Saturday, April 27, 2013

“የተዘነጉት እስረኞች” እና የተዘነጋው የቤተሰቦቻቸው ስቃይ


ላለፉት አራት ዓመታት ቃሊቲ ማረሚያ ቤት ቅዳሜ እና እሁድ የሄደ ሰው ወጣቷን ናርዶስን ሳያገኝ አይመለስም፡፡ ናርዶስ ገና የ20 ዓመት ወጣት እና በኪያሜድ የመጀመሪያ ዓመት የነርሲንግ ተማሪ ናት፡፡ ናርዶስ ዘሪሁን በየሳምንቱ  ቃሊቲ ማረሚያ ቤት የምትመላለሰው በ‹‹አሸባሪነት›› ‹በእነብርጋዴር ጄኔራል ተፈራ ማሞ መዝገብ› ከተከሰሱት 36 ሰዎች መካከል ዕድሜ ልክ የተፈረደባትን እናቷን ልትጎበኝ ነው፡፡ እነዚህ እስረኞች ሚያዝያ 16/2001 አመሻሹ 12 ሰዓት አካባቢ ነበር ሁሉም በያሉበት በቁጥጥር ስር የዋሉት፡፡ እኛም 4ኛ ዓመታቸውን ለማሰብ ተሰባስበን ወደቃሊቲ ማረሚያ ቤት በተለይ እማዋይሽ ዓለሙን ለመጠየቅ ሄደን ነበር፡፡ እንደተለመደው ናርዶስንም አገኘናት እና ብዙ ነገሮችን አጫወተችን፡፡

ናርዶስ ትረካዋን  የጀመረችው እናቷን እና ሌሎችም በተመሳሳይ መዝገብ ተከሰው የተፈረደባቸውን ሰዎች አያያዝ ነበር፡፡ ‹‹ሳስበው የተረሱ ያህል እየተሰማኝ ነው፤ ምክንያቱም ብዙ ጊዜ ሚዲያዎች ስለነሱ አይደለም እያነሱ ያሉት፡፡ በእናቴ ክስ የታሰሩት ከ30 ሰዎች በላይ ናቸው፡፡ አንድ ሰሞን ከይቅርታ ጋር በተያያዘ ስማቸው እየተነሳ ነበር አሁን ግን ሁሉ ነገር የተረሳ ይመስለኛል›› በማለት የእስሩ ሕመም ለታሳሪዎቹ እና ለቤተሰቦቻቸው ግን የሚረሳ ዓይነት አለመሆኑን ነገረችን፡፡

‹‹ሚያዝያ 16፣ አርብ ቀን ነበር ሁሉም የተያዙት›› በማለት ሲታሰሩ የነበረውን ጠቅላላ ሁኔታ በማስታወስ ትጀምራለች፡፡ ‹‹ለአንድ ሰው የመጡ የማይመስሉ ብዙ ሲቪል የለበሱ እና የፌዴራል ፖሊስ ልብስ የለበሱ ፖሊሶች መሳሪያቸውን አቀባብለው ነበር ወደቤት የገቡት፡፡ ስልካችሁን አጥፉ ወደማንም እንዳትደውሉ አሉን፡፡ የብርበራ ማዘዣ ይዘው ነበር፤ ‹ቤት ልንፈትሽ ነው የመጣነው እማዋይሽ ዓለሙ በቁጥጥር ስር ውለሻል› አሏት ቤት ፍተሻው እስከ ምሽቱ አራት ሰዓት ድረስ ቀጥሏል፡፡ ቀኑ አርብ ነበር፤ እናቴ ደግሞ እስከ 12 ሰዓት ትጾም ስለነበር ከሥራ ወደቤት እንደገባች ‹ምግብ ስጡኝ› እያለች እያለ ነበር ፖሊሶች የገቡት ስለዚህ ምግብ ሳትበላ ውላ ነው ወደ እስር ቤት የወሰዷት፡፡ ከዚያ በኋላ አራት ወራት ያክል ዓይኗን አላየነውም ነበር፤ ትሙት ትኑር የምናውቀው ነገር አልነበረም፡፡  ደግነቱ በሌላ ጉዳይ ታስራ በተፈታች ሴት አማካይነት መልዕክት ደረሰኝ፡፡ ‹አንቺ ደህና ከሆንሽ ሽሮ እና ጎመን ሰርተሸ አስገቢልኝ፤ እኔ ደግሞ ደኅንነቴነን የባናና ማስቲካ ወረቀት እልክልሻለሁ፡፡ ደኅና ካልሆንኩኝ ግን ያ ነገር ይቀራል› ብላ ላከችብኝ፡፡ ከዚያ እኔም ሽሮ እና ጎመን ሠርቼ በመላክ፣ እሷም የባናና ወረቀት በመላክ ደኅንነታችንን የሚገልፅ መልዕክት እንለዋወጥ ነበር፡፡ ይህ ሁሉ እየሆነ ባለበት ሰዓት እኛ በሌለንበት ጉዳያቸው ፍርድቤት ይታይ ነበር፡፡›› በማለት ጉዳያቸው በኢፍትሐዊ መንገድ በመንግሥት እንደተያዘ አጫውታናለች፡፡


‹‹እናቴ ስዕል መሳል ትወዳለች፡፡ እናም በየጊዜው የጀመረቻቸው ስዕሎች የተበላሹ ሲመስሏት ቅርጫት ውስጥ ትጥላቸዋለች፡፡ ይመስለኛል፤  የቤት ሠራተኛችን እጅ አለበት፡፡ ስትታሰር የቀረበባት መረጃ እነዚህ የተጣሉ ወረቀቶች ተሰብስበው ‹የድርጅቱን አርማ ስታዘጋጅ ነው› የሚል ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ ፈቃድ የነበረው፣ ያውም የማይሠራ ሽጉጥም እንዲሁ በማስረጃነት የቀረበባት መሆኑ ነው፡፡›› በማለት ለእርሷ ፍርዱ ፍትሐዊ አለመሆኑን እና እናቷም ነጻ መሆኗን እንደምታምን ነግራናለች፡፡

‹‹የሚያሳዝነው ነገር ደግሞ ሲታሰሩ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የተላለፈው ዜና ነው፤ እንኳን አገር ወዳዷ እናቴ ማንም ባገሩ ላይ የሚያደርገውን ነገር ነው አደረጉ ያለው፤›› የዜናውን ፖለቲካዊ ወገንተኝነት ወቅሳለች፡፡ እናቷ ሕዝብና አገር የማሸበር ፍላጎት ሊኖራት ለአገር ፍቅር ሕይወቷን የሰጠች መሆኗን ስታጫውተን ‹‹እናቴ ሁልጊዜ የምትነግረኝ ነገር አለ፤ ሕይወቴ ማለፍ ካለበት አገሬን በሚጠቅም ነገር መሆን አለበት ትለኝ ነበር፤›› ብላናለች፡፡ ነገር ግን መንግሥት በአንድ በኩል ‹‹ሕገ መንግሥቱን ለመናድ በመሞከር ነው ያሰርኳችሁ እያለ በሌላ በኩል ደግሞ የፖለቲካ እስረኞች የሉኝም ይላል፤›› ካለች በኋላ ‹‹ተቃዋሚ መባላቸው ካልቀረ የኢሕአዴግ መንግሥት የፖለቲካ እስረኞች እንደሆኑ ቢያምን  እንኳ ጥሩ ነው፤›› ብላናለች፡፡ ‹‹እናቴ ለአገሯ ከማንም  በላይ ሠርታለች ብዬ አምናለሁ፡፡ ነገር ግን አገራችን ለእናቴ ውለታዋን እየከፈለቻት ነው ብዬ አላምንም፡፡ ያለሃጢያታቸው ሃጢያት ተሰጥቷቸው ነው ያሉት›› በማለት ፍርዱ አገር ወዳድ እናቷን የሚያዋርድ እንደሆነ በሐዘን  ተርካልናለች፡፡

የእናቷ በአሸባሪነት መፈረጅ ለናርዶስ ማኅበራዊ እና ስነልቦናዊ ቀውስ እያደረሰባት መሆኑንም አጫውታናለች፡፡ ‹‹ለትምህርቴ መስጠት የሚገባኝ ጊዜ ያህል መስጠት አልቻልኩም፤ እናቴ የታሰረችው እኔ ስምንተኛ ክፍል እያለሁ ነበር፡፡ ዩንቨርስቲ መግባት ሲኖርብኝ አሁን ግን ‹ነርሲንግ› እየተማርኩ ያለሁት በዚሁ ተፅዕኖ ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ የእነርሱን የእስር ዜና ኢቲቪ ከአቀረበበት መንገድ አኳያ ትምህርት ቤት ውስጥ ራሱ እኔን መቅረብ የሚፈሩ ሰዎች አሉ፤› በማለት የእናቷ እስር በእርሷ ማኅበራዊ ሕይወቷ ላይ ያጠላበትን ጥላ አጫውታናለች፡፡

‹‹እስጢፋኖስ አካባቢ የሚገኘው እና በእናቴ ስም  ተይዞ የነበረው የቀበሌ ቤታችን በልማት ስም ሲፈርስ እንኳን ለጎረቤቶቻችን በምትኩ ሲሰጣቸው ለእኛ ግን አልተሰጠንም፡፡ ሌላው ቀርቶ መታወቂያ እንኳን ለኛ ለመስጠት ፈቃደኞች አይደሉም›› ቤታቸውን ካፈረሱባቸው በኋላ አክስቷ ጋር እየኖረች እንደሆነ ስትነግረን በየመሐሉ እየገታችው ታወራልን የነበረው እምባዋ ከቁጥጥር ውጪ ሆኖ ሲወርድ ማድረግ የቻልነው ነገር ቢኖር በዝምታ ማጀብ ነበር፡፡   

‹‹ያለአባት ያሳደገችኝን የእናቴን ፍቅሯን አልጠገብኩትም›› የምትለን ናርዶስ ‹‹በዚህ ዕድሜዬ ለኔ የሚገባኝ ቦታ ቃሊቲ አልነበረም፡፡›› በማለት ብዙ ነገር መሥራት በነበረባት ጊዜ ቃሊቲ በመመላለስ እንዲባክን መንግሥት እንደፈረደባት እንደሚሰማት ነግራናለች፡፡ ‹‹አራት ዓመቱን  በአሰቃቂ ሁኔታ ነው ያሳለፍኩት፤ ከ16 ዓመታት በኋላ ከእስር የተፈታው አባቴ የራሱን ሁሉ ነገር ትቶ ሕይወቱን ለኔ መስዋዕት ባያደርግ ኖሮ አልወጣውም ነበር›› በማለት እንደዕድል እናቷ ከመታሰሯ ሁለት ወር ያክል ቀድሞ በተፈታው አባቷ ድጋፍ ከብዙ ቀውስ እንደተረፈች እየነገረችን ከናቷ ጋር የነበራትን ፍቅር ‹‹እናቴ ሁለ ነገሬ ነች!›› ብላለች፡፡

‹‹እናቴን ሊጎዳ የሚያስብ ሰው እኔን  አንድ ነገር ሊያደርግ ይችላል በሚል ተሳቅቄ ነው የምኖረው›› በማለት በዙሪያዋ ያለውን ወዳጅ እና ጠላት እንኳን ማመን እየቸገራት እሷ ራሷም ቢሆን ከማኅበረሰብ የመነጠል እና የመስጋት ስነልቦናዊ ችግር ውስጥ እንደሆነች አስረድታናለች፡፡

‹‹የርዕዮትዓለሙ እህት እስከዳር ዓለሙ ‹የቤታችን ሰላም እና ፍቅር ከርዕዮት ዓለሙ ጋር ታስሯል› ያለችው በጣም ትክክል  ነው›› በማለት በታሰሩት ሰዎች ቁጥር እኩል የሚሆኑ ቤተሰቦች በከፍተኛ ፈተና ውስጥ እያለፉ መሆኑን አበክራ ነግራናለች፡፡

የናርዶስ  ታሪክ የብቻዋ ታሪክ አይደለም፡፡ የሌሎች የብዙ ቤተሰቦቻቸው የታሰሩባቸው ቤተሰቦች ታሪክ ነው፡፡ ናርዶስም ‹‹እንደኔ ሁሉ ችግር ላይ ያሉ፣ አባቶቻቸው የታሰሩባቸው ብዙ ልጆች አሉ›› ብላናለች፡፡ በዚሁ መዝገብ ተከሰው የሞት ፍርድ የተፈረደባቸው አቶ መላኩ ተፈራ ቤተሰቦችም ከሰኞ እስከ እሁድ ቃሊቲ ደጃፍ ላይ ከማይጠፉት ሰዎች ውስጥ ይመደባሉ፡፡ በሥራ ጉዳይ ከአገር ውጪ ያለችው ልጃቸው ፅዮንም አባቷን ለመጎብኘት ሲባል ቶሎ፣ ቶሎ እንድትመላለስ ተገድዳለች፡፡ እነጄኔራል ተፈራ ማሞ፣ እነአሳምነው  ፅጌ እና ሌሎችም ደግሞ በእስረኞች መሐል ‹‹ተነስቷል በሚል ፀብ›› ሰበብ ከቃሊቲ ማረሚያ ቤት ወደዝዋይ እንዲዛወሩ ተደርገዋል፡፡ ይህ ከቤተሰቦቻቸው ጋር እንዳይገናኙ ሌላ ተጨማሪ ጫና አሳድሮባቸዋል ብላናለች፡፡ እዚህ የቀሩት ታሳሪዎችም አጋሮቻቸውን በማጣት ለብቸኝነት ስሜት ተዳርገዋል፡፡

ከነርሱ መዝገብ ውጪ ያሉ ሌሎችም እስረኞች እና ቤተሰቦቻቸው በተመሳሳይ ፈተና ውስጥ መሆናቸውን እስረኞችን ለመጎብኘት በሄድንባቸው ጊዜያት ተረድተናል፡፡ መንግሥት ለፖለቲካ ግብአቱ የይቅርታ ደብዳቤ ካስፈረማቸው በኋላ እንኳን ለመፍታት ፍላጎት አያሳይም፡፡ ይልቁንም፤ ከቦታ ቦታ እያዘዋወረ ስቃያቸውን ያበዛል፡፡ ለዚህ እንደምሳሌ ባለፈው አርብ (ሚያዝያ 11/2005) ወደዝዋይ እንዲዘዋወር የተደረገው ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ ተጠቃሽ ነው፡፡ በእርሱ የጋዜጠኝነት ደሞዝ ላይ ጥገኛ የነበሩት ባለቤቱ እና ልጁ (ፍትሕ ውብሸት) በእናትዬው መፍጨርጨር ሕይወታቸውን እንዲመሩ ከመገደዳቸውም በላይ አሁን የቤቱን አባውራ ለመጠየቅ ዝዋይ ድረስ እንዲመላለሱ ተፈርዶባቸዋል፡፡ ለዚህም ነው መንግሥት የፖለቲካ አይደሉም የሚላቸውን የፖለቲካ እስረኞችን ከነቤተሰቦቻቸው ከሚቀጣበት መንገድ ይታረም ዘንድ ሊጠየቅ ይገባዋል በማለት የምንመክረው፡፡
----
ይህ ጽሑፍ ዕንቁ መጽሔት ላይ ታትሟል!

No comments:

Post a Comment