Monday, August 17, 2015

ክሱ ምን እንደሆነ መረዳት የማንችለው - አቤል

‹‹7ኛ ተከሳሽ አቤል ዋበላ ሱጌቦ ከግንቦት 2004 ዓ.ም ጀምሮ የሽብር ቡድኑ መስራችና አባል በመሆን ድርጅታዊ መዋቅር፤ የሥራ መዘርዝር በማዘጋጀት በተሰጠው የሥራ መዘርዝር የሽብር ቡድኑን የውጭና የሀገር ውስጥ አመራሮች ግንቦት ሰባት ከተባለው የአሸባሪ ቡድን ጋር ግንኙነት እንዲፈጥሩ በማድረግና በማደራጀት በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር ስልጠና በመውሰድ በሕቡዕ ቡድኑ መካከል የሚደረገውን የመልዕክት ልውውጥ የመንግስት የፀጥታ አካላት እንዳይደርሱባቸው በመደበቅና በስውር በመገናኝት security in box (sic) የህቡዕ ቡድኑ አመራሮች የሚሰለጥኑትን ስልጠና በመሰልጠን ሁለንተናዊ የትግል አቅጣጫ የግንቦት ሰባት እስትራቴጂ በመቀበልና በመሠልጠን የሽብር ተግባር ለመፈፀም ተሣታፊ (sic) በመሆን ተይዟል፡፡››
ይህ ጦማሪ አቤል ዋበላ ‹የህብረተሰቡን ሰላም ወይም ጤና ለመንሳት በማሰብ የሽብርተኝነት ድርጊት ሞከሯል፣ አቅዷል፣ አሲሯል፣ አነሳስቷልና ተዘጋጅቷል› በሚል ስለ ፀረ-ሽብርተኝነት የወጣውን አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀፅ 3(2) እና አንቀፅ 4 ጥሷል በሚል በከሳሽ የፌደራል ዓቃቤ ሕግ የቀረበበት ክስ ነው፡፡
ጉዳዩን እያየ ያለው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት፣ 19ኛ ወንጀል ችሎትም ከሳሽ ያቀረባቸውን ‹የሰነድ ማስረጃዎች› (በነገራችን ላይ ከሳሽ በአጠቃላይ ያቀረባቸው ‹የሰነድ ማስረጃዎችን› ብቻ ነው፡፡ የቀረቡት የሰው ምስክሮች የሰነድ ማስረጃዎቹን ትክክለኛነት ለማስረዳት ብቻ የቀረቡ ናቸው) መርምሮ አቤል ዋበላ መከላከል ሳያስፈልገው በወንጀለኛ መቅጫ ስነስርዓት ሕግ 141 መሰረት ‹ከክሱ በነፃ መሰናበት አለበት› ወይስ በወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት ሕግ 142 መሰረት ‹ክሱን ሊከላከል ይገባዋል› የሚለውን ለመወሰን ቀጠሮ ይዟል፡፡ እኛም አቤል ላይ የቀረቡትን ‹ማስረጃዎች› ከቀረበበት ክስ አንፃር መመልከቱ የክሱን ምንነትና ሊጠበቅ የሚችለው/የሚገባው ብይን ምን መሆን አለበት የሚሉትን ጉዳዮች ለመመለስ ይህን ፅሁፍ አቅርበናል፡፡
***
ሚያዚያ ወር መጀመሪያ 2006 አንድ ምሽት ለአቤል ጥሩ ነገርን ይዛ አልነበረም የጠበቀችው፡፡ ሰዓቱ ከምሽቱ ሁለት ሰዓት ትንሽ አለፍ እንዳለ አቤል ከቢሮ ወደ ቤቱ እየገባ እያለ የቤቱ መዳረሻ ጋር ማንነታቸውን ለጊዜው ባልለያቸው ሶስት ሰዎች ከኋላ ተመቶ ራሱን ሳተ፡፡ ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ሲነቃ ይዞት የነበረው ላፕ ቶፕና የእጅ ስልክ መወሰዳቸውን አረጋገጠ፡፡ በአስገራሚ ሁኔታ የኪስ ቦርሳውና ኪሱን አልተነኩም፡፡ በጊዜው ብዙ ጥርጣሬዎች በብዙ ሰዎች ውስጥ የነበረ ቢሆንም ጉዳዩ ለፖሊስ ሪፖርት ተደርጎ ፖሊስም መልስ አልሰጠም ነበር፡፡ የአቤል ላፕ ቶፕና ስልክ አቤል በተያዘበት ዕለት በእጁ አለመያዙ አስሮ ማስረጃ ለሚፈልገው ፖሊስ ትልቅ የራስ ምታት ነበር፡፡ ሌሎች ተከሳሾች ላይ እንዳደረጉት ላፕ ቶፑ ውስጥ ያገኙትን አንዱን መፅሃፍ ፕሪንት አድርገው በቃ ‹ማስረጃ› ነው እንዳይሉ አደረጋቸው፡፡
ነገር ግን አንድ ጥሩ መፍትሔ አገኙ፤ ምስጋና አቤል በታሰረ ዕለት ኪሱ ውስጥ የተገኝ ፍላሽ ዲስክ፡፡ አቤል ዋበላ ላይ የቀረቡት ሁሉም ማስረጃዎች አቤል በታሰረበት ዕለት ይዞት ከነበረው ፍላሸ ላይ ፕሪንት የተደረገ ነው፡፡ እዚህ ፍላሽ ውስጥ ደግሞ አንድ ስለኢንክሪፕሽን የሚያትት አጭር ፅሁፍ እና ኮሮጆ ዶት ኮም የተባለ የዌብሳይት ምክረ ሐሳብ(proposal) ነበሩ፡፡ በቃ አቤል ‹የሕብረተሰቡን ወይም የሕብረተሰቡን ክፍል ደህንነት ወይም ጤና ለአደጋ ለማጋለጥ በማሰብ የሽብርተኝነት ድርጊት ለመፈፀም አቅዷል፣ ተዘጋጅቷል፣ አነሳስቷል፣ አሲሯል እና ሞክሯል› ተብሎ ለቀረበበት ክስ ‹ማስረጃ› ተብለው የቀረቡበት እነዚህ ሁለቱ ሰነዶች ብቻ ናቸው! (‹ … ድርጅታዊ መዋቅር፤ የሥራ መዘርዝር በማዘጋጀት … › ተብሎ በከሱ ውስጥ የቀረበው ጭብጥ እና እሱን ያስረዳል ተብሎ የቀረበው ‹ማስረጃ› በመቃወሚያ ብይን ውድቅ መደረጉ ይታወቃል)  አሳዛኙ ጉዳይ ይሄ ነው፡፡ ‹ስለ ኢንክሪፕሽን ፅሁፍ ፍላሽህ ውስጥ ተገኝቷል፤ በቃ ወንጀለኛ ነህ› የሚለውን ቧልት እንተወውና እስኪ ኮሮጆ ዶት ኮም የተባለውን የዌብሳይት ፕሮፖዛል እንመልከት፡፡
ኮሮጆ ዶት ኮም
ይህ የዌብሳይት ምክረ ሐሳብ በዞን ዘጠኝ ኢ-መደበኛ የጦማሪያን ቡድን ምርጫ 2007ን አስመልክቶ (‹ምርጫ› ይኖራል በሚል ተስፋ) ለበይነ መረቡ ማህበረሰብ (online community) መረጃ ለመስጠት በማሰብ የተዘጋጀ ሲሆን፤ በምክረ ሐሳቡ ላይ የተቀመጡትን ዓላማዋች እና ዌብሳይቱ እንደ ግብ አድርጎ የወሰዳቸውን ግቦች የተመለከተ ሰው ከሳሹ አካል ይሄን ምክረ ሐሳብ ለወንጀል ድርጊት ‹ማስረጃ› ይሆነኛል ብሎ ማቅረቡ ለሕጉም ሆነ ለፍትህ ስርዓቱ ያለውን ንቀት ነው የሚገነዘበው፡፡ ለመሆኑ ስለ ምርጫ ለመዘገብ የተዘጋጀ የዌብሳይት ምክረ ሐሳብ ‹ከሽብርተኝነት› ጋር ምን ያገናኝዋል; ማለታችን አይቀርም፡፡ እንግዲህ ይህ ነው አቤልና ጓደኞቹ የሕብረተሰቡን ደህንነት እና ጤና ለመንሳት አቅደው ሲንቀሳቀሱ ነበር ያስባላቸው፡፡  
ከ15 ዓመት እስከ ሞት

አቤልና ጓደኞቹ ተከሰው ክሳቸውን እየተከታተሉ የሚገኙ ሲሆን የተከሰሱበት አንቀፅ ደግሞ ከ15 ዓመት ፅኑ እስራት እስከ ሞት ድረስ ሊያስፈርድ የሚችል ነው፡፡ እንግዲህ አቤል የዌብሳይት ፕሮፖዛል ፍላሽህ ውስጥ ስለኢንክሪፕሽን ከሚያትት ሌላ ፅሁፍ ጋር ተገኝቶብሃል ተብሎ ነው ይህ ከፍተኛ ፍርድ ሊያስፈርድ የሚችል አንቀፅ ተጠቅሶ አቤል ላይ ክስ የቀረበበት፡፡ የአቤል ብቸኛው ጥፋት በሀገሩ ሰላማዊ ዜጋ ሁኖ መኖሩ ካልሆነ በስተቀር እነዚህን ሰነዶች አቅርቦ የወንጀል ክስ መመስረት በራሱ እጅግ ያስደነግጣል፡፡ አቤል እና ጓደኞቹ ላለመታሰር ምን ማድረግ እንዳለባቸው እንኳን ግልፅ አይደለም፡፡ የት ይኑሩ? ምን ያድርጉ? የሚለውን ስናስብ መልስ መስጠት አንችልም፡፡ አዎ! አቤል ነፃ ሰው ነው!
አቤል ዋበላ

No comments:

Post a Comment