Thursday, January 3, 2013

መጅሊሱን ከውስጥ ስንመለከተው


በመሐመድ ካሊድ

በአንድ የግል ጋዜጣ የዘንድውን አወዛጋቢ የመጅሊስ ምርጫ አስመልክቶ የተመረጡትን ሰዎች ፕሮፋይል እየተመለከትኩ ነበር፡፡ ከጎኔ የነበረ ሰው የሙስሊም ኮፍያዬን ቀና ብሎ ተመልክቶ ከበፊቱ መጅሊስ የተሻለ ዓለማዊም ሆነ ሃይማኖታዊ ዕውቀት እንዳላቸው ነገረኝ፡፡ በጋዜጣ መሸጫ ዙሪያ “ሲቪሎች” ስለሚበዙ እሱም መረጃ እየሰራ ይሆናል በሚል ግምት በአጭሩ ያለውን መስማማቴን በንቅናቄ ገልጬ ገጹን በመገልበጥ አባረርኩት (አባረረኝ)- ብቻ ያው ነው፡፡ ከዚህ ሰውዬ አስተያየት ጀምሮ እስከ ዛሬ ያማጥኩትን ለአንባቢያን ላበቃ ዘንድ እነሆ ብእሬን አነሳሁ፡፡ 

ስለ ሰላማዊ ትግል በሚወራበትና ሙስሊሙ ማኅበረሰብ ለ 1 ዓመት ሙሉ ሕገ ወጡ መጅሊስ ይወገድ ከማለት ጀምሮ እስከ መሪዎቼ ይፈቱ ከዚያም ምርጫው ውድቅ ይደረግ ጥያቄ በአወሊያ ተጀምሮ እስከ ታላቁ አንዋር መስጂድ በዘለቀው የሰላማዊ ተቃውሞ የአንድ ዓመት ክብረ በዓል እየተከበረ ባለበት ወርሐ ታኅሳስ የመጨረሻ ሳምንት ስለ በግዱ መጅሊስ ማውራት ባይመስጥም ቢያንስ ውስጣዊ አሰራሩን ታነቡት ዘንድ ከትቤዋለሁ፡፡

አዲሱ መጅሊስ

በመጅሊሱ “የአባትህ ቤት ሲዘረፍ አብረህ ዝረፍ” በሚለው ይሁን የእውነት አምነውበትና በአላማው ተመስጠው አሊያም ካድሬነት በሀይማኖት ተቋም ብዙ ተሰላፊ ስለሌለውና ሕወሓቶች ስለማይበዙበት በቀላሉ ትልቅ ካድሬ ሆኖ ለመገኘት ሲሉ አለያም የሀጅ ቢዝነስ አሪፍ ነው ሲባል ሰምተው አላውቅም ብቻ ወንድሞቻቸው አደባባይ እየጮሁ አልፈው ጥቂቶች የተወዳደሩበት በግዴታ ምርጫ ተካሂዶ እነሆ  እንደገና ተዋቅሯል፡፡ (አህመዲን አብዱላሂንም እንደስም ይጠራበት የነበረውንና ጨርቅ ከመሆኑ በቀር የአጼ ምኒሊክን ዘውድ የሚመስለውን ጥምጣሙን ተገላግሎ በኮፍያና በሸሚዝ መሀል ቦሌ ፈታ ብሎ ሲሄድ ልናየው ችለናል፡፡)

አዲሱ መጅሊስ የመጣበትን የምርጫ ሂደት ከቀበሌ መጀመሩ በታሪክ የመጀመሪያ ነው፡፡ ይህን ምርጫ ለማስተባበርም የተሰጠውም የመንግስት ሚዲያ ሽፋን ከመቼውም የተሻለ ነው፡፡ ተቃውሞውም እንዲሁ ታላቅ ነበር፡፡ ለዚህም ይመስላል በመጅሊሱ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በድግሪና በማስተርስ ድግሪ ደረጃ የተማሩ ሰዎች ለስራ አስፈጻሚነት ደረጃ መድረሳቸው፡፡ ስለነዚህ ጉዶችም ብናወራ የመጅሊሱን ሁኔታ ለመረዳት የሚረዳ ይመስለኛል፡፡

አዲሱ መጅሊስ በሸህ ኪያር ሙሀመድ ፕሬዝዳንትነት ይመራል፡፡ በዋናው የመጅሊስ ስልጣን ላይ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት እና ለስላሳው ለውሳኔ የሚቸገሩት ሙሀመድ አሊ እንደ ዋና ጸኀፊ ተወዝተዋል፡፡ በምክትል ፕሬዝዳንትነት የህዋሃት አባል የሆኑትና የቀድሞ የትግራይ ክልል የሸሪዓ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት፣የክልሉ እስልምና ጉዳይ ፕሬዝዳንትነትና ሁሉንም ስራ አስፈጻሚ አባረው የሁሉም ዞኖች ተወካይ በመሆን ሁሉን ነገር የራሳቸው ጠቅለው በመያዝ ያላቸውን የአንባገነንነት አቅም ያስመሰከሩት ሼህ ከድር ማህሙድ ተሰይመዋል፡፡ ከዚህ ውጭ ሌሎቹን ስራ አስፈጻሚዎች በሌላ ጊዜ አስተዋውቃለሁ፡፡ 

ይህ መጅሊስ በጎኑ እንዳይተኛ የሚያደርጉ ሀሳቦችን በመዳሰስ ትንሽ ልበል፡፡ መጅሊስ ማለት ሙስሊሙን ማህበረሰብ በሀይማኖታዊ ጉዳዩ የሚዎክል ተቋም እንደመሆኑ በጥባጭ ካለ ማን ጥሩ ይጠጣል እንዲሉ ብዙ ነገር አርፎ እንዳይተኛ ያደርገዋል፡፡ በዚህ ጽሁፍ የመጅሊሱን ፈተናዎች እና የፈተናውን ተዋናኞች ከዚህ በታች ባጭሩ እንዳስስ፡፡

1. የመጅሊሱ ቅቡልነት

መጅሊሱ ከድሮውም ለቅቡልነት አልታደለም፡፡ ይሁንና ያሁኑ ይባስ እንዲሉ ህዝበ ሙስሊሙ መጅሊሱን አንቅሮ ተፍቶታል፡፡በሙስሊሙ ማህበረሰብ አኳያ መጅሊሱ እመራዋለሁ የሚለው ህዝብ እየከሰሰውና እየገረመመው መኖሩ ጤናማ አይደለም፡፡  ይሁንና ያለፈው አልፏል እስኪ አንድ እድል እንስጣቸው ብሎ የሚነሳ ሙስሊም እንኳ ቢኖር በጥንቃቄ ካልተያዘ ያጡታል፡፡ ለዚህ ነው መጅሊሱ ለቅቡልነቱ የሚሰራውን ስራ ፈታኝ ነው የምለው፡፡ መጅሊሱ መልኩ ከፍቷል፡፡ ከሁሉ በፊት ፊቱ መዋብ አለበት፡፡ የመጅሊስን ክፉ ፊት ለማስዋብ ብዙ የመዋቢያ መሳሪያዎች (ኮስሜቲክሶች) የሚያስፈልጉት ሲሆን ምን ቢኳኳል ግን ፊቱ ላይ ያሉት ሁለት ቡጉንጆች ካልተወገዱ ሊዋብ አይችልም፡፡

እነዚህ ቡጉንጆች ኮማንደር ሙራድና ጀማል ሙሀመድ ሳሊህ ሲሆኑ እነዚህ እያሉ ገጽታን ማስተካከል የሚታሰብ አይደለም፡፡ እነዚህ ሁለት ሰዎች የባለፈው ስራ አስፈጻሚ ይወገድልን ብሎ ህዝብ ሲጠይቅ አብሮ ፎቷቸው ተለጥፏል፡፡ ውሎ ማደሪያቸው ሳይቀር በተለያዩ ሶሻል ሚዲያዎች ተለቋል፡፡ ቀድሞም የመጅሊሱ ማንኛውም ውሳኔ የሚወሰነው በሰላም መምሪያ ጣልቃገብነት ነው፡፡ ትምህርት፣ቁርአን፣ልማት፣ሀጅ ወዘተ.. ብቻ ሁሉም ነገር ላይ የሰላም መምሪያ ጣልቃ ገብነት ያስፈልገዋል፡፡ ይህ ኃላፊነት የስራ አስፈጻሚ ሲልም በየክፍሉ ያሉ የስራ ሓላፊዎች መሆን ሲገባው እንዴት ጠቅሎ ወሰደው? ብዬ ስጠይቅ ያገኘሁት መልስ ቢኖር መንግስት ነው የሚል ነው፡፡ ብዙዎች እነደውም የሰላም መምሪያው ፕሬዘዳንቱን ማዘዙ የአደባባይ ሚስጥር እንደሆነ ይናገራሉ፡፡

አዲሱ መጅሊስ በኮከብነት የሚመሩት ሙስሊሙን ሲያተረማምሱ የኖሩት እነ ጀማል ሙሀመድ ሳልህ ( የእውነት ስሙ ገብሬና ለትግል ሲባል ስሙ ከነአያቱ የተቀየረ ተብሎ የሚታማ) በዲሲፕሊን ከጉለሌ ከተማ ፖሊስ ጣቢያ የተሰናበተው ኮማንደር ሙራድ ፎቷቸው ከሌሎች ጋር በመሆን ለህግ እንዲቀርቡ በዚህ ሳምንት ዓመቱን በሚያከብረው ድምጻችን ይሰማ የፊስ ቡክ ገጽ የለጠፋቸው ናቸው፡፡

ይታያችሁ ኮማንደር ሙራድ የመጅሊስ ጽ/ቤት ኃላፊ ሆኖ ሲሾም ያለ ሀፍረት በሴትነታቸው የጠየቃቸው ሁለት ሴት ጓደኛሞች የመጅሊሱ ሰራተኞች ምን ይሰማቸዋል? ገብሬ እንደዱሮው ሁሉ ስራ አስፈጻሚውን አመራርና አመራር ያልሆነ ብሎ ከፍሎ ሀሳብ በማቅረብ የፈለገውን ስራ አስፈጻሚ ከስራ ሲያሳግድ ማየት እንዴት…..እንዴት….. እንዴት…ቅቡልነትን ያመጣል? 

የፌደራል መጅሊስ 400 የሚሆን ሰራተኛ አለው፡፡ ይሄ ሰራተኛ ጉዳዬ ካማረው ለአደባባይ አሳልፎ ይሰጥሃል፡፡ በተለያዩ ጋዜጦች ላይ ካየናቸው የሂሳብ ሰነዶች ጀምሮ ለየመንግስት መስሪያ ቤቱ እስከገቡት ሰነዶች ድረስ ያለው ሚስጥር የወጣው በተለያዩ ሰራተኞች ነው፡፡  ባጭሩ የመጅሊሱ ሰራተኛ ማለት ወሳኝ ምስክር ማለት ነው፡፡ ምክር ቤቱ የስራ ባህሉ ክፉኛ የተጎዳ ከመሆኑ የተነሳ እድሜ ለነ እንቶኔ አብዛሀኛው ሰራተኛ ከስራ ይልቅ ወሬ ማቀበል እንደሚያሳድግ ገብቶት የነገር ማቀበል ሚና መጫወት ህሊናው የፈቀደ እያቀበለ ህሊናው ያልፈቀደው ደግሞ በስራ የሚመጣ ነገር እንደሌለ በመገንዘብ ቀኑ ሲመሽና ሲነጋ እየታዘበ ልጆቼን ላሳድግ የሚል ሆኗል፡፡

ከዚህ ባሻገር የአህሉሱና ወለወጀማአ እና ሱፊ ሰለፊ ጉዳይ ገና አነጋጋሪ ነው፡፡ የየእስልምና ምክር ቤቶቹ ምርጦች የመጡት በሱፊ መስፈርት ነው፡፡ ህዝቡ ደግሞ አንድነት እያለ ነው፡፡ የመጅሊሱ አመራሮች ቃለ መሃላ የፈፀሙትም በዚሁ መልኩ ነው፡፡ ሙስሊሙን ማህበረሰብ በአህሉሱና ወለወጀማዓ አስተምህሮ ለመምራት! ታዲያ የተመረጡበት መስፈርት ተቀይሮ አንድነትን ከግምት ውስጥ ያስገባ አካሄድ ቢሞከር ቅቡልነትን ለማግኘት ያግዝ ይሆናል፡፡

ሶስተኛው ጉዳይ የህዝብ ግንኙነት ስራ በአብዛሀኛው ቅቡልነትን ከመገንባት አኳያ ሚናው ከፍተኛ ነው፡፡ ይሁንና መጅሊስ ገብታችሁ የህዝብ ግንኙነት ክፍሉን ብትመለከቱ በሰው ሃይል ረገድ በእጅጉ ተጎድቷል፡፡ ለዚህ ይመስላል አዳዲሶቹ ስራ አመራሮች ውሉ ጠፍቶባቸው ቢሮዎችን በመቀላቀል ትላልቅ ቢሮዎችን በመፍጠርና ቀለም በመቀባት ስራ ላይ የተጠመዱት፡፡ አዲሶቹ መጅሊሶች ከገቡ ሶስት ቢሮዎች ፈርሰው አንድ ትልቅ ቢሮ እንዲሆን ተደርጓል፡፡ ሁለት የትውውቅ መድረኮች ተከፍተዋል፡፡ ……ወዘተ፡፡

2. የመጅሊሱ የውስጥ መዋቅር

መጅሊስ በውስጡ የተለያዩ የልማት ተቋማት ያሉት ሲሆን የአወሊያ ተቋማት እና የልማት ኤጀንሲ እንዲሁም በመጅሊሱ የተለያዩ ዘርፎች ስር ያሉ ክፍሎች ይገኛሉ፡፡ በነዚህ ተቋማት ስር ከ 400 በላይ ሰራተኞች ያሉ ሲሆን ከትምህርት ዝግጅትና ልምድ አኳያ ጥሩ ሊባል የሚችል አቅም ያላቸው ሰዎች አሉ፡፡ በዚህ ተቋም ያለፈ የስራ ሂደት ታዲያ ይህን የሰው ሀይል በአግባቡ ስራ ሊያሰራ የሚችል አደረጃጀትም ሆነ ህግና ደንብ የሌለው በመሆኑ ሰራተኛው በማያውቀው ምክንያት በዙሪያው ሲከናወን ቆይቷል፡፡ ይህ በዚህ ሂደት የተዳከመና የተሰላቸ ሰራተኛ ስለመጅሊሱ ከስራ አስፈጻሚዎች በላይ ያውቃል፡፡ መጅሊሱ ሲቋቋም ጀምሮ አዲሱን በመቀበል እና ነባሩን በመሸኘት ከ 15 ዓመታት በላይ ከመጅሊሱ ጋር የቆዩ ሰራተኞች ከ1987 ጀምሮ የነበሩ መጅሊሶችን ተመልክተዋል፡፡ በንግግር የተካኑ የነበሩት መጅሊስ ስራ አስፈጻማች በባዶ ተስፋ ሲደልሉት ቆይተዋል፡፡ በመሆኑም የመጅሊሱ ሰራተኞች ተጨባጭ ለውጥ በተግባር ካላዩ ለመጅሊሱ የኔነት ስሜት ፈጽሞ ሊሰጡት አይችሉም፡፡

የመጅሊሱ ነባር ስራ መረጃ አያያዝም ደካማ በመሆኑ የመጅሊሱ ስራ አስፈጻሚዎች በቀጥታ ወደ ስራ ለመግባት የሚችሉበት ሁኔታም አይኖርም፡፡ መጅሊሱ ያለው የስራ መመሪያም ሆነ መዋቅር በሰኔ 1993 ዓ.ም የተዘጋጀ ሲሆን አሁን ካለው መዋቅር ጋር ምንም አይነት ግንኙነት የሌለው እስከሚመስል ድረስ በሂደት ተቀያይሯል፡፡ የመዋቅሩን ማርጀት ተከትሎም በርካት መደቦች በተፈለገው ጊዜ ሊቀጠር በተፈለገው ሰው ልክ ሲፈጠሩ ቆይተዋል፡፡በዚህ ሂደት የተጠራቀሙ ሰራተኞች ቀን አሳላፊ ሆነው ተቀምጠዋል፡፡ የስራ አስፈጻሚ ሚስት፣ልጅ፣እህት ባጠቃላይ ዘመድ አዝማድ ሆነው ግቢውን የረገጡና በዛው የቀሩትን ብዛት መጅሊሱ ይቁጠረው፡፡ ከእንግዲህ ይህን ሰራተኛ ነው ሁሉንም የሚመጥን የትምህት ዝግጅትና ልምድ ላይ ተመስርቶ ስራ ሰጥቶ ወደጤናማ ተቋም አካል መቀየር የሚቻለው፡፡

3. የውጭ እጆች

ሌላኛው የመጅሊስ ጣጣ ሆኖ የሚገኘው የውጭ እጆች  ልብ በሉልኝ ፡፡ ይህ ምክር ቤት በሀጅና ኡምራ ስራ ከብዙ ድርጅቶች ጋር ሲሰራ ቆይቷል፡፡ በዚህ አወዛጋቢ የሀጅና ኡምራ ስራ የመስራት አበሳ ከተቋሙ ጋር ያነካካቸው ሰዎች ሁሉ ምንጌዜም ስራ አይፈቱም፡፡ ከመጪው ስራ አስፈጻሚ ጋር ሲስማሙ አብረው በመስራት ሳይስማሙ ይሄኛውን ጥለው ለነሱ የሚመቸውን ለማስመጣት ጥረት ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡ ይሄ እጅ ምንጊዜም ስራ አይፈታም፡፡ ታዲያ ይህ እጅ አነዴ በጋዜጣ ሌላ ጊዜ በመጽሄት፤ ካልሆነም በተለያዩ የመንግስጥ የደህንነት መዋቅሮች ውስጥ አልፎ መምጣቱ ነው መከራው፡፡ አላሰርቅ ያለ ስራ አስፈጻሚ በሆነ ምክንያት አሸባሪ እንደማይባልና ከስራ እንደማይታገድ ምን ዋስትና አለን??

4. የመጅሊሱ የሰላም መምሪያ

ሌላኛው የመጅሊሱ ጣጣ የመጅሊሱ የሰላምና መረጃ መምሪያ ነው፡፡ የቀድሞ መጅሊስ አመራሮች መጅሊሱ በተለያየ ጊዜ ስልጣኑን ማቆየት ሲሳነው የዙፋኑ ጠባቂዎች እንዲሆኑ ለማድረግ ያመጣቸው የሚታወቅ ሙያም ሆነ ትምህርት የሌላቸው ሰዎችን ያቀፈ ክፍል ነው፡፡(ይህ ክፍል ከላይ የጠቀስኳቸውን ኮማንደር ሙራድን አቶ ገብሬ (ጀማል ሙሀመድ ሷሊህን) ጨምሮ 30 ሰራተኞችን የያዘ ነው፡፡ ይህ ቡድን በሀጅ ጉዞ 43434 ብር ተሸፍኖለትና ተጨማሪ 30000 ብር አበል ተሰጥቶት ሀጅን ሊቆጣጠር ሳይቀር ሳውዲ ይሄዳል፡፡ በመጅሊሱ ምርጫ ሂደትም በተለይም ዋና ጸኀፊ የነበረውን አቶ አልሙሀመድ ሲራጅን ለማስመረጥ እልህ አስጨራሽ ትግል ውስጥ እንደነበረ በሰፊው ተወርቷል፡፡ ይህ ክፍል የመጅሊሱ ግል ማህደሩ ውስጥ የሁለተኛ ደረጃ መረጃ እንኳ የሌለው መሆኑን የሚያመለክተውን የመጅሊሱን ሰራተኛ በግጭት አፈታት ከአምስተርዳም ዩኒቨርስቲ ማስትሬት ድግሪ አለው ብሎ በኢትዮ ሙስሊም ጋዜጣ ሲያስነበበን ነው ተብሎም ይታማል፡፡

በአዲሱ የመጅሊስ ምርጫ የተመረጡት የመጅሊስ ፕሬዝዳንት የትምህርት ደረጃ ቀድሞ ተነግሮን ነበር፡፡ይህ በኋላ ላይ ሲጣራ ሃሰት ሆኖ የተገኘው ይህ የተመራጮች መረጃ የተቀነባበረው እና የሚነዛው በዚሁ ክፍል ስር ለዚህ ስራ በተሰማሩ ሰራተኞች መሆንም የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡

 የፕሬዝዳንቱ ቤተሰቦች የጉዞ ወኪል ቢዝነስ ያላቸው ሲሆን ከድፍን ኦሮሚያ ይህን አይነቱን ሰው ማምጣቱ በአንድ በኩል ለሀጅ ሙስና የተመቻቸና በልቶ የሚያበላ ነው የሚል ሃሜት በአዲሱ አመራር ላይ በሰፊው እየተወራ ቢሆንም የሰላም መምሪያው የግልና  ተቋማዊ ድጋፍ አዲሱም መጅሊስ ከቀድሞው የተለየ እንዳልሆነ ያመለክታል፡፡ አዲሱ ፕሬዝዳንት ግቢ ከገባ ጀምሮም ከሰላም መምሪያ ጋር ጠንካራ ግንኙት እንዳለው መገንዘብ ተችሏል፡፡

እንደመውጫ

የሕዝብ ተሳትፎ ለልማት ወሳኝ እንደሆነ ሁሉ ለሀይማኖትም ወሳኝ ነው፡፡ እና እስኪ ትንሽ ቢያንስ የተማረውን ሙስሊም አሳትፉ፡፡ አቅጣጭ ቀይሱ፡፡ ለሀገር ልማት አጋዥ የሁኑ አያሌ ነገሮች መስራት ይቻላል፡፡ አዲሱ ስራ አስፈጻሚ ላይ ተስፋ መጣል የመጡበትን መንገድ መርሳት ቢሆንም ከድሮው አሰራር እቅፍ ለመውጣት መሞከር ከቻሉ አሁንም የሙስሊሙ እውነተኛ ተወካይ ለመሆን መሞከር ይቻላል፡፡ ብዙ የሀይማኖት እውቀት ባይኖረኝም በሰማይ ቤት አካውንት እንዳለን አምናለሁ፡፡ ተስፋ አልቆርጥም፡፡ ታሪክና ፈጣሪ መዝግበው እንደሚይዙንም አለመርሳት ነው፡፡

ውድ አንባቢያን የመጅሊሱ የቅርብ ሰዎች ብዙ ሳይዘጋጁና ሳይጨነቁ ይህን ሁሉ መረጃ ሰጥተውኛል፡፡ ለግል ደህንነታቸው ሲሉም የተወሰነውንም ዝርዝር ነገር እንደማይነግሩኝ ገልጸውልኛል፡፡ ይሁንና በሂደቱ ያወቅኩት ነገር ቢኖር በመጅሊሱ የተማሩ ሰዎች በዙሪያው እንዳሉትና ያሉትን ሰራተኞች በአግባቡ ቢጠቀም ውጤታማ የመሆን እድል እንዳለው ነው፡፡

ይሁንና ሰራተኞቹ  የሰላም መምሪያ ግን ለሰራተኛውና ለስራ አስፈጻሚ አለመገናኘት ብዙ ሚናዎችን ከመጫወት አይቦዝንም ብለው ያሙታል፡፡ አዲሱ ስራ አስፈጻሚ ይህን ሰላም መምሪያ ካለው ሚና ለማቀብ ደፍሮ ሊያፈርሰው ይችላል የሚል ተስፋም እንደሌላቸው ነግረውኛል፡፡ በዚህ አጋጣሚ ይህን ጽሁፍ ለሚያነብ ሙስሊምም ሆነ ሌላ ወገን የመጅሊስ ጉዳይ የሙስሊሞች ብቻ ሳይሆን የሁላችንም በመሆኑ ለመስተካከሉ የቻልነውን ሁሉ ጥረት እንድናደርግ እላለሁ፡፡                   
----- 
ጸሐፊውን ለማግኘት በኢሜይላቸው (mkahlid9@gmail.com) ይጻፉላቸው፡፡

No comments:

Post a Comment