Thursday, January 3, 2013

ምሁርነት እና ምሁር



በተለያዩ የሀገራችን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ አንድ የተለመደ አባባልን ማስተዋል የተለመደ ነው፤ ‹በምሑራን* ተሳትፎ የኢትዮጵያን ሕዳሴ እናረጋግጣለን› የሚል ፅሁፍ በሕዳሴው ግድብ ፎቶ ታጅቦ፡፡ ቃላቶቹ ከተሰቀለበት ቦታ አንፃር ስንመለከተው ምሁሩ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ መሽጓል፤ ሕዳሴውንም ‹በምሑሩ› ፊት አውራሪት ይረጋገጣል የሚል አንድምታ እንዳለው መረዳትም ብዙም አይከብድም፡፡

በርግጥ ምሁሩ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ አለን? ኧረ እንዲያውም ምሁር በአጠቃላይ በሀገራችን አሉ ወይ? እያልን እንጠይቅ ዘንድ ፈቀድን፡፡

ምሁር ስንል

በተለያዩ ወቅቶች እና ቦታዎች መታዘብ እንደምንችለው ‹ምሁር› የሚለው ስያሜ በሀገራችን ተለጥጦ ፊደል የቆረን ሁሉ አካትቶ ይዟል፡፡ ኮሌጅ የበጠሰ ሰውማ የሊቀ-ሊቃውንትነት ካባን ይደርባል፡፡ እዚህ ላይ በመጀመሪያ የምናገኝው ችግር ምሁርን (Intellectual) ከባለሙያ (Professional) መደባለቅን ነው፡፡ ባለሙያ የሚለውን ማዕረግ ከሳቴ ብርሃን የአማረኛ መዝገበ ቃላት ‹‹ሥራን ዐዋቂ መኾን ልዩ ልዩ የትምህርት ሥራን የእጅ ሥራ ጥበብን ማወቅ ወይንም ያንድ ቀን ሥራን ሠርቶ ደመወዝን ማግኘት።›› በማለት የተወሰነ ስራን መስራት እና ምንዳን እንደ ምላሽ ማግኝት (Quid Pro Quo) በማለት ሲያቀርብ፡፡ ምሁር የሚለውን ስያሜ ደግሞከፍተኛ የሆነ የማሰብና የመመራመር ችሎታ ያለው፤ ሊቅ የተማረ በኹሉ ምሉ ትምህርት ያለው ሰው› ብሎ ሰፊ ደርዝ በማስያዝ ምሁርነት ከፍ ያለ ጉዳይ እንደሆነ ያሰረዳል፡፡

Robert Roberts እና Jay Wood ‹Intellectual Virtues› ባሉት መፅሃፋቸው አንድ ምሁር ሊኖረው ስለሚገባው መሰጠቶች (Virtues) አብዝተው ይተነትናሉ እንደ ፀሃፊያኑ ገለፃም ምሁር፤ ምሁር ለመባልም እውቀትን የመሻት (Love of Knowledge) ፀናኢነት (Firmness)፣ ልበ ሙሉነት( Courage)፣ ቀናኢነት (Humility)፣ ነፃነት (Autonomy)፣ ደግነት (Generosity)፣ እና በሳት የፈተነ ጥበብን (Practical Wisdom) መታደል ይኖርበታል በማለት፤ የምሁርነት ተራራ ብዙ ነገሮችን ያቀፈ መሆን እንዳለበት ይናገራሉ፡፡

እንግዲህ የአፍላጦኗ (Plato) ሀገረ-መንግሰት (State) በእነዚህ ላቅ ያሉ ስብዕናዎች የምትመራ ነች ማለት ነው፡፡

የእኛዎቹ ወዴት ናቸው?

ምሁር መባል እንዲሁ ቀላል ነገር እንዳልሆነ ከትርጎሞቹ ለማየት ችለናል፡፡ ምሁርነትም መለያ ባህሪውን በራሱ አሳቢ መሆን በማድረግ፤ ምጡቅነትን የሚጠይቅ ጉዳይ ነው ማለት ነው፡፡

እናም በሀገራችን በኢትዮጵያ እነዚህን አሳብያን ከወዴት አሉ? ብለን እንጠይቃለን፡፡ በመጀመሪያ የተማረ ሰው ሁሉ ምሁር እንዳልሆነ ለማሳየት ሞክረናል፡፡ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚስመርቋቸውም ተማሪዎች ባለሙያዎች እንጅ ምሁራን እንዳልሆኑ ከትርጉሙ እና ማሟላት ካለባቸው መሰጠቶች አንፃር አይተናል፡፡


ከዚህ በመለስስ ኢትዮጵያዊ ምሁርን ወዴት እናገኝዋለን? ቀጣዩ መመለስ ያለበት ጥያቄ ነው፡፡ ከላይ ከተጠቀሱት የምሁር መሰጠቶች ጋር በተያያዘ አሜሪካዊው ሊቅ Noam Chomsky የምሁራን ድርሻ በአንድ ማህበረሰብ ውስጥ ምንድነው? ብለው ይጠይቁና ‹It is the responsibility of intellectuals to speak the truth and to expose lies-የምሁር ዋነኛ ግዴታው ለእውነት መኖር እና እውነትን መናገር ነው› ብለው ይመልሳሉ፤ የትኛውን እውነት? ሲባሉም የMartin Heideggerን የእውነት ትርጉም በመዋስ ‹ህብረተሰቡን እርግጠኛ፣ ግልፅ፣ ጠንካራ እና አዋቂ የሚያደርገውን እውነት› ብለው ይመልሳሉ፡፡

እናም ይሄ ኢትዮጵያዊ ምሁር ወዴት አለ? ፍትህ ተጓደለ የሚለው ሊቅ፣ መብት ይከበር ማለት የሚገደው ልበ ብርሃን፣ ደፋሩና ፅኑው ምሁር ኢትዮጵያ ውስጥ ወዴት ነው? 

የምሁር ካባ ለባሹ

የነጠረውን ምሁር ፈልጌ ባጣ ጊዜ፤ እስኪ ከተለመደው ‹የምሑር› ሰፈር ይፈለግ ብየ አሰሳ ገባሁ፡፡ ጂቡቲያዊው የዩኒስኮ ሰራተኛ Ali Moussa Iye በአፍሪካ ቀንድ ያለው የምሁራን ጉዳይ እጅግ አሳስቧቸው ‹The Betrayal of the Intellectuals›  በሚል ርእስ፤ ስለ ቀንዱ ሀገራት የምሁራን ክህደት እና መፍትሄው አጭር ፅሁፍ ፅፈዋል፡፡ ፅሁፋቸውን ሲጀምሩም ‹የቀንዱ ሀገራት ምሁራን አደግዳጊ፣ አቤት ወዴት ባዩችና ሎሌዎች ናቸው› በማለት ነው፡፡ ሲቀጥሉ ‹They have rallied to every flag of convenience raised by powerholders and powerseekers… Intellectuals in the Horn of Africa have failed to fulfill their mission and have betrayed their people.› በማለት ‹ምሑራን› በቀንዱ ሀገራት ከዳተኛ እና ሸክም እንደሆኑ ያስረዳሉ፡፡ ጋናዊው ፕሮፌሰር ጆርጅ አይቴ እነዚህን ‹ምሑራን› ‘Intellectual Prostitutes’ ይሏቸዋል፡፡ የሀገራችን ‹ምሑራንስ› ከዚህ ይልቃሉን?

‹ግማሽ ወንበዴ፣ ግማሽ መደዴ›

ፊደል የቆጠሩ፣ በዲግሪ ላይ ዲግሪ የደራረቡ ብዙ ኢትዮጵያዊያን እንዳሉ አይካድም፡፡ ከእነዚህ ውስጥ አንባቢ-ማህይማን (Functionally Illiterates) በዝተው ይታያሉ ማለትም ለኔ ስህተት አይደለም፡፡ ሀብት በምን መንገድ ማጋበስ እንደሚቻል ሲያሰላስል የሚውል ዶክተር እና ፕሮፌሰርን ማየት ብርቅ አይደልም፡፡ ሀብትን መፈለግ ሳይሆን ችግሩ የሕዝቡን ሀብት ዘርፌ ካልሄድኩ ብሎ መኳተኑ ነው ትዝብቱ፡፡ ይህ ነው እንግዲህ ወንበዴው የምሁር ካባ ለባሽ፡፡ በምሁርነት ካባ ለባሹ ሌላኛ ተርታ የሚሰለፈው ደግሞ ‹ሀገሪቱን ወዴት እናስኪድ?› ማለቱን ትቶ፤ ‹እኔ ወዴት ልሂድ?› ማለትን የሚያዘወትረው ነው መደዴው፡፡

የPrinceton ዩንቨርስቲ ፕሮፌሰር የሆኑት Forrest Colburn በወታደራዊው ዘመነ መንግስት ጊዜ በፃፉትና ‹The Tragedy of Ethiopia's Intellectuals› ባሉት ፅሁፋቸው ላይ አንድ ተማሪ እንዲህ አለኝ ይላሉ "Ignorants are more concerned about Ethiopia than are intellectuals." ይህ ነው ኪሳራው፣ ይህ ነው ድቀቱ፡፡

አሸርጋጁ

በሌላ በኩል ደግሞ መንግስታዊ መናን በማሰላሰል መንግስትን አይዞህ በርታ የሚሉ ‹ምሑራን› አሉ፡፡ መንግስትን የሚቃወም ሀሳብም ሲቀርብ ጅራፍ እያነሱ ጀርባ ገራፊዎች ይሆናሉ፡፡ ከዚህ በተቃራኒው ደግሞ መንግስትን መቃወም እንደ አንጀራ የያዙ ‹ምሑራን› ተሰልፈዋል፡፡ በመንግስት ተቀጥሮ፤ ለመንግስት ስራ መስራት ስህተት ነው እያልኩ አይደለም፤ መንግስትንም ማማከር ሀጢያት የለውም፡፡ ስህተቱ የሚጀምረው ‹ምሁራን ዋነኛ አላማቸው ለእውነት መኖር ነው› የሚለውን ጥልቅ ሀሳብ ትቢያ ላይ ወርውረው ጥለው. የምሁርነት ካባውን ግን ሲደርቡት ነው፡፡ ወይ ካባውን ማውለቅ ያለዛም ለሀሳበ መኖር ነው ምርጫው መሆን ያለበት፡፡ ግን በምን ወኔ፡፡ ‹ምሑር› ካልተባሉ መናው ይቀራላ፡፡

ምሁር› የለሽ፣ ‹የአደባባይ ምሁር› ትፈልጊያለሽ

እንደ Edward Saïd ያሉ ፀሃፍት ‹[The] ... real or 'true' intellectual is, therefore, always an outsider, living in self-imposed exile, and on the margins of society.› ይላሉ፡፡ ‹ምሁር ከባዕቱ መውጣት የለበትም፤ ራሱን ያሳሰረ የህብረተሰብ ግንጣይ ነው› ይላሉ፡፡ ይህ ‹የጋን መብራት› የሚባለው  ነው፡፡
ገጣሚው ከበደ ሚካኤል በበኩላቸው፡
‹‹የተማረ ሆኖ፣ እውነቱን የማይገልጽ
ባለ ጸጋ ሆኖ፣ ገንዘቡን የማይሰጥ፣
ደሃ ሆኖ፣ መስራት የማይሻ ልቡ፣
ሶስቱም ፍሬ ቢሶች፣
ለምንም አይረቡ።››
ይላሉ፡፡
ዘመናዊ እሳቤው ምሁራን ለህብረተሰቡ ግልጋሎት ይሰጡ ዘንድ ይሰብካል፡፡ ምሁራን ወደ ሕብረተሰቡ ሲወጡም የአደባባይ ምሁራን (Public Intellectuals) ይባላሉ፡፡ እናም በሀገራችን እነዚህ የአደባባይ ምሁራን ያሰፈልጉናል ማለታችን ያስማማን እና ግን የታሉ? ከወዴትስ ይመጣሉ? አሁንም ጥያቄ ነው፡፡ በርግጥ የጓዳውን ምሁር ሳናገኝ የአደባባዩን ምሁር መፈለጋችን ቧልት ይሆን?
ምሁሩ ወይ ወዴት ነህ? ምሁሩን ያገኛችሁ ወይም የት እንደገባ የምታውቁ እስኪ ሀሳባችሁን ወዲህ በሉ፡፡

* በዚህ ፅሁፍ በሀገራችን በተለምዶ ‹ምሑር› የሚባሉትን ለመግልፅ ሐመሩ ‹ሐ›ን መጠቀምን መርጫለሁ፡፡ ለቀሪዎቹ ግን የተለመደውን ‹ምሁርን› ተጠቅሜያለሁ፡፡ 

3 comments:

  1. Zele, it is interesting view,keep iu up!!!

    ReplyDelete
  2. wondimamachochu Zelalem Kibret & Daniel kibret alitechalachuhim

    ReplyDelete
  3. Nice Article....ye universitiwochachin betam yemiyasazin new....ene simar betam yitemagn neber mihur mikniyatum bemihur memar yimeslegn sileneber universiry gin yelem hulum almach and traz netek....1relatively dena yemibal prof. Eyastemaren lachir gize koyito kobelele wede belgium....2009 yetemerekut Jimma U

    ReplyDelete