Sunday, November 4, 2012

ልፈራ የሚገባኝ “ሕይወቴን ያለክብር እንዳልመራ” ነዉ እንጂ “ክብር የተነፈገዉ ሕይወቴን እንዳላጣ አይደለም፡፡”

ፍቃዱ አንዳርጌ

ዞን 9 በተባለዉ የመወያያ መድረክ ላይ ብዙ ጠቃሚ ሃሳቦች በተለያዩ ፅሃፊዎች እየተነሱ ሲብራሩና ለዉይይት ሲቀርቡ እከታተላለዉ ይበል የሚያሰኝም ነዉ :: እንደ አስተያየት ግን በየጊዜዉ የሚነሱ ሃሳቦች እንደ ቆዳ እየለፉ ማለፍ እንዳለበት ይሰማኛል፡፡
ዛሬ እኔም የማህሌት ፋንታሁንየፍርሃት ዘመንየሚለዉን መጣጥፍ አንብቤ ከሃሳቧ ላይ ሃሳቤን መጨመር ፈለኩ - ማህሌት በፅሁፏ የዘረዘረቻቸዉ የህብረተሰብ ክፍሎች ማለትምተማሪዎች፣ሰራተኞች ፣አሰሪዎችና ባለሃብቶች ፍርሃት መር ኑሮ ለመኖራቸዉ ተማሪዉ ተመርቆ ስራ አጥ እንዳይሆን፣ ሰራተኞች የስራ ዋስትናቸዉን፣ እድገት እና የትምህርት እድል የሚያገኙት በመፍራት ስለሆነ፣ አሰሪዎች ከቀዳሚ አለቆቻቸዉ ሞገስን እና ጥቅማጥቅምን ያገኙ ዘንድ እነሱዉ እራሳቸዉ ፈርተዉ ሰራተኞችን የፍርሃት ሀሁ ማስቆጠር ስላለባቸዉ እና በቁስ ቀዳሚነትም ያመኑት ባለሃብቶችም ቢሆኑ ጣሪያ የሌለዉ ፍላጎታቸዉ ይሞላ ዘንድ የፍርሃት መንፈስ ይጠናወታቸዋል፡፡ብላለች፡፡

እኔም ሁሉም ሳይፈልግ ወደ ፍርሃት ዓለም የሚያደረገዉ ጎዞ መነሻዉ የእዉቀት፣የምክንያት እና ፍላጎት ያለመመጣጠን እንደ ሆነ እና መጨረሻዉምየፍርሃት ማህበረሰብ”(fear society) መፈጠር ሊሆን እንደሚችል አምናለሁ ፡፡ በፍርሃት እሳቤ የተከበበ ማህበረሰብ ደግሞ የተቃወሰ ማህበራዊ ስሪት ስለሚኖረዉ ለመጪዉ ትዉልድ ሊያስተላልፈዉ የሚችል ባዶ የፍርሃት መንፈስን ብቻ ነዉ፡፡ እዉቁ ፈላስፋፕላቶየሰዉ ልጅ የተስተካከለ፣ ጤናማ እና ከፍርሃት የፀዳ ምክንያታዊ ስብዕና ይኖረዉ ዘንድ ሊሟሉ ይገባል ያላቸዉን ነገሮችን ዘርዝሯል፡፡ እኛምፍርሃትከስነ ልቦና ስሪታችን ጋር የተያያዘ ስለሆነ የሊቁን ስራ በከፊል እንመልከተዉ እንዲህም ይላልየሰዉ ልጅ አካለዊና ስነ ልቦናዊ ስሪቱ የተስተካከለ ሊሆን ግድ ይለዋል፡፡ የሰዉን ልጅ የነፍስ ሁነት ከሶስት ከፍሎ ማዬት ይቻላል፡፡ የመጀመሪያዉምክንያታዊክፍል ሲሆን አንድ ሰዉ እንዲጠይቅ፣ እንዲያዉቅ ፣እንዲከራከር እና ሃሳቡን እንዲገልፅ የሚያደርግ ክፍል ሲሆን፤ ሁለተኛዉመንፈሳዊ ክፍልየሚለዉ ሲሆን ደግሞ አንድ ሰዉ መልካም ፈቃዱን የሚሰጥበት እና የፍርሃት እና የድፍረት ስሜቱ የሚብላሉበት ክፍል ነዉ፡፡ ሶስተኛዉ ፍላጎትን መሰረት ያደረገዉ ፍላጎታችን የሚርመሰመስበት ክፍል ሲሆን የምግብ፣የመጠጥ፣የወሲብ፣ የሃብትና መሳሰሉ ፍላጎታችን ማንፀባረቂያ ክፍል ነዉ፡፡ይቀጥልናምየአንድ ሰዉ የተስተካከለ ስብዕና ይኖረዉ ዘንድ የእነዚህ ክፍሎች የተመጣጠናና የተስማማ አካሄድ ሊኖራቸዉ ግድ ነዉይለናል፡፡

Thursday, November 1, 2012

የውሃ-ፖለቲካ እና የአባይ ጉዳዮች፡ ወፍ በረር ቅኝት



በዘሪሁን አበበ ይግዛው 
እንደ መነሻ
ባለቅኔ እና ጸሐፌ-ተውኔት ጸጋዮ ገብረመድህን ለመጀመሪያም ለመጨረሻም ጊዜ ባሳተመው የግጥም ካሴት አዋሽ ለሚለው ግጥሙ መግቢያ ማብራሪያ ሲሰጥ… “በማናቸውም የዓለም ህዝብ ባህል ውስጥ አብዛኛውን ጊዜ የየአገሩ ወንዝ ጉዞ በተለይ የታላላቅ ወንዞች ጉዞ፤ የየአገሩ የሰፊው ህዝብ ጉዞ፤ የየትውልዱ ጉዞ ተምሳሌት ሆኖ ይቀረፃል፡፡” ይለናል፡፡ በርግጥ የእያንዳንዱ ሀገር ወንዝ የእያንዳንዱን ህዝብ ጉዞ ታሪክ ይናገራል፡፡ እውነት ነው ከዶን በራይን እና በቴምስ እስከ ዳኑብ በአውሮጳ፣ ከዮርዳስ እስከ ኤፍራጠስ እና ጢግሮስ በመካከለኛው ምስራቅ፣ ከኮሎራዶ እስከ ሚሲሲፒ በሰሜን አሜሪካ፣ አማዞን በደቡብ አሜሪካ፣ ኢንደስ-ጋንጅስ በህንድ፣ ፓኪስታንና ባንግላዴሽ፣ ያንገቲዝ በቻይና፣ እንዲሁም ጉዳያችን የሆነው አባይ በአፍሪካ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ እነዚህ ወንዞች የሚያልፉባቸውን የሚያገናኟቸውን ህዝቦች እና ሀገሮች ስናይ ከወንዙ ጋር የሚያቆራኛቸው እጅግ በጣም አያሌ ምክንያቶች አሉ፡፡ ምክንያቱም እነዚህ ወንዞች ህይወትን፣ ስልጣኔን እና ማንነትን ገንብተዋልና፡፡ እርግጥ ነው ኤፍራጠስ የሚባል ከገነት የሚፈስ ወንዝ ባይኖር የአሲሪያም ሆነ ሞሶፖታሚያ ወይም የባቢሎን ስልጣኔ ባልኖረ፤ እርግጥ ነው አባይ የሚባል ህይውትን ያዘለ ከኤደን የሚመነጭ ወንዝ ባይኖር ግብጽ የሚባል ሀገርም ሆነ ህዝብ ባልኖረ፡፡ ወንዞች የሀገራት ስልጣኔ መሰረቶች እና ማማዎች ናቸው፡፡ ምንም እንኳን በአካባቢ ጥናት-ጅኦግራፊ እይታ ወንዞች አንድ ወጥ የሆኑ ስነ-ምድራዊ ክስተቶች ቢሆኑም በዘመናት በሰው ልጆች በተፈጠሩት ወሰኖች እና ድንበሮች መሰረት ወንዞች ከተፈጥሯቸው በተለየ ፖለቲካዊ ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡ እነዚህንም ወንዞች ወሰን ተሸጋሪ ብለን እንጠራቸዋልን፡፡

ወጣት ሴት የመሆን ጣጣ




እኛ ሴቶች በተወሰነ ጊዜ በቋሚነት የምንገናኝ ሴት ጓደኞች  አይጠፉንም፡፡ የከተማዋ ካፌዎች ውስጥ የሚሆነው ይህ ቆይታችን በተለይ ወደ ሥራው ዓለም ከገባን ወዲህ ስለወንዶቻችን (በተለመደው አጠራር ባሎቻቸን) እና  በዚያው  ዙሪያ ስላሉ ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ሲሽከረከር ይቆያል፡፡ ፓለቲካ ያልተቀላቀለበት፣ ጠንካራ ማኅበራዊ ችግሮች የማይወሩበት እና ቀላል ጨዋታ የሚመስለው ይህ  ቆይታ  ከባድ የማይመስሉ ነገር ግን የወጣት ሴቶችን ሕይወት እና አኗኗር የሚያመሳቅሉ ጉዳዮችም ይነሱበታል፡፡ የሚለያዩ የማይመስሉ ጥንዶች ሕይወት “ውይ we break up እኮ”  በሚል ቀላል የትካዜ ቃል የሚጠናቀቅበት፣ “surprise…………… guys am engaged………..’’ የሚል ጬኸት የሚደመጥበት፣ አልፎ አልፎም አስቸኳይ ስብሰባ ተጠርቶ “I think am pragenat ምን ይሻለኛል” ተብሎ የሚተከዝባቸው ናቸው፡፡ ወደ “በሰለ ወጣትነት” ከገባንበት ጊዜ አንስቶ የወጣት ሴቶች ችግሮች በውበታቸው እየተሸፈኑ ወይም እየተለመዱ ሳይሆን አይቀርም መነጋገሪያ ሲሆኑ ሰምተንም  ተወያይተንባቸውም  አናውቅም፡፡ በዛ ቢባል የቁሳቁስ ፍቅርና የቸልተኝነት ነገር እያነሳን ሴቶቻችንን ማማረር ነው፡፡


ወጣት ሴት መሆን ጣጣ ነው፡፡ አመቱ ከመፍጠኑ አንስቶ የሚጠበቅብን አበዛዙ አብዛኛውን ዓመታት ባልሰከነ ውዥንብር ውስጥ እንድንከርም ያደርገናል፡፡ በዚህ ላይ የማኅበረሰቡ ግልጽነት ያጣ ጫና እና ማስፈራሪያ ለአንዲት ወጣት ሴት የመረጃ ምንጯ ጓደኞችዋ ብቻ፣ ትክክል የሚሆነውም ብዙዎቹ ጓደኞችዋ ያደረጉት ነገር ይሆናል፡፡ በትምህርት ቤት እና ከቤተሰብ ጥብቅ ቁጥጥር በአንጻራዊነት ነጻ በሚኮንባቸው በነዚህ ዓመታት የቦይ ፍሬንድ ምርጫ እና ውዝግቡ፣ የማግባት አለማግባት እና የዕድሜ ነገር ሐሳቡ ሁሉ ቀላል ቢመስሉም መስመር ካለው (focused) የሐሳብ መስመር በተደጋጋሚ ሲያናጥቡ እና ለብዙ የሚጠበቅ አቅም ያላቸውን ሴቶች ከተለመደው መንገድ ሲያስቀሩ ይስተዋላል፡፡

የመምሰል  ጣጣ

ወጣት ሴት ሆኖ ወጣት ሴቶችን አለመምሰል ችግር ነው፡፡ ሁላችንም ከአለባበስ ጀምሮ እስከ አስተሳሰብ ድረስ እንድንመሳሰል ይጠበቅብናል፡፡ ወንዶች እንዲጋብዙን ዝግጁ ሆኖ መገኘት፣ የተመጠኑ የሴት ልጅ ዕውቀቶች ላይ ብቻ ማተኮር እና መመሳሰላችንን የሚያፈጥኑ ጉዳዮች ላይ ብቻ እንድናተኩር መደረጋችን ግድ ነው፡፡ የሴት ጓደኛው በአለባበስ፣ በአወራር፣ በመግባባት ዘዬ ዘመናዊ ሴቶቸን እንድትመስል የማይፈልግ እና የማይገፋፋት ወንድ የለም፡፡ በመሠረቱ በዚህ ዕድሜ ብዙ ሚና የሚኖራቸው የወንድ ጓደኞች ራሳቸው ልዩነትን በፍጹም አይቋቋሙም፡፡ ከለመዱት የሴቶች ዓይነት ወጣ ያለች ሴት ስትገኝ የግንኙነት መስመሩ ብዙም ሳይቆይ የሚቋረጥበት ጊዜ የሚበዛውም ለዚያ ነው፡፡ “ኧረ  ሴት ልጅ ምሰይ? የምን ጎረምሳ መምሰል ነው?” የሚሉ ወላጆችም ቀላል አይደሉም፡፡ የጓደኛ እና የጎረቤት ልጆች እንደምሳሌ እየተጠሩ የመመሳሰልን አስፈላጊነት ከወላጆቻቸን ጀምሮ እስከ ወንድ ጓደኞቻችን ድረስ እንመከራለን፡፡ በዚህም ምክንያት መሆን የምንፈልገውን እና የምናስበውን ሳይሆን ወንዶቻችን እንደንሆን የሚፈልጉትን ነው እየሆንን ያለነው፡፡ ለምሳሌ ብንጠቅስ፡- ወንዶች ወፍራም የሆነች ሴት ስለማትመቻቸው ወይም ምርጫቸው አይደለችም ብለን ስለምናስብ እኛ ሴቶች ክብደት ለመቀነስ፣ ለመክሳት እና ቦርጭ ለማጥፋት ከረሃብ አድማ ያልተናነሰ የአመጋገብ ዘየ ስንከተል ይስተዋላል፡፡ ከልክ በላይ መወፈር አግባብ ነው እያልን ሳይሆን ‹ወንዶች ስለማይመቻቸው› ግን መሆን አልነበረበትም፡፡