Friday, January 11, 2013

ዋኤል ጎኒም ኢትዮጵያዊ ቢሆን ኖሮ…?


-->ዋኤል ጎኔም የግብጽ ደኅንነት ሰዎች ደብድበው የገደሉትን ካሊድ ሰኢድ ለማሰብ ‹‹እኔም ካሌድ ሰኢድ ነኝ›› የተሰኘ የፌስቡክ ገጽ ከፍቶ ለግብጽ አብዮት ያበቃ ሰው ነው፡፡ የመጀመሪያውን የአደባባይ እንውጣ ጥሪ ያቀረበው ይኸው የፌስቡክ ገጽ ነው፡፡ ዋኤል አደባባይ የወጡበትን የመጀመሪያ ቀን (ጃንዋሪ 25) አንድ ዓመት ለማክበር (Revolution 2.0 የተባለ) መጽሐፍ አሳትሟል፡፡ የመጽሐፉ ገቢ በሙሉ በአብዮቱ ለተጎዱ ሰዎች መደጎሚያ እንደሚውልም ተነግሯል፡፡ አሁን እዚህ ልጽፍላችሁ ያሰብኩት ግን ዋኤል ገጹን እና የግል ማንነቱን አስመልክቶ ለሚቀርብለት ጥያቄ ይሰጥ የነበረውን መልስ ነው (መጽሐፉ ላይ እንዳሰፈረው)፤ ዋኤል ኢትዮጵያዊ ቢሆንና የከፈተው ገጽም ኢትዮጵያዊ ቢሆን ኖሮ… በሚል ምናባዊ ምሳሌ፡፡ ስለዚህ ጽሑፉ በዋኤል የተጻፈው በኢትዮጵያኛ ተተርጉሞ ነው ልትሉት ትችላላችሁ፡፡

ስምህ ማነው?

[1]ስሜ ሽብሬ ደሳለኝ ነው፤
[2]ስሜ ዩሱፍ አብደላ ነው፤
[3]ስሜ እስክንድር ነጋ ነው፤
[4]ስሜ ርዕዮት አለሙ ነው፤
[5]ስሜ አሕመዲን ጀበል ነው፤
[6]ስሜ አንዱአለም አራጌ ነው፤
[7]ስሜ በቀለ ገርባ ነው፤
[8]ስሜ ኦልባና ሌሊሳ ነው፤
[9]ስሜ መስፍን ነጋሽ ነው፤
[10]ስሜ አርጋው አሽኔ ነው፤

ስሜ…. ብዙ ነው፡፡

እኔ በጎዳና ላይ የተገደልኩ፣ ያለወንጀሌ የታሰርኩ፣ ያለሀጢያቴ የተገረፍኩ፣ መብቴን በፍርሐት የተነጠቅኩ፣ ከገዛ አገሬ የተሰደድኩ ኢትዮጵያዊ ነኝ፡፡

ዕድሜህ ስንት ነው?

ዕድሜዬ ይህን ያህል ነው አልልም፤ ነገር ግን ከተወለድኩ ጀምሮ ያለው ያው አምባገነን መሪ ነው፤… ሙስናውም ያው ነው፤…. ጭቆናው ያው ነው፤… እናም በአገሬ የገነነው የፖለቲካ ፓርቲ ‹‹ተስፋ የለም›› ይባላል፡፡

ከጠቀስካቸው ሰዎች ጋር ዝምድና አለህ?

እነዚህ ሰዎች የተኛውን ውስጤን ቀስቅሰውታል… ዕድሜ ለነርሱ አሁን ለውጥ ማምጣት እንደምችል ይሰማኛል፤… ታዲያ በራዕይ አልተዛመድንም ማለት ይቻላል?... አንድም ቀን አግኝቻቸው የማላውቃቸው እነዚህ ሰዎች ወንድሞቼ/እህቶቼ ናቸው፡፡

ይህንን የምታደርገው ለምንድን ነው?

ወገኖቼ ላይ የሚደርሰውን በደል ተመልክቼ ወደጥናት ክፍሌ ስገባ እምባዬን መግታት አልችልም፤… ፍርሐት የተጫናቸው ኢትዮጵያውያን ምን ያህል ውርደትን እንደሚታገሱ አየሁ… ከራሴ በመጀመር በፍርሐት የምሠራውን ስህተት ሁሉ ማረም ጀመርኩ፤ እናም ለዛ ነው ይህንን ገጽ የፈጠርኩት፡፡ ለተበደሉ ወገኖቼ ያለቀስኩት ለሞቱ ዘመዶቼ ካለቀስኩት በላይ ነው… በየዕለቱ ፎቷቸውን ስመለከት ድብታ ውስጥ እገባለሁ፤ ኢ-ፍትሐዊነትን እስከመጨረሻው ለመዋጋትም ለራሴ ቃል እገባለሁ፡፡

ማነው በገንዘብ የሚረዳህ?

ፈጣሪ ይመስገን፣ የገንዘብ ምንጮቼ ብዙ ናቸው፡፡ የመጀመሪያው ንቃተ ሕሊናዬ ነው… ይህ ምንጬ በቀን አራት ሰዓተ ብቻ እንድተኛ እና ጠዋትም ፊቴን ከመታጠቤ በፊት የፌስቡክ ገጼን እንድከፍት ያስገድደኛል፡፡

ሁለተኛው ምንጬ መማሬ ነው፡፡ በመማሬ ደስተኛ ነኝ፤ ዕውቀቴን አገሬን ለማገልገል አውለዋለሁ፡፡

ሦስተኛው ምንጬ የልጆች አባት መሆኔ ነው፡፡ ሁሌም የሚጨንቀኝ ልጆቼ አንድ ቀን ‹‹አባዬ፤ ዜጎች ሲጨቆኑ እያየህ አቅምህ የሚፈቅደውን ለምን አላደረግክም?›› ብለው ይጠይቁኛል ብዬ ነው፡፡

የመጨረሻው ምንጬ የሕዝብ ፍቅር ነው፡፡ አይቶኝ የማያውቅ፤ አይቼው የማላውቀው እና በስም የማንተዋወቀው ሕዝብ ፍቅር… በየዕለቱ የአመሰግናለሁ ማስታወሻ ይደርሰኛል…. የተለያዩ ዲዛይኖች፣ ሎጎዎች፣ ቪዲዮዎች ይልኩልኛል… ገጹ ብዙ ሰዎች ጋር እንዲደርስ ያስተዋውቁልኛል፡፡

ስለዚህ ምንድን ነው የምትፈልገው?

ይህንን ገጽ የፈጠርኩት ራሴን ከአደጋ ለመጠበቅ ብቻ አይደለም.. ነገር ግን አገራችን መልሳ የኛው የሕዝቦቿ እንድትሆን ከመፈለግ በላይ ሌላ ዓላማ የለኝም… አንድ ቀን እንዲህ ይሆናል ብዬ አልማለሁ፡- እርስ በእርስ ዳግም እንዋደዳለን፤ ሁላችንም ኢ-ፍትሐዊነትን እንቃወማለን፤ ከመሐከላችን ማንኛውም ሰው ክፉ ነገር ቢያይ ራሱ ይፈታዋል… እናም የመንግሥት ቅጥረኛ አንድን ዜጋ በጥፊ ከመምታቱ በፊት አንድ ሺሕ ጊዜ ያስብበታል፡፡

አትፈራም?

በጣም እፈራለሁ እንጂ፤… ፍርሐት እኮ የሰው ልጅ ተፈጥሮ ነው… ለተጨቆኑ ዜጎች የሚቆረቆር እንደእኔ እና እናንተ ያለ ሰው ግን ካለ ፍርሐቴ ይከስማል… ዕጣፈንታችንንም የምንወስነው እኛው ራሳችን እንሆናለን… እንዲህ እያልን፡- ‹‹ማንም ያለዕድሜው አይሞትም፣ ማንም ያለወንጀሉ አይታሰርም፣ ማንም አገሩን ለቅቆ አይሰደድም…›› አንድ ዘመዴ በ25 ዓመቱ ሞተ… ቁም ነገር ካልሠራሁበት የኔ ዕድሜ መርዘሙስ ምን ዋጋ አለው?

ብዙ ሰዎች ይህንን ለማመን ይቸገራሉ፤ እውነቱን ለመናገር ቃሉ የወጣው ከልቤ ነው… አገሬን ከልቤ እወዳታለሁ እናም በተሻለ ሁኔታ የምንኖርባት አገር እንድትሆን እፈልጋለሁ፡፡ መፈንቅለ መንግሥት ወይም አብዮት የማቀጣጠል ዓላማ የለኝም… እራሴን እንደፖለቲካዊ መሪም አልቆጥርም… ዋሊያዎችን እና ሉሲዎችን የሚደግፍ፣ ካፌ ደጃፍ ላይ ቁጭ ብሎ ተቆራጭ እየበላ፣ ማኪያቶ እየጠጣ ጋዜጣ የሚያነብ ተራ ዜጋ ነኝ፡፡… የሚከፋኝ ብሔራዊ ቡድናችን በሰው አገር ሲሸነፍ ነው፡፡ … ቁምነገሩ በኢትዮጵያዊነቴ መኩራት እፈልጋለሁ፡፡… ማንም ሰው የዜግነት ክብሩን ተገፍፎ እንዲጨቆን አልፈልግም፡፡ ይኸው ነው ምኞቴ፡፡
----
[1] - ሽብሬ ደሳለኝ፤ ምርጫ 97ን ተከትሎ በተነሳው ብጥብጥ የመንግሥት ጥይት ሰለባ የሆነች ወጣት ተማሪ፤ [1] - ዩሱፍ አብደላ፤ በተመሳሳይ ወቅት የተገደለ የኮተቤ መምህራን ኮሌጅ ተማሪ፤
[3] - እስክንድር ነጋ፤ በሽብርተኝነት ተከሶ የተፈረደበት ጋዜጠኛ፤
[4] - ርዕዮ ዓለሙ፤ መረጃ ለሽብርተኞች አቀብለሻል በሚል የተፈረደባት ጋዜጠኛ፤
[5] - አሕመዲን ጀበል፤ በሙስሊሞች የመጅሊስ ይቀየር ጉዳይ የታሰረ፣ ጋዜጠኛ እና ደራሲ፤
[6] - አንዱአለም አራጌ፤ ሽብር አሲረሃል በሚል የተፈረደበት የአንድነት ፓርቲ አባል፤
[7] - በቀለ ገርባ፤ ከኦነግ ጋር ግንኙነት አለህ በሚል የተፈረደበት የኦፌዴን ም/ሊቀመንበር፤
[8] - ኦልባና ሌሊሳ፤ ከኦነግ ጋር ግንኙነት አለህ በሚል 8 ዓመት የተፈረደበት የኦብኮ አባል፤
[9] - መስፍን ነጋሽ፤ በሽብርተኝነት አዋጅ/ክስ ምክንያት ከተሰደዱ የቀድሞዋ አዲስ ነገር ጋዜጠኞች አንዱ፤
[10] - አርጋው አሽኔ፤ የመረጃ ምንጩን እንዲሰጥ በመንግሥት ኃይሎች በግዴታ በመጠየቁ የተሰደደ ጋዜጠኛ፤

No comments:

Post a Comment