Showing posts with label Sociopolitics. Show all posts
Showing posts with label Sociopolitics. Show all posts

Sunday, February 7, 2016

እከላከላለሁ!


በበፍቃዱ ኃይሉ

ከ18 ወራት እስር በኋላ ስንፈታ ዐ/ሕግ ያቀረባቸው ማስረጃዎች፣ በሁለት “ምክንያቶች” በወንጀል ሕጉ (አንቀጽ 257/ሀ) ግዙፍ ያልሆነ “በጽሑፍ ለአመፅ የማነሳሳት” ጥፋት ተከላክዬ ነጻ መሆኔን የማረጋገጥ ሸክሙን ወደ እኔ አዙሮታል፡፡ ምክንያቶቹ እነዚህ ናቸው፤

፩) “የግብጽ ዓይነት አብዮት ኢትዮጵያ ውስጥ እንዲነሳ የሚቀሰቅስ ጽሑፍ መጻፉን ለፖሊስ በሰጠው ቃል …‹የእውነት ቃል መስጠቱን› አምኗል” የሚልና፣

፪) ዐ/ሕግ ባቀረባቸው ሰነዶች “በፌዴራሉ ሕገ-መንግሥት የተቋቋመውን ስርዓት ለማፍረስ በጽሑፍ አማካኝነት የቀሰቀሰ ለመሆኑ የተጠቀሱት ማስረጃዎች የሚያስረዱ በመሆኑ” የሚል ናቸው፡፡

የእምነት ወይስ የእውነት ቃል?

ሳይቤሪያ (የማዕከላዊ ጨለማ እስር ቤት) ውስጥ ያለ ማንኛውም ሰው ለምርመራ ወጥቶ ሲመለስ ክፍሉ ውስጥ ያሉ ታሳሪዎች በሙሉ የሚጠይቁት የመጀመሪያው ጥያቄ “አመንክ?” የሚል ነው፡፡ ታሳሪዎቹ ስለምርመራው የሚያውቁት ነገር ስላለ አይደለም ይህንን ጥያቄ የሚጠይቁት፡፡ ነገር ግን የማዕከላዊ ምርመራ በተፈጥሮው፣ በተለይ በሽብር ለተጠረጠረ ሰው “አንዳች ወንጀል እመን” በሚል ስለሆነ ነው፡፡ ሒደቱም፣ በዱላ ነው፡፡ ማዕከላዊ ቆይተው ክስ የተመሰረተባቸው ብዙዎቹ ተጠርጣሪዎች ፍርድቤት ክስ ከተመሰረተባቸው በኋላ “ተከላከሉ” የሚባሉት ለፖሊስ የሰጡት የእምነት ቃል ነው፡፡ ፖሊስ በሥነ ስርዓት ሕጉ ቁጥር 27 መሠረት የተጠርጣሪ ቃል የሚቀበልበትን ሰነድ ሲያስፈርም “… ይህንን በነጻ የሰጠሁትን የእምነት ቃሌን አንብቤ ወይም ተነቦልኝ ፈረምኩ” የሚል ዓ/ነገር ከግርጌው ይጨምርበታል፡፡

ማዕከላዊ ውስጥ የተከሳሽን ቃል በነጻ አእምሮው በፈቃደኝነቱ እንዲሰጥ ማድረግ ነውር ነው፡፡ አንድ ሰው ማዕከላዊ ውስጥ ሲመረመር፣ ክብሩ በስድብ ተዋርዶ፣ እየተደበደበ ነው፡፡ የሥነ ስርዓት ሕጉ አንቀጽ 27/2 ‹ማንኛውም ተጠርጣሪ ለፖሊስ ቃሉን ሲሰጥ በነጻ ፈቃዱ መሆኑ መረጋገጥ እንዳለበት፤ ቃል ያለመስጠት መብቱም የተጠበቀ እንደሆነ› ይደነግጋል፡፡ ይህን ግን የማዕከላዊ ፖሊሶች የሚያውቁት አይመስልም፡፡



እኔ ላይ የደረሰው ብቻ ሕግ ለይስሙላ የሚወጣባት እንጂ በሕግ አስከባሪው አካል እንኳን የማይከበርባት ኢትዮጵያ ውስጥ እንደምንኖር ያሳያል፡፡ ማዕከላዊ ውስጥ ቃሌን ለፖሊስ ስሰጥ እንኳን እንደዕቅድ ይዤ ልንቀሳቀስባቸው፣ በመርሕ ደረጃ እንኳን የምቃወማቸውን ነገሮች “አዎ፣ ላደርግ አስቤ ነበር (ማለትም ‹አመፅ ላነሳሳ ጽፌያለሁ›)” ብዬ መርማሪ ፖሊሶች ሲያሻቸው እኔ የተናገርኩትን ወንጀል ሊሆን በሚችልበት መንገድ እየጠመዘዙ፣ ሲያሻቸው ደግሞ ጭራሹኑ እኔ ያላልኩትን ፈጥረው እየጻፉ ያመጡትን የእምነት ቃል አስፈረምውኛል፡፡ ሲደበድቡኝ የከረሙት ሕሊናቸውን በወር ደሞዝ የሸጡ መርማሪዎቼ ያለምንም የሕሊና ወቀሳ የእኔ ቃል ከተባለው ከራሳቸው ቃል ግርጌ “የእውነት ቃሌ ነው” ብለው ጽፈውበታል፡፡ ፍርድ ቤቱም ምንም እንኳን በማዕከላዊ የተጠርጣሪ ቃል በነጻ እንደማይገኝ ከበቂ በላይ በብዙ ተከሳሾችን ጉዳይ በመመልከቱ የሚረዳ ቢሆንም፣ መረዳት ስላልፈለገ “አምኗል” ብሎኛል፡፡ እርግጥ ነው አምኛለሁ፤ በኃይል ፊት ጀግና መሆን ስላልቻልኩ ያላሰብኩ፣ ያላደረግኩትን አምኛለሁ፡፡ እምነቴ ግን እውነቴ አልነበረም፡፡ ወትሮም እኔ የኃይል ትግል ውስጥ አይደለሁምና ኋላም ሆነ ወደፊት በኃይል ፊት የመጀገን ጀብደኛ ሕልም የለኝም፡፡ እስከአቅሜ ጠብታ ድረስ ለፍትሐዊነት የምታገለው ስመታ እየወደቅኩ ነው፤ እረፍት ሳገኝ እየተነሳሁ!

ፍ/ቤቱም ይሁን ከሳሼ መንግሥት ግን መከላከል ሳያስፈልገኝ ቃሉ የኔ አለመሆኑን ሊረዱ የሚችሉባቸው በርካታ ዕድሎች ነበሯቸው፡፡ ጥቂቶቹን ቀጥሎ እንመለከታለን፣

Wednesday, February 3, 2016

የአንድ ሰው ኃይል፤ በአንዲት ሴት ገድል ሲፈተሽ



በበፍቃዱ ኃይሉ

አንድ ሰው ብቻውን የሚወስደው እርምጃ፣ እሺታው ወይም እምቢታው ለብዙኃን ለውጥ ያመጣ ይሆን?

ልክ የዛሬ 97 ዓመት (ጥር 26፣ 1905) አላባማ/አሜሪካ ውስጥ ሮዛ ፓርክስ ስትወለድ፣ ከ97 ዓመት በኋላ እና ከትውልድ አገሯ ብዙ ሺሕ ማይሎች እና ሦስት ትውልዶች በላይ ርቄ የምገኘው እኔ ታሪኳን በጨረፍታ ለመጻፍ የኮምፒዩተር የቁልፍ ሰሌዳ እንደምነካካ ማን ሊገምት ይችላል? የአንዲት ነጠላ ሮዛ፣ የአንዲት ነጠላ ቀን፣ ነጠላ እምቢታዋ ግን ይህንን የማይገመት ታሪክ ሊፈጥር ችሏል፡፡

ሮዛ ፓርክስ የዛን ዕለት “እምቢ” ባትል ኖሮ፣ ምናልባትም የጥቁሮች የሲቪል መብቶች ትግል ባልታወቀ አቅጣጫ ሊጓዝ ይችል ነበር፡፡ ምናልባትም ደግሞ ዛሬ በሠላማዊ ታጋይነቱ አርኣያ የምናደርገው ማርቲን ሉተር ኪንግ (ትንሹ) ጭራሹን ይህንን መክሊቱን የሚያወጣበት አጋጣሚ ሳያገኝ ተድበስብሶ ያልፍ ነበር፡፡

ቀኑ ኅዳር 21፣ 1948 ነበር፤ ሐሙስ ዕለት፡፡ ጀምበር ስታዘቀዝቅ ሮዛ ከሥራዋ ወጥታ ወደቤቷ ለመሄድ የሞንቶጎምሪ ከተማ የሕዝብ አውቶቡስን ክሊቭላንድ ጎዳና ላይ ተሳፈረች፡፡ የአውቶቡሱ ሹፌር “እሱ በሚነዳው አውቶቡስ ሁለተኛ አልሳፈርም” ብላ የማለችለት ጄምስ ብሌክ መሆኑን ሮዛ አላወቀችም ነበር፡፡ ከ12 ዓመት በፊት ሮዛ፣ ጀምስ በሚነዳው አውቶቡስ ውስጥ ገንዘቧን ከፍላ በመሳፈር ለጥቁሮች በተከለለው ቦታ ሄዳ ስትቀመጥ፣ ‹የገባሽበት የፊተኛው በር የነጮች መግቢያ ነው ውጪና መልሰሽ በኋላ በር ግቢ› ሲላት “አላደርገውም” በማለት በዝናብ ውጪ ቆማ ጥሏት ሄዷል፡

የሞንቶጎምሪ ከተማ አውቶቡሶች በዘመኑ ሕግ መሠረት የአውቶቡስ ውስጥ መቀመጫዎች የጥቁሮች እና የነጮች ተብለው ተከፋፍለው ነበር፡፡ የመጀመሪያዎቹ አራት መደዳዎች ለነጮች ብቻ የተከለሉ ናቸው፡፡ ለጥቁሮች ወደኋላ ላይ አንዳንድ ወንበሮች ይተዉላቸው ነበር፡፡ ምንም እንኳን 75 በመቶ የሚሆኑት ተሳፋሪዎች ጥቁሮች ቢሆኑም መሐል አካባቢ ያሉት ወንበሮች ነጮች የራሳቸውን መደዳ እስኪሞሉ ድረስ ጥቁሮች እንዲቀመጡ ይፈቀድ ነበር፡፡ በልምድ ግን የአውቶቡስ ውስጥ ተቆጣጣሪዎች ባሱ ውስጥ ያሉ ነጮች በሙሉ መቀመጫ እስኪያገኙ ድረስ ጥቁሮችን ከወንበራቸው ያስነሷቸው ነበር፡፡ ይህ ልምድ እና ኢፍትሓዊ ሕግ ግን ለእምቢ ባይዋ ሮዛ ፓርክስ እያደር የማይለመድ ነገር ነበር፡፡ ለሮዛ ፓርክስ በልጅነቷ አውቶቡሶች “የጥቁር” እና “የነጭ” ሁለት ዓለም መኖሩን ያረዷት የልዩነት ማሳያዎቿ ናቸው፡፡

ጄምስ ብሌክ ዝናብ ላይ ጥሏት ከሄደ ከ12 ዓመታት በኋላ ሹፌሩ እሱ መሆኑን ሳታውቅ ሮዛ ፓርክስ ጄምስ በሚያሽከረክራት አውቶቡስ ውስጥ ገባች፡፡ ለ“Colored” (ነጭ ያልሆኑ) ተሳፋሪዎች መቀመጥ የሚፈቀድላቸው ቦታ ላይ ሄዳ ተቀመጠች፤ ከሷ ሌላ ሌሎች ሦስት ጥቁሮችም እዚያው ተቀምጠዋል፡፡ ሌሎች ሁለት ነጮች ባሱ ከሞላ በኋላ ገቡ እና ቆሙ፡፡ ጀምስ ብሌክ መጥቶ “Colored” የሚል ምልክት ያለበትን ተንቀሳቃሽ መጠቆሚያ ወደኋላ አንቀሳቀሰውና ሮዛ ፓርክስና ሌሎቹ ጥቁሮች ለነጮቹ ወንበራቸውን እንዲለቁ ጠየቃቸው፡፡ ሮዛ ፓርክስ ያንን ቅፅበት ከዓመታት በኋላ ስታስታውሰው እንዲህ ነበር ያለችው፤

“When that white driver stepped back toward us, when he waved his hand and ordered us up and out our seats, I felt a determination cover my body like a quilt of a winter night.” (“ያ ነጭ ሹፌር ወደእኛ መጥቶ ከወንበራችን ሊያስነሳን እጆቹን እያወናጨፈ ሲያዘን፣ የቁርጠኝነት ስሜት ልክ እንደክረምት ድሪቶ እላዬ ላይ ሲከመር ነው የተሰማኝ፡፡”)

“ተነሱ” ለሚለው ትዕዛዝ ሌሎቹ ሦስት ጥቁሮች በእሺታ ወንበራቸውን ለቀቁ፡፡ ሮዛ ፓርክስ ግን በመነሳት ፈንታ ወደመስታወቱ ጥግ ወዳለው ወንበር ፈቀቅ አለች፡፡

Tuesday, January 19, 2016

“ልማታዊ” የትሮይ ፈረስ በኢትዮጵያ



በበፍቃዱ ኃይሉ

ጥንት፣ ዐሥር ዓመት ከዘለቀ የግሪክ እና ትሮይ ጦርነት በኋላ ግሪኮች ሰለቻቸው እና መላ ዘየዱ። ግዙፍ የጣውላ ፈረስ ገንብተው ውስጡ የተመረጡ ወታደሮችን አስቀምጠው ሸሹ። ይህንን እንደ ድል የቆጠሩት ትሮዮች ለድላቸው መታሰቢያ ይሆን ዘንድ ፈረሱን ጎትተው ከተማቸው መሐል አቆሙት፡፡ በውድቅት ለሊት፣ ፈረሱ ውስጥ የተደበቁት ግሪኮች ወጥተው የትሮይ ከተማን በማውደም በጦርነቱ አሸናፊነት ተቀዳጁ እስከወዲያኛው ይባላል። ዛሬ-ዛሬ በመላው ዓለም “የትሮይ ፈረስ” (Trojan Horse) የሚለው ሐረግ ‹ለእኩይ ዒላማ መሸሸጊያነት የሚሰጥ መልካም መሳይ ምክንያት› የሚለውን ለመግለጽ ይጠቅማል።


ኢትዮጵያ ውስጥ ባለው የገዢው ፓርቲ ብያኔ መሠረት የኢትዮጵያ ችግር የሠላም፣ የልማት እና የዴሞክራሲ (እንደ ቅደም ተከተላቸው) ነው። ሦስተኛው ለሁለተኛው፣ ወይም ሁለተኛው ለአንደኛው ሲባል ሊጨፈለቁ ይችላሉ። ሦስቱ አብረው እንደሚገኙ ሳይሆን፣ በተራ በተራ እንደሚረጋገጡ ይደሰኮራል፡፡ ሠላም ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መኖር አለበት የሚለው የኢሕአዴግ መደምደሚያ የኦጋዴንን፣ የጋምቤላን እና በቅርቡ ደግሞ (በማስተር ፕላኑ ሳቢያ) የኦሮሚያን ሕዝባዊ ጭፍጨፋዎች ለማስተባበል (to justify) ከመዋሉም በላይ ብዙ የተሞተለትን የባድመን መሬት አሳልፎ መልሶ አስከመስጠት አስደርሷል። “ለሠላም” ሲባል! አንፃራዊ ሠላም ባለበት ጊዜ ደግሞ ዴሞክራሲ ለልማት በሚል ሰበብ እየደማ ነው። በሌላ በኩል የዚሁ ብያኔ ባለቤት ኢሕአዴግ “ዴሞክራሲ ለኢትዮጵያ አማራጭ አይደለም፣ ግዴታ ነው” ይላል። ስለዚህ ‹ልማትና ዴሞክራሲን አብረን እያስኬድን ነው› የሚል ነቢብ እየደሰኮረ በሌላ አጀንዳ ደግሞ መልሶ ‹ለልማት ሲባል ዴሞክራሲ ይ ቆይ፤ የድኃ ሕዝብ ቀዳሚ ጥያቄ ዳቦ ነው› በሚል ዴሞክራሲን ጥያቄ እንደቅንጦት እቃ ጥያቄ ቸል ይለዋል። የሁሉም ነገር ታዛቢዎች ‹አለ የሚባለው ልማትስ የታለ?› ብለው መጠየቃቸው አልቀረም።

እውን ልማትና ዴሞክራሲ ይጋጫሉ?

ቻይናና ሕንድ፣ ሁለቱም፣ ልማታዊ አገረ-መንግሥት (developmental state) የሚል ማዕረግ አግኝተዋል። በሁለቱ መካከል ያለው ልዩነት ሕንድ ዴሞክራሲያዊ መሆኗ ላይ ነው። ፋሪድ ዘካርያ  “The Post-American World” ባሰኘው መጽሐፍ ሕንዶችን “በየዓመቱ በአማካይ 9 በመቶ የሚያድግ ኢኮኖሚ ይዘው በመሪዎቻቸው የማይደሰቱ ሕዝቦች ናቸው” ይላቸዋል። በየምርጫው መሪ ይቀያይራሉ። ቻይኖች ግን ለዚህ አልታደሉም። ነገር ግን እነሱ በፈንታው ‹ታድለናል› የሚሉለት ነገር አለ።

ፋሪድን አንድ የሕንድ ባለሥልጣን እንዲህ ብለውታል፡- “በፖለቲካው ረገድ ሕዝባዊነትን የሚያስገኙ ብዙ ቂላቂል ተግባሮችን መፈፀም አለብን።… እነዚህ ነገሮች የረዥም ጊዜ የኢኮኖሚ ዕቅዶቻችንን ያደናቅፋሉ። ነገር ግን ደግሞ ፖለቲከኞች በአጭር ጊዜ ውስጥ የሕዝብ ድምፅ ያስፈልጋቸዋል።…” አርክቴክት ኖርማን ፎስተር የተባለ ሰውም ይህንኑ የሚያጠናክር የሚመስል ነገር ለፋሪድ ነግሮታል። “በሕንድ፣ የኸርትሮው 5ተኛ ተርሚናልን ለመገንባት፣ የአካባቢ ተስማሚነት ቅኝት (environmental review) ለማድረግ የወሰደበት ግዜ፣ በቻይና ቢሆን የቤጂንግ አየር ማረፊያን (የኽርትሮው 5ቱንም ተርሚናሎች ቢደመሩ የሚበልጠውን) ጨምሮ ለመፈፀም የሚበቃ ጊዜ ነው።” ቻይናዎች የዴሞክራሲ “ጣጣ” የለባቸውም፤ ኮሚኒስቶቹ ይህንን እንደመታደል ይቆጥሩታል።

የሁለቱን ልዩነት ፋሪድ ዘካሪያ ሲደመድም “ዴሞክራሲ ለረዥም ጊዜ ልማት የራሱ የሆነ ተመራጭነት ሊኖረው ይችላል፤” ይላል። ሆኖም አውቶክራሲያዊ (ሕዝባዊ ተጠያቂነት የሌለባቸው) መንግሥታት “ትልልቅ የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶችን በማይቀናቀኑት  አቅም ዐቅደው፣ ማስፈፀም ይችልሉ፤” ይላል። ፋሪድ በመደምደሚያው ያልገለፀው አውቶክራሲያዊ መንግሥታት የሚሠሯቸው ፕሮጀክቶች ያለበቂ ‹ሴክተር ሪቪው› በመሆኑ ለዘለቄታው የሚያስከትሉት ችግር መኖር አለመኖሩን ቀድሞ መገመት የማይቻል መሆኑን ነው። እንዲያም ሆኖ የቻይናን ልማት “ተአምራዊ” የሚሉት ኢኮኖሚስቶች የሕንድን የዛን ያክል አያዳንቁትም። ሕንድ የቻይናን ያክል መገስገስ ያልቻለችው በከፊል የሕዝብ ብዛት ዕድገቷን (Population growth rate) እንደ ቻይና መቆጣጠር ስላልቻለች ነው። ዴሞክራሲያዊ ተጠያቂነት የሌለባት ቻይና የሕዝብ ብዛት ዕድገቷን ፍጥነት በጉልበት መቆጣጠር ችላለች። ይህንን ለማድረግ የነደፈችው ስትራቴጂ ብዙ ማኅበራዊ ቀውስ እና ሰብኣዊ እልቂት ያስከተለ ቢሆንም መንግሥቷ አውቶክራሲያዊ ተጠያቂነት አላስከተለም። ያለቀው አልቆ የቀረው በቁሳዊ ጥቅም አንፃር ይለፍለት የሚል አቋም ይመስላል። ሕንድ ዴሞክራሲያዊ በመሆኗ ይህንን ዓይነት ነገር ማድረግ አትችልም፤ “ቻይኖች በሁሉም ነገር ይበልጡናል፤ ከሕዝብ ብዛት ዕድገት ፍጥነት በቀር” የሚሉትን ዝነኛ አባባላቸውንም ያፈሩት ለዚያ ይመስላል።

Monday, January 18, 2016

ዴሞክራሲና የዘውግ ብሔርተኝነት



በናትናኤል ፈለቀ

በኢትዮጵያ አቆጣጠር 1983 . በኋላ የሀገሪቱን ስልጣን የያዘው ሕወኃት/ኢሕአዴግ መራሹ አገዛዝ ሀገሪቱን መልሶ ለማዋቀር ትከክል ብሎ ያሰበውን በዋነኝነት ቋንቋን ማዕከል ያደረገ የዘውግ ፌደራል ስርዓት ሲገነባ ቆይቷል፡፡ ይህም በቅርብ ጊዜ የሀገሪቱ ታሪክ ውስጥ የዘውግ ማንነት ተኮር ውይቶች ጎልተው አደባባይ እንዲወጡ ዕድል ፈጥሯል፡፡ የሀገሪቱን የፖለቲካ ልሂቃን ውይይት መድረክ የተቆጣጠረው የዘውግ ማንነት ተኮር (ብሔርተኝነት) አጀንዳ ልሂቃኑ በሚያሳዩት የፅንፈኝነት ባህሪ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተካረረ መጥቷል፡፡ በዚህም የተነሳ አሁን ስልጣን ላይ ያለው አገዛዝ አምባገነናዊ ቢሆንም በለውጥ ምክንያት ከስልጣን ቢወገድ በሚፈጠረው ክፍተት (Vacuum) ጊዜ ውስጥ የዘውግ ማንነት ተኮር የእርስ በርስ ግጭት ሊነሳ ይችላል ብሎ በመፍራት አምባገነናዊ ባህሪውን ይዞም ቢሆን ሕወኃት/ኢሕአዴግ መራሹ አገዛዝይቆይልንየሚል አስተያየት ያላቸው ሰዎች ጥቂት አይደሉም፡፡ ከዚህ ከፍ ሲል ደግሞ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት አሁን ሀገሪቱ ውስጥ አለ ብለው የሚያምኑትን የዘውግ ተኮር ግጭቶች ስጋት ለመቆጣጠርልፍስፍስ ስለሆነ አምባገነናዊ ስርዓት አሁን ላለንበት ተጨባጭ የማኅበራዊ-ፖለቲካ ሁኔታ ተመራጭ ነውየሚሉ ሃሳቦችም ይሰማሉ፡፡

በርግጥ ከላይ የተጠቀሱትን ሁለት አስተያየቶች የሚሰነዝሩ ሰዎች ሀገሪቱ እስከመቼ በአምባገነናዊ ስርዓት ውስጥ ብትቆይ እንደሚሻልና ምን ሲከሰት ወደ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ሽግግር ማድረግ ተገቢ እንደሆነ ግልፅ የሆነ የመፍትሄ ሀሳብ አብረው ሲሰነዝሩ አይሰማም፡፡ አንድ ነገር ግን ግልፅ ነው፡፡ ሀገሪቱን ለአምባገነናዊ ስርዓት ለተራዘመ ጊዜ መተው መዘዙ ብዙ ነው፡፡ በዚህ ጽሑፍ ዴሞክራሲያዊ ስርዓቶች የዘውግ ማንነት ተኮር የራስን ዕድል በራስ ለመወሰን የሚነሱ ጥያቄዎችን የሀገሪቱን ሉዓላዊ ግዛት አደጋ ውስጥ በማይከት ሁኔታ ማስተናገድ እንደሚችሉ በማሳየት ሀገሪቱ አሁን ባለችበት ተጨባጭ ሁኔታ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት እንደሚያስፈልጋት ይሞግታል፡፡ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ስለተፈጠረ ብቻ በዘውግ ብሔርተኝነት ምክንያት የሚፈጠር የግጭቶች ስጋት ተኖ ይጠፋል ማለት አይቻልም፡፡ ጽሑፉ ለማስረዳት የሚሞክረው ዴሞክራሲያዊ መንግስት (ስርዓት) በኢትዮጵያ ውስጥ ሲገነባ ችግሩ አሁን ካለበት ደረጃ የበለጠ አስጊ እንደማይሆን እና ከኢትዮጵያ በፊት ተመሳሳይ ስጋት የነበረባቸው ሀገራት ዴሞክራሲን ተጠቅመው ችግሩን እንዴት እንዳለፉት ነው፡፡ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ኢትዮጵያ ውስጥ እንዴትና በማን ይመጣል የሚሉት ጥያቄዎች በዘውግ ብሔርተኝነት ጥያቄ መልስ ማግኝት ውስጥ ግብዓቶች ቢሆኑም ከዚህ ጽሑፍ ወሰን (Scope) በላይ ናቸው፡፡

የዘውግ ማንነት ተኮር የፌደራል ስርዓት ለምን ኢትዮጵያን ይበታትናል?

የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኦዴግ) የሚባል ድርጅት በአዲስ መልክ አደራጅተው ወደ ኢትዮጵያ ፖለቲካ የተመለሱት ሌንጮ ለታ በጻፉት አንድ ጽሑፍ ኢትዮጵያ ውስጥ አሁን ስልጣን ላይ ያለው አገዛዝ ወደስልጣን ሲመጣ የነበረው የሀገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ (setting) የዘውግ ማንነት መሰረት ያደረገ የፌደራል ስርዓትን እንዲከተል ከታሪክ የተረከበው የውዴታ ግዴታ እንደነበር እና ብቸኛ ሀገሪቱን ከመበታተን ለማዳን የሚችል ስርዓት እንደነበር አስረድተዋል፡፡ እንደሌንጮ ትንተና ከሆነ የዘውግ ማንነት ጉዳይ ገዢ ሕዝብን የማደራጅያ (mobilizing) ሀሳብ አድርገው የፈጠሩት በዘውግ ማንነታችን ምክንያት ጭቆና ደርሶብናል ብለው የዘውግ ማንነት ተኮር ድርጅቶችን የመሠረቱ ቡድኖች ሳይሆኑ ከዛ በፊት ዘውግ ተኮር ጭቆናን የፈፀሙ ሀገሪቷን ይገዙ የነበሩ ቡድኖች ናቸው በማለትዘውግ ማንነት ተኮር ንቅናቄዎችን ቀድሞ ለተፈጠረ ችግር ምላሽ ብቻ እንደሆኑ ያስቀምጣሉ፡፡

ሌንጮ በጽሑፋቸው የፌደራል ስርዓቶች በተፈጥሯቸው የአገር ግዛት አንድነትን ለማስጠበቅ ጥንካሬ እንደሚያንሳቸው፣ የፌደራል ስርዓቱ የተዋቀረው ደግሞ የዘውግ ማንነትን (ቋንቋን) መሠረት አድርጎ ከሆነ የበለጠ ደካማ እንደሚያደርገው አትተዋል፡፡ የሌንጮን ሃሳብ የሚያጠናክር ተሞክሮ ለመጥቀስም የዓለም ግዙፏ ዲሞክራሲ ህንድ ከታላቋ ብሪታኒያ ቀኝ ግዛት ተላቃ ከፓኪስታን ጋር ፍቺ ከፈጸመች በኋላ ሃገሪቷን በጠቅላይ ሚነስትርነት ያስተዳድሩ የነበሩትጆዋሃርላል ኔህሩየገንጣይነት ስሜትን ያበረታታል እና ሀገሪቷን ወደ በለጠ መከፋፊል ያመራልበሚል ምክንያት የሕንድ ፌደራል ስርዓትን ቋንቋን መሠረት አድርጎ መልሶ ለማዋቀር ይነሱ የነበሩ ምክረ ሃሳቦችን ለመቀበል ፍላጎት እንዳልነበላራቸው አቱል ኮህሊ የተባሉ የሕንድ ማህበራዊ ሳይንስ ተመራማሪ “Can Democracies Accommod-ate Ethinic Nationalism? Rise and Decline of Self-determination Movements in India” በሚልርዕስ ባስነበቡት የጥናት ጽሑፍ ውስጥ ጠቅሰዋል፡፡ ኔህሩ የኋላ ኋላ ግን የታሚል ቋንቋ ተናጋተናጋሪዎች የራሳቸው ፌደራል ግዛት (Tamil Nadu) እንዲኖራቸው ያነሱትን ጥያቄ ተቀብለው የታሚል ቋንቋ ተናጋሪዎች ግዛት እንዲመሠረት አድርገዋል፡፡ የሰጉት የመበታተን አደጋ ግን አልተከሰተም፡፡