲሆን በዚህም መሰረት
1. የሲዲ ማስረጃ ተብለው አቃቤ ህግ በተደጋጋሚ የሚያነሳቸው ነገር ግን በስተመጨረሻ ከኮምፒውተር ላይ የሰነድ ማስረጃዎቸን ለመገልበጥ ብቻ የተጠቀምኩባቸው ናቸው ያላቸውን ሲዲዎች የኤግዚቢትም የሰነድም ማስረጃ ስላልሆኑ ሙሉ ለሙሉ አንዲሰረዙ ሲል ፍርድ ቤቱ ወስኗል፡፡ አቃቤ ህግ ከመጀመሪያው የማስረጃ መስማት ሂደት አንስቶ እስከ 28ተኛው ቀጠሮ ድረስ አንዴ ባለሞያዎች የሉም ሌላ ጊዜ የወንጀሉ ኤግዚቢት ናቸው ሲላቸው የከረሙትን ሲዲዎች በስተመጨረሻ ምንም አይነት የተለየ ይዘት ያላቸው ሲዲዎች የሉኝም ሲል አምኗል፡፡ እነዚህ ሲዲዎችን አስመልክቶ ብቻ ትንሽ የማይባሉ ቀጠሮዎች መሰጠታቸው ከዚያም በተጨማሪ የጦማርያኑ እና የጋዜጠኞቹ እነዲሁም የጠበቆች እና የፍርድ ቤቱ ጊዜ እና ጉልበት መባከኑ ይታወቃል፡፡
2. አቃቤ ህግ የጠየቀውን ተጨማሪ ምስክሮች ተፈልገው አንዲመጡ ጊዜ ይሰጠኝ ያለውን ጥያቄ አስመልክቶ ምስክሮቹ አሁንም የደረጃ ምስክሮች በመሆናቸው እቃ ሲፈተሽ አይተናል ከማለት ውጪ ስለማይመሰክሩ አቃቤ ህግም በተደጋጋሚ በፍርድ ቤቱ እድል ተሰጥቶት ምንም የተለየ ምስክር ሊያቀርብ ባለመቻሉ ተጨማሪ ምስክሮችን ለማቅረብ ተጨማሪ ቀጠሮ አይሰጠውም በማለት የምስክሮቹን ጉዳይ ፍርድ ቤቱ ዘግቶታል፡፡
አንደኛ ተከሳሽ ሶልያና ሽመልስን የተመለከተ ማስረጃ
አቃቤ ህግ እስካሁን ምንም ሳይል የቆየባት አንደኛ ተከሳሽ ሶልያና ሽመልስን በተመለከተ በትናንትናው የፍርድ ቤት ውሎ ማጠቃለያ ላይ አንድ ዶክሜንተሪ የያዘ ሲ.ዲ በማስረጃነት ማቅረቡን ገልጾ ፍርድ ቤቱ እንዲመለከተው ማመልከቱ ይታወሳል፡፡ ይህን የሲ.ዲ ማስረጃ በተመለከተ በ29ኛው ችሎት ቀጠሮ ብይን የተሰጠ ሲሆን፣ በብይኑ መሰረትም ትላንትና ከሰዓት በኋላ አቃቤ ህግ ሲ.ዲውን በጽ/ቤት በኩል እንዲያስገባ ታዝዟል፡፡ ፍርድ ቤቱ ጨምሮ እንደገለጸው በአንደኛ ተከሳሽ ላይ የቀረበውን ዶክሜንተሪ በቢሮ ዳኞቹ እንዲመለከቱት ከተደረገ በኋላ ሲ.ዲው ሌሎችን ተከሳሾች ይመለከታል ወይስ አይመለከትም የሚለውን አይቶ ብይን የሚሰጥ ይሆናል፤ ብይኑን ለመስጠትም ለሰኔ 8/2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ በተጨማሪም ሲ.ዲው የያዘው ዶክሜንተሪ በግልጽ ቢታይ የሚያስከትለው ጉዳት አለ ወይስ የለም የሚለውንም ፍርድ ቤቱ ብይን እንደሚሰጥበት ይጠበቃል፡፡ አቃቤ ህግ በቀደመው ችሎት አንደኛ ተከሳሽ አመጽ ስታነሳሳ የሚያሳይ ዶክመንተሪ ሲዲ አለኝ ማለቱ ይታወሳል፡፡
አቃቤ ሀግ ጠበቆች ላይ ያቀረበው አቤቱታ
አቃቤ ህግ በዚሁ ችሎት ጠበቆች የፍርድ ቤቱን ውሎ አስመልክቶ የሚሰጡትን አስተያየት የአንድ ወገን አስተያት ከመሆኑም በላይ የፍርድ ሂደቱን ተጽእኖ ሊያመጣ ይችላል የሚል በቤቱታ አቅርቧል፡፡
ጠበቃ አምሃ መኮንን በበኩላቸው አቃቤ ሀግ እዚህ አንድ ተከራካሪ ወገን አንጂ የሂደቱ አዛዥ አለመሆኑን በተጨማሪም ግድፈት ካለ የተጣሰውን ህግ ግድፈት በጽሁፍ አቤቱታ ማቅረብ አንደሚችል ከዚያ ውጪ ግን በግልጽ የተሰየመውን ችሎት ከአገር ቤት እስከአለም አቀፍ ሚዲያዎች በዝርዝር አንደሚዘግቡትና የጠበቃው አስተያየትም ከዚህ የተለየ አንዳልሆነ ገልጸዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ በበኩሉ ‹‹የተሰጠው አስተያየት አቃቤ ህግ በሰጠው ቃል መሰረት ተፈጽሞ ከሆነ ስህተት ስለሆነ ሊስተካከል ይገባል›› በሚል ማሳሰቢያ ብቻ አልፎታል፡፡
በፍርድ ቤትም ውስጥ የታፈነው የተከሳሾቹ ድምጽ
ብይኑ መሰማት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ በተደጋጋሚ ጥያቄ ለመጠየቅ ሲጠይቁ የነበሩት ተከሳሾች በፍርድ ቤቱ እድል አልተጣቸውም ፡፡ በተለይም የአቶ አመሃን የሚዲያ አስተያት ተከትሎ
ጦማሪ ናትናኤል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሳይቀር በተከሳሾች ላይ የወንጀለኛነት ንግግር ሲያደርጉ መደመጣቸውን በማስታወስ የፍርድ ቤቱ ማሳሰቢያ ለእሳቸውም ይሁን በማለት ንግግሩን ለማብራራት ሲሞክር ፍርድ ቤቱ ‹‹ይሄ የአቶ አምሃ ጉዳይ እንጂ እናንተን አያገባችሁም›› በሚል አቋርጦታል፡፡ ጦማሪ ዘላለም ክብረትም አንዲሁም ጋዜጠኛ አስማመው ሃይለጊዬርጊስ በተመሳሳይ ሀሳቡን ለመግለጽ ጠይቀው ተከልክለዋል፡፡ ጦማሪ ናትናኤል ፍርድ ቤቱ ሳይፈቅድለት ተናግሯል ወደጎንም ዞሮ አውርቷል በማለት ፍርድ ቤቱ ለጥያቄ አንዲነሳ ሲታዘዝ የናትናኤል ጥያቄ የሁላችንም ጥያቄ ነው በማለት ሁሉም ተከሰሶች አብረውት ተነስተዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ሎሎቹ ተከሳሾ አንዲቀመጡ ቢያሳስብም አንቀመጥም በማለት አብረውት ቆመዋል፡፡
ናትናኤል መናገር ሲከለከል ‹‹ከአሁን በፊትም ሀሳባችን እንዳንገልጽ ገደብ ባደረጉብን ዳኛ ላይ አቤቱታ ማሰማታችን ይታወሳል፡፡ ህገ መንገስታዊ መብታችንን አክብሩ...ሀሳባችንን እንግለጽ›› ሲል ተናግሯል፡፡ ፍርድ ቤቱ ግን ንግግሩን አስቁሞ በመሐል ዳኛው አማካኝነት ‹‹ወዳልሆነ ነገር አታስገቡን›› ሲል ዛቻ መሰል ማሳሰቢያ ሰጥቷል፡፡
በዚህ ያላበቃው የተከሳሾችና የፍርድ ቤቱ ውዝግብ ጦማሪ አቤል አሁንም ለመናገር አድሉ አንዲሰየው ሲጠይቅ " ስነስርአት ያዙ " በማለት ፍርድ ቤቱ በመከልከሉ ጦማሪ አቤል " እኛ ብቻ ሳንሆን ራሳችሁም ስነስርአት አድርጉ ጥያቄ አለን ሰምታችሁ ምላሽ ስጡን" በማለት ምላሽ ሰጥቷል፡፡ ይህንን ምላሹን ፍርድ ቤቱ ችሎት መድፈር ነው ብሎታል፡፡ ይህንን ተከትሎ ጠበቆች ጣልቃ በመግባት ደንበኞቻቸው አንዲደመጡ ፍርድ ቤቱን በማሳሰብ አቤልም ይህን እድል በመነፈጉ በስሜታዊነት የተናገረው በመሆኑ በተግሳጽ አንዲታለፍ ጠይቀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ አቤልን በዚህ የጠበቃው ሃሳብ ይስማማ እነደሆነ ሲጠየቅ የጠየቁት መብቴን ነው የምጠይቀው ይቅርታ የለም በማለቱ የችሎት መድፈሩን አስመልክቶ ውሳኔ ለመስጠት ለግንቦት 25 ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ይህንን ተከትሎ የአቤል ሀሳብ የሁላችንም ሃሳብ ስለሆነ ሁላችነም በዚያ ቀን ልንቀርብ ይገባል የሚል አቤቱታ ሁሉም ተከሳሾች ቢያሰሙም ፍርድ ቤቱ ፓሊስን አንዲያስወጣቸው በመታዘዙ ችሎቱ ወጥተዋል፡፡ በኋላ ከተከሳሾች ጠበቆች አንደገለጹት የጦማሪ አቤል ጥያቄ አንደኛ ተከሳሽ ሶልያና ሽመልስ ላይ የሚቀርበው የተባለውን የዶክመንተሪ ማስረጃ ሎሎች ተከሳሾችም አንዲያዩት ለመጠየቅ ነበር ፡፡
የዞን 9 ማስታወሻ
1. ዘግይቶም ቢሆን የተወሰደውን የፍርድ ቤቱን የሲዲ ማስረጃዎቸን መሰረዝ አንዲሁም ለአቃቤ ህግ ተጨማሪ ጊዜ አለመስጠት ውሳኔ እናበረታታለን ፡፡ ይህ ውሳኔ ከሶስት ቀጠሮ አስቀድሞ መወሰድና የጓደኞቻችን የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብት ሊከበር ቢገባውም አሁንም ቢሆን ከመቅረት ይሻላል ፡፡ ፍርድ ቤቱም ይህንን መሳይ ፈጣን ምላሾችን በመስጠት ጓደኞቻችን ጦማርያን እና ጋዜጠኞች መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነጻ ማሰናበት የሚቀጥለው ብይን ሊሆን ይገባል፡፡ ያልተሰራ ወንጀል ምስክርም ሆነ ማስረጃ ለአመታት ቢፈለግም አይገኝለትም ፡፡
2. ፍርድ ቤት ውስጥ ያለውን ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት አሁንም አሳሳቢ ነው ፡፡ ተከሳሾች ሃሳባቸውን አንዲሰጡ መፍቀድ አንድ ገለልተኛ ፍርድ ቤት ለተከሳሾች ሊሰጠው የሚገባ መሰረታዊ መብት ሆኖ ሳለ ተከሳሾች ይህንን መብት በተደጋጋሚ መነፈጋቸው ከዚም አልፎ ይህንን መብት በመጠየቃቸው ችሎትን አንደደፈሩ መቆጠሩ በጣም አሳዛኝ ነው፡። የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች እንኳን አሁን ታስረንና ተሰደን መስዋእትነት እየከፈልንበት እያሉ ቀርቶ ቀድሞም ሃሳብን የነጻነት የመግለጽ መብት የማይቀየር ቋሚ እሴታችን አንደሆነ ይታወቃል፡፡ ፍርድ ቤቶች ይህንን ቀላል መብት መንፈጋቸው ደግሞ የተለመደውን የስራ አስፈጻሚው አካልነታቸው ሃሜት የሚያጠናክር ከመሆን ውጪ ሌላ ፋይዳ የለውም ፡፡
አሁንም ስለሚያገባን እንጦምራለን!
ዞን9
ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ እና ጦማሪ ማህሌት ፋንታሁን

No comments:

Post a Comment