Tuesday, November 4, 2014

የዛሬው የዞን9 ጦማርያን የፍርድ ቤት "ግርግር"


#FreeZone9bloggers #FreeEdom #FreeTesfalem #FreeAsemamaw #Ethiopia 
ዛሬ ከጠዋቱ ሶስት ሰአት ጀምሮ ይሰየማል ተብሎ ሲጠበቅ የነበረው የጦማርያኑ እና የጋዜጠኞቹ ችሎት ከወትሮው በተለየ ጥብቅ ጥበቃ ለአጭር ደቂቃዎች ተከናውኗል፡፡ 

በነሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ ከተከሰሱት 10 ተከሳሾች ( አንድ በሌለችበት) ዘጠኙ ፍርድ ቤት የቀረቡ ሲሆን ሲሆን በእለቱ ፍርድ ቤቱ የክሱ ላይ የተከሳሽ ጠበቆች ያቀረቡትን የመጀመሪያ ደረጃ የክስ መቃወሚያ እና የአቃቤ ሀግን መልስ አይቶ ብይን ይሰጣል ተብሎ ተጠብቆ ነበር፡፡ 

ችሎቱ ከተለመደው አዳራሽ ይከናወናል በሚል እሳቤ ወዳጅና ቤተሰቦች ቢገኙም መጀመሪያ በደፈናው ወደ ችሎት አዳራሽ መግባትን በመከልከል በማስከተል ደግሞ የተወሰኑ የቤተሰብ አባላት ችሎት ውስጥ አንዲገቡ ተደርጎ ነበር፡፡ ከአፍታ ቆይታ በኋላ ግን ችሎቱ ውስጥ ያለው የድምጽ ማጎያ ስለማይሰራ ይበልጥ አነስተኛ ወደሆነ ክፍል ችሎቱ አንዲዘዋወር ተደርጓል፡፡ በመሆኑም የተከሳሽ ወዳጅና ቤተሰቡ ባልታደሙት አጭር ችሎት ሁለት የግራ እና የቀኝ ዳኞች አዲስ የተለመወጡ በመሆናቸውና ኬዙን ስላልመረመሩት ለህዳር ሶስት ( ኖቬምበር 12) ተለዋጭ ቀጠሮ በመስጠት የዛሬው ቀጠሮ በአጭሩ ተዘግቷል፡፡ 

እስር ላይ የሚገኙት ሴት ተከሳሾች ጉብኝት መብትን አስመልክቶ ፍርድ ቤቱ ባለፈው ቢሰየምም ለውጥ አለመኖሩን በመጥቀስ አቤቱታቸው ያሰሙ ሲሆን የማረሚያ ቤት ሃላፌው በሚቀጥለው ቀጠሮ መጥተው አንዲያስረዱ ፍርድ ቤቱ ትእዛዝ ሰጥቷል፡፡ 

ዛሬ ከፍተኛ ግርግር እና የቦታ እጥረት አንዲሁም ወላጆች መንገላታት የታየ ሲሆን ጦማርያኑ እና ጋዜጠኞቹ እነደቀድሞው ችሎት ነጭ ልብስ በመልበስ በመልካም ሁኔታ ላይ አንደሚገኙ ታይቷል፡፡ 

በተያዘ ዜና የጦማርያኑን የዋስትና ጥያቄ አስመልክቶ ጠበቃቸው ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ የተባለ ሲሆን ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ነገ ጠዋት በሚሰየመው ችሎት ውሳኔ ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ( አጋርነታችሁን የምታሳዩ የዞን 9 ነዋሪያን ነገ ስድስት ኪሎ በሚገኘው የጠቅላይ ፍርድ ቤት ችሎት በመገኘት አጋርነታችሁን እነድታሳዩ ጥሪ እናቀርባለን)

No comments:

Post a Comment