ይህ ጽሑፍ ባለፈው ወር በአዲስ
አበባ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ውስጥ በብሔር ሰበብ በተነሳ ፀብ ላይ ተመስርተው በተከታታይ ድረገጾች ላይ የተጻፉ ጽሑፎች መነሻነት የተጻፈ
ማጠናከሪያ ሐተታ ነው፡፡ ስለሆነም እዚህ ውስጥ የተበታተኑት የሰዎቹ ውይይት አጽርኆት (summary) እና ተጨማሪ ሐሳቦች ይንፀባረቃሉ፡፡
ጃዋር መሐመድ
(የፖለቲካ ተንታኝ) ነበር ውይይቱን የጀመረው፤ በጽሑፉ ‹‹ዩኒቨርሲቲዎች ነጻ መንፈስ ተኮትኩቶ የሚያድግባቸው፣ እልፍ ገጽታ ያላቸውን
ችግሮቻችን ለመፍታት የሚያስችሉ አዳዲስ ሐሳቦች የሚፈልቁበት የላቀ እና ገንቢ ውይይቶች የሚካሔዱባቸው ቦታዎች መሆን ይገባቸዋል፡፡
በተቃራኒው ግን፣ የኢትዮጵያ ኮሌጆች የዘረኝነት፣ ጠባብነት እና አመጽ መፈልፈያ እየሆኑ ነው፡፡›› ይላል፡፡
እኔም በዚህ
ጽሑፍ ይህንኑ ጉዳይ ከታሪክ እና ከወቅታዊ ጉዳዮች አንጻር እመላለስበታለሁ፡፡
ለመሆኑ መቼ እና በማን ተጀመረ?
የኢትዮጵያ ዩኒቨርሲቲዎች
ዕድሜ አጭር በመሆኑ ብሔር-ነክ ግጭቶች መቼ እንደተጀመሩ የሚዘረዝር መረጃ ማግኘት ቢቸግርም እንኳን ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዩኒቨርሲቲ
(የአሁኑ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ) እንደሆነ መገመት አይቸግርም፡፡ ሆኖም በቅርቡ በጆን ያንግ የተጻፈ፣ Peasants
Revolution of Ethiopia የሚል ርዕስ ያለውን መጽሐፍ ሳገላብጥ ያገኘሁት አንቀጽ አጀማመሩን የሚገልጽ መስሎኝ ወስጄዋለሁ፡፡
“…ዊንጌት ውስጥ … በአሁኑ ጠቅላይ
ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የሚመሩ የትግራይ ተወላጅ ተማሪዎች በቅርጫት ኳስ ጨዋታ ላይ በተነሳ አለመግባባት ከኦሮሞ ተወላጆች ጋር ተጋጩ፡፡
ከዚያ ቀጥሎ መለስ በጣም አወዛጋቢ የነበረውን እና በአድዋ ጦርነት ወቅት የትግራይ ተወላጆች ከየትኛውም ብሔረሰብ የበለጠ የሕይወት
እና የሰው ኃይል ከፍለዋል፣ ምኒልክንም ለድል አብቅተዋል የሚል የታሪክ ጽሑፍ አቀረቡ…” (ገጽ 82) እያለ ይቀጥላል፡፡