Sunday, November 11, 2012

የቀለም ልዩነት(መድልኦ) በአገራችን ኢትዮጵያ



ይህን ጽሑፍ ከላይ ርዕሱን አይታችሁ ምን ለማለት ፈልጎ ነው? አሊያም ሁሌም ጠንካራ ጎናችን የሆኑትን መስማትና ማንበብ ስለለመድን ይህ ሐሳብ ግርታ የሆነ ስሜት ሊፈጥርባችሁ ይችላል። ሐቅ ቢመርም መዋጥን መልመድ አለብና የተሰማኝን ጻፍኩት የሚሰማችሁን በጨዋ ደንብ አክሉበት። (ፀያፍ ካልተሳደቡ አስተያየት ያልሰጡ የሚመስላቸውን ታታሪ ተሳዳቢዎችን ነው ማሳሰቢያው የሚመለከተው!)

በኢትዮጵያችን ውስጥ ጥቁሩ ማኅበረሰብ (ከጠይም በላይ የጠቆሩትን ማለቴ ነው) በቆዳው ቀለሙ ብቻ መድልዖ ይደርስበታል የማግለልና በቀለም ብቻ የሚፈፀሙት በደሎችና መንስኤዋችን ለመዳሰስ እሞክራለሁ።

፩፡-የሥራ ዕድል

ሥራ ለማግኘት ከትምህርትና  ከችሎታ መመዘኛዎች በተጨማሪ የምትጠየቀው ወይ የሚፈለግብህ/ ነገር አለ፡፡ የት አገር እንዳትሉኝ በእኛዋ ኢትዮጵያችን ውስጥ መልከ መልካም መሆን አሊያም ጠይም የቆዳ ቀለም ሚዛኑን ትደፉ ዘንድ ከፍተኛውን ድርሻ ይወስዳሉ። የስራ አመራር፣ አስተዳደራዊና ፖለቲካዊ ሹመቶች ወዘተ... ግርማ ሞገስና ውበት ከብቃት ይልቅ ሚዛን ይደፋሉ። የቤት ሠራተኝነት የምትቀጠር አንዲት ሴት ጠቆር ካለች የመጥፎ ገድ ምልክት ተደርጋ፣ ልጆቻችን ሊፈሩ ይችላሉ ተብሎ፣ ያቺ ምስኪን የሥራ ዋስትና ታጣለች። በተፈጠሩበት አገር ላይ መገለል ጉዳቱ ምን ያህል መሆኑን ከቀመሱት በላይ ማን ሊሰማው ይችላል?

(
አካላዊ ውበትና ቅርፅ የሚሹ የሥራ መስኮች የሉም እያልኩኝ ግን አይደለም!)

፪፡-የፍቅርና የትዳር አጣማጅ ማግኘት ጫናዎች

አንዲት የአገራችን ልጅ ከናይጀሪያዊ ጓደኛዋ ጋር በፍቅር ከነፈች ሲበዛ በጣም ትወደዋለች እሱም በጣም  ይሳሳላታል፣ የተማረ ስልጡን ባለሙያ ነው። በፍቅር የወደቀችለት ልጅን አግብቶ ቤተሰብ መመሥረት ይፈልጋል፤ እሷም ትፈልጋለች ግን ያደገችበት ማኅበረሰባዊና ቤተሰባዊ ጫና በትምህርት ያገኘችውን ዕውቀት በልጦ በጭንቀት ማዕበል ውስጥ በሰመመን እየተብከነከነች መኖርን አስመረጣት። ለምን እየወደደችው፣ እያፈቀረችው የትዳር አጣማጁ መሆንን አትሻም? መልሱ ቀላል ነው የቀለም ልዩነት ብቻ ነው። የቆዳው መጥቆር፣ የከንፈሩ መተለቅ አካላዊ ገፅታውን እሷ ብትወድለትም ቤተሰቦችዋ ግን እንደማይቀበሉት ታውቃለች፡፡ ያንንም በቀጥታም በተዘዋዋሪም ነግረዋታል የመካነ አዕምሮ (ዩንቨርሲቲ) መምህሩ ወንድሟ በፌስቡክ ላይ ምስሉን አይቶ ዘራችንን ልታበላሺ ላልጠፋ ወንድ ባርያ ትይዣለሽ? በማለት አሸማቋታል (ይህ ሰው ለተማሪዎቹ ምን ይሆን የሚያስተምራቸው? የዘር፣ የቀለም ልዩነት ወንጀል በሆነበት ዘመን ያልተለወጠ ሰው በተለይ መምህር መሆኑ ጥፋቱን ያሰፋዋል!)

Wednesday, November 7, 2012

የትምህርት ጥራት ነገር (ክፍል አንድ)



በመልማት ላይ ያሉ ሀገራት ካላቸው የመዋለ-ነዋይ ውስንነት አንፃር መንግስቶቻቸው የትኛው መስክ እና የትኛው ስራ ቀድሞ መከናወን እንዳለበት ለመወሰን አስቸጋሪ የሆነ አጣብቂኝ ያጋጥማቸዋል፡፡ ድህነትን ለማሸነፍ በሚደረገው ጥረት ውስጥ ከፍተኛ እና ፈጣን ውጤት የሚያስመዘገቡት መስኮች እና ተግባራት ወይንም ደግሞ ከሌሎች መስኮችና ተግባራት ይልቅ አንገብጋቢ ለሆኑት ችግሮች መፍትሄ መስጠት  የሚችሉት የመዋለ-ነዋይ ፍሰት ከሚደረግባቸው ተግባራት የመጀመርያውን ረድፍ ያገኛሉ፡፡ ብዙዎቹ ተግባራት ግን አይጠቅሙም ወይንም አያስፈልጉም ከሚል መነሻ ሳይሆን ድሀ ሀገራት በሚለዩባቸው የአቅም ውስንነት ብቻ ሳይተገበሩ ይቀራሉ፡፡


ሀገራችን ኢትዮጵያ ደሀ ናት፡፡ ከፍተኛ የሆነ የመዋለ-ነዋይ ውስንነት፣ ቢሰራ ህዝቡን ይጠቅማል ብሎ መንግስት የሚያስባቸውን ተግባራትን እውን እንዳያደርግ ማፈናፈኛ ያሳጡታል፡፡ (በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንዲሉ ከዚህም በላይ በብልሹ አሰራር እና በሙስና ምክንያት ሀገሪቱ እጅግ አድርጋ የምትፈልገው ነዋይ ያለ አግባብ ይባክናል፡፡) የኢትዮጵያ መንግስትን የአቅም እጦት አጣብቂኝ ውስጥ ከሚከተው ተግባራት መካከል የትምህርት ጥራት ከተደራሽነት ጋር እኩል ማራመድ አለመቻሉ ይጠቀሳል፡፡ በርግጥ ለትምህርት ጥራት መጓደል ሌሎች አያሌ ምክንያቶችን መደርደር ይቻላል፡፡ ነገር ግን የአቅም ውስንነት ትልቅ ሚና እንዳለው የማይካድ ነው፡፡


ዜጎች ለሀገራቸው ዕድገት ጉልበታቸውን፣ ገንዘባቸውን እና ዕውቀታቸውን በመጠቀም የየራሳቸውን አስተዋፅዎ ያደርጋሉ፡፡ የላቀ ዕውቀት ባለቤት የሆኑ ዜጎች የበዙባት ሀገር ከድህነት ለመላቀቅ መንገዱ እጅግ የቀለለ ይሆንላታል፡፡ ዜጎቿ ዕውቀታቸውን በመጠቀም ከድህነት የምትወጣበትን ውጤታማ መንገድ ይቀይሳሉ፣ ሀገር ተረካቢውን ትውልድ በሚገባ ይቀርፃሉ፡፡ የተማሩ ዜጎች የተመሰረተ ቤተሰብን መጥኖ መውለድ ስለሚሰጠው ጥቅም ለማገንዘብ ብዙ ወጪ አያስፈልገውም፡፡ በቤተሰቡ ውስጥ የሚወለዱ ህፃናትም እድሜያቸው ለትምህርት እንደደረሰ ትምህርት ቤት የመግባታቸው እድል ያልተማሩ ዜጎች በመሰረቱት ቤተሰብ ውስጥ ከተወለዱት ህፃናት አንፃር ሲገመገም የጎላ ልዩነት አለው፡፡


በአሁኑ ወቅት እድሜያቸው ከ15 ዓመት በላይ ከሆኑት ኢትዮጵያዊያን መካከል 30 በመቶ የሆኑት መሰረታዊ የሆነውን ዕውቀት ማንበብና መፃፍ ይችላሉ፡፡ ቀሪዎቹ ግን ጣቶቻቸውን ፊደላትን ለመከተብ እና አይኖቻቸውን ከወረቀት ላይ ተክለው ፊደል ቆጥረው መረጃ ለማግኘት አይቻላቸውም፡፡ ላቅ ያለ ዕውቀት ኖሯቸው ሀገራችን ከድህነት አረንቋ ለመውጣት በምታደርገው ሩጫ ንቁ ተሳታፊ ሆነው የጎላ አስተዋፅዎ ማድረግ የሚችሉት ዜጎች ደግሞ እጅግ በጣም ጥቂቶቹ ናቸው፡፡

Monday, November 5, 2012

ወጣት ወንድ የመሆን ጣጣ



በወጣትነት ወንድ ዕድሜ ክልል ከሆንክ አሁን የምናወራው ነገር ቢያንስ አንድ ቀን እንደገጠመህ አንጠራጠርም፡፡ መንገድ ላይ እየሄድክ ነው እንበል፣ ሰፈሩን አታውቀውም፡፡ ወደየሆነ ቦታ አቅጣጫ የሚያመለክትህ ሰው እየፈለግክ ነው፤ አንዲት በአንተ የዕድሜ ክልል ውስጥ ያለች ሴት ከወዲያ ማዶ ስትመጣ አይተህ በመደሰት ‹‹ይቅርታ የኔ እህት፤›› ትላታለህ - አቅጣጫ ለመጠየቅ፡፡ ሴቲቱ ገልመጥ ብላ ታይህና (ወይም ቀድማ ካየችህ) እንዳልሰማ ሰው ፊት ነስታህ ታልፍሃለች፡፡ አቅጣጫውም አልተገኘ፣ ክብርህም አልተጠበቀ ይሉሀል ይህን ጊዜ ነው - በለካፊ ወንድነት የመፈረጅ ጣጣ፣ ወጣት ወንድ የመሆን ጣጣ! ነገር ግን ይሄ ‹‹እዳው ገብስ›› የሆነ ጣጣ ነው፡፡

የዞን ዘጠኝ ብቸኛ የሴት ጦማርያን የሆኑት ማሕሌት እና ሶልያና ባለፈው ሳምንት ማገባደጃ ላይ ያስነበቡን ‹‹ወጣት ሴት የመሆን ጣጣ›› ለዚህ ጽሑፍ መወለድ መንስኤ ሆኗል፡፡ እነርሱ የወጣት ሴትነትን ጣጣ በዘረዘሩ ቁጥር ወንድ ሆኖ እያነበበ ያለ ወንድ የመሆን ጣጣን ማሰብ የሚቸግረው ይኖራል ብሎ ማለት ዘበት ነው፡፡ ነገርዬው ‹‹የሴቶች ጉዳይ›› ብቻ የሚጮህበት ዘመን መሆኑ፣ ወንዶች ወንድ በመሆናቸው ብቻ የሚጋረጡባቸውን ፈተናዎች (ወይም በዚህ ጽሑፍ ቋንቋ ‹ጣጣዎች›) የሚያወራ መገናኛ ብዙኃን የለም፡፡ የዚህ ጽሑፍ ዓላማ የሴቶቹን ጣጣ ማጣጣል፣ ወይም ዕውቅና ማሳጣት ሳይሆን ወጣት ወንድ በተለይ እና ወንድ በጥቅሉ መሆንም በራሱ የራሱ ጣጣዎች እንዳሉት ማመላከት እና ለጣጣዎቹ ዘላቂ መፍትሄ ወደሚያመጡ የውይይት አጀንዳዎች የዞን ዘጠኝን ነዋሪዎች በዚህ መድረክ እና ከዚህም ውጪ እንዲያበረክቱ ማነሳሳት ነው፡፡

በልጦ የመገኘት ጣጣ

በሀገራችንም ሆነ በዓለማችን በተገነቡ ባሕሎች እና እሴቶች መሠረት ወንድ ልጅ የአውራነት፣ ወይም በልጦ የመገኘት ግዴታ ተጥሎበታል፡፡ ለምሳሌ የፍቅር ወይም የትዳር አጋር ለማግኘት በትምህርት ደረጃ፣ በደመወዝ ሌላው ቀርቶ ተፈጥሮ በሚያስገድዳቸው ቁመት እና ዕድሜ ሳይቀር በልጦ መገኘት አለበት፡፡ ይህንን ባሕል አመጣሽ በልጦ የመገኘት ኃላፊነት በዘመነኝነት ለመስበር ቢሞከርም የተሳካ አይመስልም፡፡ ሴቲቱን ከፍሎ የሚያስተምር፣ ሸምቶ የሚያስውብ፣ አግብቶ ቤቱ የሚያመጣ እንጂ በተቃራኒው የሚንቀሳቀስ ወንድ የለም፤ ሴቶቹም (ብዙኃኑ) አይፈልጉትም፡፡

ወንድ ልጅ ለሴት ልጅ ከለላ እንዲሆን በወንዶቹም በሴቶቹም ይጠበቅበታል፡፡ ሚስቱን ከለካፊ ጎረምሳ ማስጣል (መጠበቅ)፣ መሠረታዊ ፍላጎቷን ማሟላት፣ በየካፌው መጋበዝ፣ የዕድሜ፣ የትምህርት እና የደሞዝ (አቻው የሆነችውን ሳይቀር) ሙሉ የኢኮኖሚ ጥብቅና ማድረግ ያልተጻፈ ግዴታው ነው፣  ወዘተ… ወዘተ… ከዚህም በላይ ደግሞ በዚህ ክፉ ዘመን ኑሮን ታግሎ አሸንፎ፣ ጎጆ መሥርቶ፣ የቤት ዕቃ ሞልቶ፣ ሠርጎ ማግባት አለበት፡፡ ይህንን ሁሉ ማድረግ ስለሚከብደው ቆሞ የቀረ አለሌ የመሆን ጣጣ ፊቱ ላይ ተደቅኖበታል፡፡

Sunday, November 4, 2012

ሕፃናትና ኢትዮጵያችን



ልጆች የዛሬ አበባዎች የነገ ፍሬዎች ናቸው፡፡ የነገይትዋ ኢትዮጵያ ተተኪ ብላቴናዎች ከአበባነት ወደ ፍሬነት
እንዴት ይቀየራሉ? ምን ዓይነት ፍሬዎች እንድናገኝ እየተሰራ ነው?  የሚለውን ጥያቄ በዚህ ጽሑፍ ወፍ በረር ለመዳሰስ እሞክራለሁ።

ልጆችን ከአስተዳደጋቸው መሠረት አስይዞ አርሞ ማሳደግ ጥቅሙ ለቤተሰብ ብቻ ሳይሆን ትሩፋቱ ለአገርና ለወገን የሚጠቅሙ የነገይትዋን ኢትዮጵያ የሚረከቡ ብቁ ትውልድ እንዲኖረን ያስችላል። ይህ ግን ዝም ብሎ አይመጣም ከቤተሰብ እስከ ማህበረሰቡ እንዲሁም ልጆች ዕድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስ ብዙ ጊዜያቸውን የሚያሳልፉበት ትምህርት ቤት ትልቁን ኃላፊነት ይወስዳሉ። ሰንሰለታማው የኃላፊነት ድርሻ አንድ ቦታ ላይ ከተስተጓጎለ ወይም ሰንሰለቱ ከተበጠሰአሜከላ ዜጋ” የማፍራታችን ዕድል ይጨምራል።

ሕፃናት ወረቀቶች ናቸው ንፁህ ሕሊናቸውን በመልካም ነገሮች እየተገነቡ እንዲያድጉ ከላይ የተጠቀሱት አካላት ምን  ምን መደረግ አለባቸውብሎ መወያየት ለነገ የምንፈልገው አይነት ትውልድ ምን አይነት ይሁን የሚለውን ለማወቅ ይረዳናል፡፡

፩፡ቤተሰብ

በቤተሰብ ውስጥ ስለልጆች ያለው አመለካከት ላይ ለውጥ ቢኖርም አሁንም በቤተሰብ ደረጃ  ብዙ ችግሮች አሉብን። ለአብነት ያህል ብናነሳ ልጆችን የማበረታታት ባህላችንንም ብዙ የሚቀረው ነው፡፡ እሰየው፣ ጎበዝ፣ በርታ፣ በጣም ተለውጠሃል ወዘተ... የሚሉ ሞራል የሚገነቡ ማበረታቻዎችን ቢኖሩንም እነዚህን ማበረታቻዎች በተከታታይ ለሕፃናት ማሰማት በራሳቸው የሚተማመኑ ልጆችን ለመፍጠር አዎንታዊ አስተዋፆ አለው። በአንፃሩ
·         ልጅ ያቦካው ለእራት አይበቃም
·         ልጅና ጫማ አልጋ ስር
·         ነገር ሁለት ፍሬ አንዱ ብስል አንዱ ጥሬ ወዘተ...

ከላይ የተጠቀሱ ሞራል ገዳይ አባባሎችን በማዝነብ ብላቴናዎችን ማሸማቀቅ ልንተወው የሚገባን ማኅበራዊ እንከኖቻችን ናቸው። ወላጆች ልጆቻቸው ፊት ለፊት መጨቃጨቅ፣ መደባደብና መዘላለፍ የልጆችን ሕሊና ክፉኛ ከመጉዳቱም በላይ  ቤት ውስጥ ሰላም ከሌለ ሕፃናት በጭንቀት ውስጣቸው ክፉኛ ስለሚጎዳ ትምህርታቸውን በአግባቡ መከታተል ይሳናቸዋል። ወላጆች አቅማቸው በፈቀደ መጠን የልጆቻቸውን ስሜት ማጥናት አለባቸው፡፡ወደ ቀለም ትምህርታቸውም ሆነ በልዩ ተስእጦአቸው አሊያም ሙያ ምርጫቸው በየትኛው መስክ ዝንባሌ እንዳላቸው በፅሞና መከታተል ያሻል ፡፡ ስሜታቸውን በመጫን ወላጆች የሚመኙትን ወይም ሞክረው ያቃታቸውን ነገር በልጆቻቸው ላይ ለማየት መሞከርና ካለፍላጎታቸውና ዝንባሌዎቻቸው ማሳተፍ ደስተኛ እንዳይሆኑ ያደርጋቸዋልና ወላጆች ጥንቃቄ ሊወስዱ ይገባቸዋል። በተጨማሪም ከትምህርት ውጪ ያሉትን ሰዓታት ልጆችን ቤት ውስጥ ብቻ እንዲታጎሩ በማድረግ፣ በፊልምና የግዴታ ሥራ ማጥመድ ልጆች ልጅነታቸውን በአግባቡ ተጫውተው እንዳያልፉ ያደርጋቸዋል። በዕቅድ ይመሩ ዘንድ ወላጆች የጫወታና የጥናት ጊዜያቸውን በመመደብ የጊዜ ክቡርነትን በልጅነታቸው በማስተማር የጊዜ አጠቃቀምና ኢትዮጵያዊነት(ቀጠሮ ላይ ያለንን አገራዊ ደካማነት) የሚታረቁበትን መሠረት መጀመር አለብን።