Showing posts with label ማኅበራዊ. Show all posts
Showing posts with label ማኅበራዊ. Show all posts

Tuesday, September 10, 2013

የ2005 የጊዜ መሥመር


በማሕሌት ፋንታሁን

ክቡራት የዞን 9 ነዋሪዎች ዓመቱ ከማለቁ በፊት እንዴት እንዳለፈ ለማስታወስ እንዲረዳን በማሰብ በ2005 የተከናወኑ አበይት ተግባራትን በዓመቱ የጊዜ መሥመር ላይ እንደሚከተለው ለማሳየት ሞክረናል፡፡ መልካም አዲስ ዓመት ይሁንላችሁ፡፡

መስከረም
  • §  መስከረም 11/2005 የተከበሩ ኃ/ማርያም ደሳለኝ የኢትዮጵያ ጠ/ሚ ሆነው፣ የተከበሩ ደመቀ መኮንን ደግሞ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው ቃለ መሐላ ፈፀሙ፣
  • §  መስከረም 17 ቀን 2005 ድምፃዊ ቴድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) በሒልተን ሆቴል አንድ ሺሕ ያህል ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ጋብቻውን ፈፀመ፣

ጥቅምት
  • §  ጋዜጠኛ ርዕዮት ዓለሙ አሜሪካን ሃገር ከሚገኘው የዓለም አቀፉ የሴቶች ሚዲያ ፋውንዴሽን የ2012 ‹ፅናት በጋዜጠኝነት ሥራ› የተሰኘ ሽልማት አገኘች፣
  • §  የ2005 የእስልምና ምክር ቤት /መጅሊስ/ ምርጫ በየቀበሌው ተካሄደ፣  

Wednesday, June 26, 2013

#ስንፍና፤ ባሕላችን ነው እንዴ?



ሁሉም ሰው የለውጥ ምኞት አለው፣ ሁሉም ሰው የለውጥ ምኞቱን እውን ማድረግ የሚችልባቸውን አማራጮች ከሞላ ጎደል ያውቃቸዋል፣ ሁሉም ሰው ግን ለውጡን እውን የማድረግ አቅም የለውም፡፡ ጥቂቶች ናቸው ይህንን ማድረግ የሚችሉት፡፡ ዋነኛው ምክንያታቸው ደግሞ ስንፍና ነው፡፡ የስንፍና ተቃራኒው ጉብዝና ነው እንበልና - ጉብዝናቸውን ከስንፍናቸው ማስበለጥ የቻሉ ሰዎች ብቻ ለውጦችን ማስመዝገብ ይችላሉ ብለን መጣጥፉን በድምዳሜ እንጀምረው፡፡

ከላይ ‹ጉብዝናን ከስንፍና ስለማስበለጥ› ያወራኋትን ነገር ‹‹ለመግቢያ መግባቢያነት›› እንድደግማት ፍቀዱልኝ፡፡ ጉዳዩ አወዛጋቢ ቢሆንም ሰዎች ሁሉ በጥቅሉ /በመሠረታዊ ነገራቸው/ አንድ ናቸው ብዬ አምናለሁ፡፡ ጥልቀቱ እና ስፋቱ ይለያይ እንጂ፣ በትምህርትና በልምምድ ብሎም በኑሮ አጋጣሚ ይዳብር/ይሳሳ እንጂ ሁሉም በሰብኣዊነታቸው የሚጋሯቸው ባሕርያቶች አሉ፡፡ ከነዚህ ውስጥ ስንፍና እና ጉብዝናን ነው መርጬ ላወራበት የፈለግኩት - በተለይ ስንፍናን፡፡ ሆኖም በማወራበት ጊዜ ሁሉ ፍፁም ስንፍናን (ወይም ፍፁም ጉብዝናን) እያሰብኩ እንዳላወራሁ እንድትገነዘቡልኝ እፈልጋለሁ፤ የሌለውን ከየት አመጣዋለሁ?!

ስንፍና - የኢትዮጵያውያን ባሕል?

ይህንን ጽሑፍ ለመጻፍ ስነሳ ገና ‹‹ኢትዮጵያውያን የስንፍና ባሕል አለብን›› የሚል ስጋት እየተጫጫነኝ መሆኑን አልደብቃችሁም፡፡ ጥያቄው፤ ይህ ሰብኣዊ ባሕርይ ባሕል ሊሆን ይችላል ወይ? ባሕል ሊሆን የሚችል ከሆነስ ኢትዮጵያውያን ስንፍናን ባሕል አድርገውታል ወይ? ኢትዮጵያውያን ባሕል አድርገውታል/አላደረጉትም ለማለትስ ሁሉንም በአንድ መጨፍለቅ እንችላለን ወይ? (ለምሳሌ አማራ፣ ኦሮሞ፣ ትግሬ፣ ጉራጌው… ሁሉ በየራሱ የሥራ ባሕል ውስጥ የሚኖር ስለሆነ አንድ ዓይነት የስንፍና/ጉብዝና ባሕል ይኖረዋል ወይ? የክርስትያን ሙስሊሙስ የሥራ ባሕል አይለያይም ወይ?...)

ጥያቄዎቹን ባወጣሁ እና ባወረድኳቸው ቁጥር የመመለስ አቅሜ ውሱን እንደሆነ ተረድቻለሁ፤ ሆኖም ጥያቄውን ማንሳት በራሱ ወደመልሱ የሚያመራ ነውና መጻፌን አላቋረጥኩም፡፡

Wednesday, February 13, 2013

#Valentine’s Day, #Ethiopia: ኢትዮጵያውያን ፍቅር ያውቃሉ?




‹‹ፍቅር ማወቅ እና አለማወቅ›› የሚባል ነገር አለ? ‹‹ፍቅር ማወቅ›› የሚባል ነገር ካለስ - ኢትዮጵያውያን ፍቅር ያውቃሉ? - የዛሬ የፍቅር (የቫለንታይን) ቀን ጽሑፋችን በዚህ ዙሪያ ያጠነጥናል፡፡

መቃጠር (Dating)

“Dating” የሚለው የእንግሊዝኛ ቃል በአገርኛ አማርኛ እኩያ አንድ ቃል ፍቺ ይገኝለት ከተባለ - መቃጠር - የሚለው ተቀራራቢ ይሆናል፡፡ ሆኖም ‹‹አቃጣሪ›› የሚለው የቆየ ቃል የሚሰጠው አሉታዊ ትርጉም ነው፤ ሁለት ሰዎች መሐል ነገር የሚያመላልስ ማለት ሲሆን በፍቅርም ቢሆን አቃጣሪ የሚለው (በተለይም ከጥንታዊ አመጣጡ አንጻር) ቤተሰቦቻቸው ለመገናኘት ዕድሉን የነፈጓቸውን ተፋቃሪዎች በመሐል እየተመላለሰ የፍቅር መልዕክታቸውን የሚያደርስ የሚል ትርጉም ይኖረዋል፡፡ ትርጉሙን ቦርቀቅ ስናደርገው ደግሞ ሁለት ሰዎች እንዲፋቀሩ ለማድረግ በመሐላቸው የድለላ ሥራ የሚሠራ - የሚያቃጥር (dating agent) - እስከሚል ትርጉም ሊደርስ ይችላል፡፡

የፈረንጅኛውን ትርጉም ስንወስደው ደግሞ የተለየ እና አዎንታዊ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ዊኪፔዲያ ለምሳሌ ለDating  የሚሰጠው ትርጉም እንዲህ ይተረጎማል ‹‹Dating is a form of courtship consisting of social activities done by two people with the aim of each assessing the other's suitability as a partner in an intimate relationship or as a spouse. While the term has several meanings, it usually refers to the act of meeting and engaging in some mutually agreed upon social activity in public, together, as a couple.…››

ኢትዮጵያ ውስጥ አንዳንድ ዘመነኛ ከተሜዎች ካልሆኑ በስተቀር፣ መግጠም አለመግጠማችንን እናጥና ብለው ተከታታይ ቀጠሮዎች አመቻችተው፣ አንደኛ፣ ሁለተኛ፣ ሦስተኛ ቀጠሮ በ‹መቃጠር› የሚጠናኑበት እና የሚወያዩበት መንገድ አለ ለማለት ይከብዳል፡፡ አጋጣሚዎች ፈቅደው ከንፈር ለከንፈር ሲገናኙ በሚጀመር የከንፈር ወዳጅነት ድንገት ወደ‹‹ግንኙነት›› ወይም ዕውቅና ያልተሰጠው ፍቅር (affair) ይገባሉ፡፡

ይህንን የመቃጠር ልምድ ማዳበር የግንኙነት ወቅት ለሚኖሩ ክፍተቶችን ለመቀነስ ይረዳል የሚሉ ልምዱ መዳበሩን የሚያበረታቱ ሲኖሩ በሌላ በኩል ደሞ ከባሕላችን ውጪ የሆነና በእኛ ማኅበረሰባዊ ባህሪ ሊለመድምና ውጤታማ ሊሆን አይችልም በሚል ያጣጥሉታል፡፡

ፍቅረኝነት፣ ፍቅር አገላለገጽ እና “Romance”

ልክ እንደ‹dating› ሁሉ ‹romance› ለሚለው ቃልም ሁነኛ የአገርኛ አማርኛ ትርጉም ማግኘት አይቻልም፡፡ ‹romance› ማለት ፍቅርን መግለጫ መንገድ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ጥንዶች ፍቅረኞቻቸውን ለማስደሰት ቢፈልጉም እንኳን ፍቅረኛቸውን ለማስደሰት አቅደው የሚያደርጉበት ልምድ/ባሕል የለም ብሎ መከራከር ይቻላል፡፡ እንዲያውም ብዙዎች የፍቅር አጋራቸውን ‹‹ፍቅረኛዬ›› ነች ብሎ ማለት እያሳፈራቸው፤ በእንግሊዝኛ ‹‹ቦይፍሬንዴ/ገርልፍሬንዴ›› ማለት እየቀናቸው ነው፡፡ ያውም ይህ በከተማ ውስጥ ነው፡፡ በገጠሩ ክፍል በምስጢር ከሚጠበቅ የከንፈር ወዳጅነት ተሻግረው ለትዳር ከበቁ በኋላ ፍቅር የሚገለጸው በቁፍጥንና ነው፡፡ በሁሉም የኢትዮጵያውያን ብሔሮች እና ባሕሎች ብዙም በማይራራቅ ሁኔታ ባሎች ሚስቶቻቸውን በመቆጣጠር እና በመቆጣት የበላይነታቸውን ከማሳየት በላይ ሌላ ፍቅር የሚገልጹበት መንገድ የለም ማለት ይቻላል፡፡ ይህ ማለት ግን ፍቅር የላቸውም ተብሎ ሊተረጎም አይገባም፤ ፍቅር አላቸው ነገር ግን ፍቅራቸውን የመግለጫ መንገድ/ባሕል/ልምድ ግን የላቸውም፡፡ በተደጋጋሚ ሲገለጽ እንደሚስተዋለው ዱላ የፍቅርና ቅናት መገለጫ እየተባለ ቢነሳ አሁን አሁን ግን ጉዳዩ ወንጀል በመሆኑም ጭምር በጊዜ ሂደት ቢያንስ እንደፍቅር መገለጫነት መቆጠሩ ቀርቶአል፡፡

ማቆላመጥ

አንዱ የኢትዮጵያውያን ፍቅርን የመግለጽ ችግርን የሚያንፀባርቀው ፍቅረኞችን ለማቆላመጥ የምንጠቀምበት ቃላት ማጠር ነው፡፡ ፈረንጆቹ ‹‹honey, sweetie, baby…›› እያሉ የፍቅረኛቸው ስም እስኪረሳቸው ሲያቆለማምጡ የኛዎቹ ግን የፍቅረኛቸውን ስም እንኳ በቁልምጫ መጥራት የሚከብዳቸው ጊዜ ይስተዋላል፡፡ ስንቶች ፍቅረኞቻቸውን ‹‹ማሬ፣ ጣፋጯ፣ ፍቅሬ…›› ብለው በአደባባይ ይጠራሉ? ከጓደኞቻቸው ጋርስ በግልጽ ያስተዋውቃሉ? ብዙ ጊዜ ከወጣቶቹ አንደበት የማትጠፋው ‹‹የኔ ቆንጆ›› የምትል ቃል ራሷ፣ የወል ስም እየሆነች አጠቃቀሟ የምር ይሁን የልምድ ለመለየት ያስቸግራል፡፡

Friday, February 8, 2013

የታክሲዎቻችን ነገር




ከሌላው የኑሯችን ሳንካ ባልተናነሰ የአዲስ አበባ ከተማ ታክሲዎች አሠራር ተጠቃሚዎችን ማማረር እና ማበሳጨት ሥራቸው ከሆነ ሰነባብቷል፡፡ ከረዳትና ከሹፌር ጋር አተካሮ ሳይገጥም የሚሄድ ተሳፋሪ ያለበት ታክሲ ውስጥ መገኘት መታደል ነው፡፡ ባለታክሲ ስል ሾፌርንም ረዳትንም በጅምላ ወይም በተናጠል ማለቴ ነው፡፡ የፀቡ መንስኤ ሁል ጊዜ ባለታክሲ ነው  ብዬ አላስብም ተሳፋሪም  ሊሆን ይችላል፤ ነገር ግን የዛሬ ርዕሴ  ባለታክሲዎችን የሚመለከት ነው፡፡

ባለቤት፣ ሹፌርና ረዳት

የታክሲ ሥራ ዋና ተዋናይ ሲሆኑ፤ ሁሉም አንድ የሚያረጋቸው የቀን ገቢያቸው ከፍ የሚልበትን ማንኛውንም መንገድ መጠቀማቸውና ለተሳፋሪም ርህራሄ የሌላቸው መሆኑ ነው፡፡ የታክሲ ባለቤት ሹፌር በሚሆንበት ጊዜ ረዳቱ ለከፍተኛ ቁጥጥር አደጋ የተጋለጠ ነው፡፡ ሹፌሩ ተቀጣሪ በሚሆንበት ጊዜ ግን በአብዛኛው ሹፌርና ረዳት በመመካከርና በመረዳዳት ላይ የተመሰረተ ግንኙነት ይኖራቸዋል፡፡ ረዳቱ የታክሲው ባለቤት የሚሆንበት ጊዜም አለ፡፡ ወይም የታክሲው ባለቤት ሹፌር ይቀጥርና የራሱ የቅርብ ሰው የሆነ ረዳት ይመድባል፡፡ (የባለቤቱ ዘመድ የሆኑትን ረዳቶች ሹፌሮች ‹‹ዕንባ›› ነው የሚሏቸው፤ ዕንባ ጠባቂ እንደማለት፡፡) ይህም ለሒሳብ ቁጥጥር ያመቸዋል፡፡ በሁለቱም መንገዶች ረዳቱ ሹፌሩን ሲመራ እና ሲያዝ ይስተዋላል፡፡ አብዛኛዎቹ ረዳቶች ሹፌር የሆነ ወቅት ያክል ከረዱ በኋላ የሹፌርነትን የሥራ መደብ ይይዛሉ፡፡

Wednesday, January 16, 2013

ፎቶግራፍ የሌለው የጉዞ ማስታወሻ




የገና ማግስት በቅጡ ሳልዘጋጅ ከቤቴ በመውጣቴ ካሜራ እንደሚያስፈልገኝ የተረዳሁት 200 መቶ ኪሎ ሜትር ከተጓዝኩ በኋላ ነበር - አዋሽን ስንሻገር፡፡ ስለዚህ በዚህ የጉዞ ማስታወሻ ላይ ምስል ከሳች ትረካ እንጂ ምስል የለም፡፡ እየተጓዝኩ ያለሁት ወደአፋር ነው፤ ሰመራ፡፡ ከጠዋቱ ሁለት ሰዓት ገደማ ከአዲስ አበባ ተነስተን፣ የመኪና ጉዞ ምቾትን ትርጉም በሚያሰጠው ላንድክሩዘር ጉዞ ጀመርን፡፡ አዳማ ላይ ቁርጥ እና ጥብስ ለመብላት ሲቆሙ እኔም በሳቅ እና በፈገግታ አጀብኳቸው፡፡

ከአዲስ አበባ በወጣሁ ቁጥር የሚገጥመኝ ችግር ምርጫዬ የሆነ ምግብ ነው፡፡ ሁሉም ሰው ጥብስ ወይም ቁርጥ መብላት እንደሚያምረው ቁርጤን ስላወቅኩ… እኔም ሽሮ፣ ፓስታ፣ አትክልት የመሳሰሉትን ለብቻዬ እፈልጋለሁ፡፡ አብረውኝ ከሚጓዙት አንዱ ‹‹ቬጅቴርያን ነህ ወይ?›› አለኝ፤ ‹‹አይደለሁም›› አልኩት እንጂ ምንም የምለይበት የለኝም፡፡ እርግጥ ነው ዱለት፣ ክትፎ፣ አሩስቶ ምናምን ከተገኘ አልምርም፡፡ የዛን ዕለት ጠዋት ግን ለነርሱ ከቀረበው ጥብስ ላይ ጥቂት ዛላዎች እያነሳሁ ነካከስኩ፡፡

አዋሽ አርባ የተባለችው ከተማ ከመግባታችን በፊት የአዋሽ ወንዝን ማቋረጥ ነበረብን፡፡ የአዋሽ ወንዝ ሞልቶ ድልድዩ አግድርም የተዘረጋ ታንኳ መስሏል፡፡ ስንመለስ ታንኳው (ድልድዩ) በከፊል ሰምጧል፡፡ ስንሄድ ከአዋሽ አርባ ከተማ ወደግራ ታጥፈን ወደሰመራ ከማምራታችን በፊት የድንገቴ ዕቅድ ለውጥ አደረግን፤ ሐረርን አይቻት የማላውቀው እኔ በመሆኔ ለምን በጨረፍታ አናሳየውም ተባባሉ፤ እርግጥ ነው እኔን ሰበብ አርገውኝ ነው እንጂ እነርሱም መሄድ የፈለጉበት ምክንያት አላቸው፡፡

ሐረር - የታጠረች ከተማ?

በካፊያ ታጅበን ወደ12 ሰዓት ገደማ ሐረር ገባን፡፡ የ1000 ዓመቷን እመቤት ሐረር አንድ ቀን ለጉብኝት እንደምሄድባት አውቅ ነበር፤ ግን እንዲህ በድንገቴ ይሆናል ብዬ ስላላሰብኩ ድጋሚ መምጣት እንዳለብኝ እያሰላሰልኩ በወፍ በረር ጎበኘኋት፡፡ መቼም ጉብኝት ያውም በማታ፣ ያውም  (በእግር መንሸራሸሩ ባይቀና እንኳ) የሕዝብ ትራንስፖርት ሳይጠቀሙ የጉብኝትን ጣዕም ያሳጣል - ስለዚህ አየኋት ለማለት በማያስችል ሁኔታ ቃኘኋት፡፡ ምናልባት በዚያ ፍጥነት ካየሁት የማስታውሰው የአዲስ አበባውን አጤ ምኒልክ ሐውልት መንትያ የሚመስለውን የራስ መኮንን ሐውልት እና ጀጎልን ነው፡፡ ያቺ ጨረፍታ ግን ሐረር - የታጠረች ከተማ ሲባል የነበረኝን ግንዛቤ ለመቀየር በቂ ነበረች፡፡ በዘመኗ ከተማ የነበረችው አሁን ከአንድ የሀብታም ግቢ የምትሰፋ አይደለችም፡፡

Wednesday, December 26, 2012

አክሱምን ወላይታ አገኘሁት!!! (የአርባ ምንጭ ጉዞ ማስታወሻዬ)


በናትናኤል ፈለቀ

ኅዳር 12 ቀን 2005 ዓ.ም በሥራ ጉዳይ ወደ ጋሞ ጎፋ ዞን ዋና ከተማ አርባ ምንጭ መሄድ ነበረብኝ፡፡ ለሁለት ቀን ተኩል የሚበቃኝን  ሸክፌ ከመሥሪያ ቤቴ በተመደበልኝ መኪና ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ላይ ለሚነሳው በረራ ለመድረስ ወደቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ጉዞ ጀመርኩ፡፡ በቅዱስ ኡራኤል ቤተ ክርስቲያን በኩል ወደ ቦሌ የሚወስደውን መንገድ ይዘን ስንጓዝ ከመንገዱ ግራ እና ቀኝ ላይ የተደረደሩት የፌደራል ፖሊስ አባላት አቀባበል ወይንም ሽኝት የሚደረግለት ባለሥልጣን/እንግዳ እንዳለ ስለጠቆመኝ መንገዱ ሳይዘጋ ቦሌ ለመድረስ ጥረት እንዲያደርግ ለሹፌሩ ጠቆምኩት፡፡ ብዙም ሳንጓዝ አትላስ ሆቴል የትራፊክ መብራት ላይ ስንደርስ በስፍራው የነበሩት የትራፊክ ፖሊሶች ወደ ቺቺንያ ወይንም ወደ ቦሌ ሩዋንዳ የሚወስደውን መንገድ እንድንጠቀም አስገደዱን፡፡ ወዲያውኑ ሰዓቴን ተመለከትኩ፤ ለሰባት ሰዓት ሩብ ጉዳይ ይላል፤ ብዙም አልተረበሽኩም፡፡ በስተቀኝ በኩል ታጥፈን በውስጥ ለውስጥ አቋራጭ መንገድ ጥቂት ከሄድን በኋላ መልሶ ዋናውን መንገድ ስላገናኘን መኪናውን አቁመን እንግዳውን እስኪያልፍ መጠባበቅ ጀመርን፡፡

በዚያው ሰሞን ወደ ሩዋንዳ ዋና ከተማ ኪጋሊ ሄዶ የነበረ አንድ የሥራ ባልደረባችን በአምስት ቀን ቆይታው ሁለት ጊዜ በመንገድ ያለፋቸው ፕሬዝዳንት ፖል ካጋሜ በከተማው መንገድ ላይ ሲጓዙ እሳቸው ከሚጓዙበት አቅጣጫ በተቃራኒው የሚወስደው የመንገዱ ጎን ክፍት እንደሚሆን የነገረኝን ለሹፌሩ እያጫወትኩት ሳይረን እያሰማ የሚከንፈውን ሞተረኛ ተከትለው ካልተሳሳትኩ አምስት መኪኖች በፍጥነት ወደ ቦሌ የሚወስደውን መንገድ ይዘው ሲያልፉ አየን፡፡ ካለፉት መኪናዎች ሦስቱ ባለግርማ ሞገሶቹ ጥቋቁር ሼቭሮሌቶች ነበሩ፡፡ ያለፉት ባለሥልጣን ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ መሆን አለባቸው (በእርግጥም ነበሩ፤ ለሥራ ጉብኝት ወደ ጎረቤት ሀገር ኬንያ እያቀኑ)፡፡ እንደ ሥራ ባልደረባችን ከሆነ ፕሬዝዳንት ካጋሜን የሚያጅቡት አንድ ሞተረኛ ፖሊስ ከፊት እና አንድ መኪና ከኋላ ሆነው ነው፡፡ ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ይህን ሁሉ ጥበቃ የሚደረግላቸው ከፕሬዝዳንት ካጋሜ ይልቅ ለደኅንነታቸው የሚሰጉ መሪ ስለሆኑ ነው? ወይስ ኢትዮጵያዊያን ከሩዋንዳዊያን ይልቅ አስፈሪ ሕዝብ ስለሆንን? ይህንን እቆቅልሽ እያሰላሰልኩ መንገዱ ተከፍቶ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ የአገር ውስጥ በረራ የሚደረግበት ጣቢያ ቁጥር 1 ደረስኩኝ፡፡

የኢትዮጵያ አየር መንገድን ቀልቤ አይወደውም፡፡ ምናልባት የመጀመርያ በረራ ባደረኩበት ወቅት በድርጅቱ እንዝላልነት ምክንያት ያጋጠመኝ በሕይወቴ ከዛ በፊትም ሆነ በኋላ አጋጥሞኝ የማያውቅ እንግልት ተፅዕኖ አድርጎብኝ ይሆናል፡፡ ጥሎብኝ ደግሞ በሕይወቴ ውስጥ ትልቅ ቦታ የምሰጣቸው የቤተሰብ አባላት እና የቅርብ ጓደኞቼ ለአየር መንገዱ ተቀጥረው ሠርተዋል/እየሠሩ ነው፡፡ አየር መንገዱ ላይ ያለኝ አቋም ከነዚህ ወዳጆቼ ጋር አልፎ አልፎ ቅራኔ ውስጥ ይከተኛል፡፡

ተርሚናሉ ውስጥ ገብቼ በመፈተሻ መሳሪያው ካለፍኩ በኋል የያዝኩት ሻንጣ ማሽኑን አልፎ እስኪመጣ ቀበቶዬን እያጠለኩ ስጠባበቅ ‹‹ወደ አርባ ምንጭ ስለሆነ እንጂ ሌላ ቦታ ቢሆን አይፈቀድም›› የሚለው ከማሽኑ ጀርባ ተቀምጣ ሻንጣዎች ውስጥ ያለውን እቃ በምስል የምትከታተለው የጥበቃ ባለሙያ ንግግር ቀና አደረገኝ፡፡ ‹‹አቤት›› አልኳት በተገረመ ድምፅ፡፡ ‹‹አይ አንተን አይደለም›› አለችን በአገጯ ከአጠገቤ የቆመውን ሰው እየጠቆመችኝ፡፡ ሰውየው ስሙ ያልተጠራው እሱ ሻንጣ ውስጥ ያለው እቃ ምን እንደሆነ ገብቶታል፡፡ ተረጋጋሁ፡፡ ወዲያው ደግሞ ሌላ ሐሳብ ገባኝ፤ ሌላ በረራ ላይ የማይፈቀድ ነገር ግን አርባምንጭ ስለሆነ የሚፈቀድ እቃ ምንድን ነው?

የአየር መንገዱ ሠራተኞች የ‹ቼክ-ኢን› ሰዓታቸው የደረሱትን በረራ ተሳፋሪዎችን በሁለት መስኮቶች እያስተናገዱ ነበር፡፡ ከሚያስተናግዱት የአየር መንገዱ ሠራተኞች መካከል አንደኛዋ ፀጉሯን መሸፈኛ (በእስልምና እምነት ሥርዓት) ‹ሂጃብ› አድርጋለች፡፡ ‹ሂጃቡ› ከለበሰችው የአየር መንገዱ ሰራተኞች የደንብ ልብስ ጋር አብሮ እንዲሄድ መደቡ ነጭ ሆኖ አረንጓዴ መስመሮች ያሉበት ሲሆን በቀጭኑ ‹የኢትዮጵያ/Ethiopian› የሚል ጽሑፍ አርፎበታል፡፡ ብዙ ድርጅቶች እንኳን ለሠራተኞቻቸው ይቅርና ለሚያገለግሏቸው የእስልምና እምነት ተከታዮች ምቾት እምብዛም እንደማይጨነቁ ስለማውቅ በአየር መንገዱ እርምጃ ተደሰትኩኝ፡፡ ወድያውኑ ስልኬን አውጥቼ ብዙ ግዜ በአየር መንገዱ ላይ የማማርርባት ጓደኛዬን ቁጥር መታሁ፡፡ ስልኩ ሲነሳም በአየር መንገዱ ውስጥ እንዳለሁ ጠቅሼ የደወልኩት እንደበፊቱ ለማማረር ሳይሆን ባየሁት ነገር ደስ ስላለኝ እንደሆነ፤ ጥፋት ሲሆን እንደማማርረው ሁሉ በቀጣሪዋ ሥራ ስደሰትም ማመስገን እንዳለብኝ ጉራ ቢጤ ቸበቸብኩ፡፡

ከፊቴ ከነበሩት ሰዎች ቁጥር አንፃር ሰልፍ ላይ ረጅም ሰዓት ያሳለፍኩ ስለመሰለኝ ‹ቼክ-ኢን› አገልግሎት የሚሰጠት ሠራተኞችን መከታተል ጀመርኩ፡፡ ጥርጣሬዬ ልክ ነበር፡፡ እኔ ስደርስ ቀድመውኝ ከፊቴ ከነበሩት መንገደኞች መካከል ከሦስት በላይ ተሳፋሪዎች ‹ቼክ-ኢን› ጨርሰው ወደ እንግዳ መቆያ ስፍራ አልተመሩም፡፡ ችግሩን ለማጣራት ሞክሬ ጥፋቱ የደንበኞች አገልግሎት የሚሰጡት ሠራተኞች እንዳልሆነ ተረዳሁኝ፡፡ ችግሩ ሠራተኞቹን የሚረዳቸው ‹ሲስተም› እክል ስለገጠመው ነበር፡፡ የመንገድ መዘጋቱን ተከትሎ አብዛኛው ተሳፋሪ ዘግየት ብሎ በመድረሱ ምክንያት ሰልፉ በርከት ብሏል፡፡ የደንበኞች አገልግሎት ሰራተኞቹ ደንበኞቻቸውን በቶሎ ማስተናገድ ስላልቻሉ ኮምፒውተር እየቀያየሩ ይሞክራሉ፣ ስልኮቻቸውን እያነሱ ችግሩን ለበላይ ሰዎች ለማስረዳት ይሞክራሉ፣ ፊታቸው ላይ መጨነቃቸው ያስታውቃል፡፡ እዛው ሰልፍ ላይ ሆኜ ለስምንት ሰዓት አስራ አምስት ደቂቃዎች ብቻ ቀሩት፡፡ አርባ ምንጭ ስራዬን የምጀምረው በማግስቱ ስለነበር ማርፈድ አላስጨነቀኝም፡፡ ነገር ግን ከአየር መንገዱ የተሰጣቸውን ሰዓት ተንተርሰው የሥራ ወይንም ሌላ ቀጠሮ የያዙ ሰዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ ገመትኩኝ፡፡ ‹‹ቀድሞ ማመስገን ኋላ ለሐሜት ይቸግራል›› የሚለውን የሀገሬን አባባል አስታወስኩኝ፡፡

ስምንት ሰዓት ሊሆን ጥቂት ደቂቃዎች ሲቀሩት አንድ በአካባቢው ከዛ ቀደም ያላየሁት በእጁ መገናኛ ሬድዮ (ዎኪ-ቶኪ) የያዘ የአየር መንገዱ ሠራተኛ (የቅርብ አለቃ ይመስለኛል) ወደ ጅማ እና አርባ ምንጭ የምንሄድ ተሳፋሪዎችን ጠይቆ ከሰልፉ ውስጥ ለይቶ ‹ቼክ-ኢን› በ‹ማንዋል› እንዲሰራልን አዝዞ ወደ አውሮፕላኑ በቀጥታ እንድንሳፈር አደረገ፡፡

Monday, December 24, 2012

የደሞዝ Vs. የጠብሽ* ሰሞን




አነጋገራችንን፣ አካሄዳችንን፣ አበላላችንን፣ አስተያየታችንን ባጠቃላይ የምናደርገውን ማንኛውም እንቅስቃሴ ላይ ቀጥጠኛ አስተዋፅኦ ካላቸው ነገሮች አንዱና ዋነኛው በኪሳችን ያለው ገንዘብ ዋነኛው ነው፡፡ ገንዘብ ከምናገኝባቸው አንዱ መንገድ ደግሞ ተቀጥሮ መሥራትና ወር ሲያልቅ የሠራንበትን ክፍያ/ደሞዝ ማግኘት ይገኝበታል፡፡ አብዛኛው በከተማ አካባቢ የምንኖር በዚህ መስመር ውስጥ እንገኛለን፡፡

ደሞዝ ተቀብሎ ቀጣዩን የደሞዝ ቀን እንደ ምፅአት ቀን በጉጉት የማይጠብቅ ካለ ይህ ሰው ከደሞዙ ውጪ ሌላ ተጨማሪ ገቢ አለው ወይም አንድ ቀልድ ላይ እንደሰማሁት በአስማት ነው የሚኖረው ማለት ነው፡፡ ደሞዛችን እዛው እንዳለ ወይም በተወሰነ ጭማሪ… ብቻ ኑሮ ግን በብዙ እጥፍ ጨምሮ መኖር መቻላችን እውነትም አስማተኛ ያስብላል፡፡ እንደየደረጃው ይለያይ ይሆናል እንጂ አብዛኛው ደሞዝተኛ ደሞዝ ከተቀበለ በኋላ ካሉት የተወሰኑ ቀናት ውጪ ለመጪው የደሞዝ ቀን ስንት ቀን እንደቀረው በመቁጠር፤ ቀሪውን ጊዜ በብድር እንዴት እንደሚያሳልፍ በማውጠንጠን፤ የሰቀቀን ኑሮ መኖሩን የተለማመድነው ይመስላል፡፡

የደሞዝ ሰሞንና የጠብሽ ሰሞን እንደየሰው ይለያያል፡፡ በአብዛኛው ደሞዝ ከተቀበሉ ከ10-15ኛው ቀን በኋላ ሰሞነ ጠብሽ ይገባል፡፡ ደሞዝ የተቀበሉ እለትም ደሞዟ ብድር ብቻ ከፍላ የዕለቱለት ጠብሽ የሚጀምርበት አጋጣሚም አለ፡፡ የበዓል ወቅቶች እና ጳጉሜ ወር “የጠብሽ” ወቅትን ከሚፋጥኑ/ከሚያረዝሙ ምክንያቶች ውስጥ ዋነኞቹ ናቸው፡፡ የጳጉሜ ወር ግን ለምን ደሞዝ እንደሌላት ሁሌም ይገርመኛል፡፡ በዛ ላይ የአዲስ ዓመት ወጪ ተጨምሮበት አስቡት፡፡

Tuesday, November 13, 2012

ስለ ወንድና ሴት የመጻፍ ጣጣ



ይህ አጭር ጽሑፍ በዞን ዘጠኝ ጦማር ላይ "ወጣት ሴት የመሆን ጣጣ" በሚል ጽሑፍና ለዚህ ጽሑፍ ምላሽ በተሰጠ "ወጣት ወንድ የመሆን ጣጣ" በሚል ጽሑፍ አነሳሽነት የቀረበ ነው።

ስለስርዓተ ጾታ የሚደረጉ ውይይቶችና ክርክሮች በተለያዩ የልማድ ማነቆዎች የታሰሩ ናቸው። ከመጀመሪያው ዙር የፌሚኒስቶች ንቅናቄ በኋላ የተፋፋመው የስርዓተ ጾታ ጉዳይ የአብርሆት ዘመን ፍልስፍናን ኋላ ቀር ሊያስብለን በሚያስችል ደረጃ ግሩም ሐሳቦች የቀረቡበት ነው። ከግሪክ ፈላስፋዎች ጀምሮ አብዛኞቹ የቅድመ ፌሚኒዝም ፈላስፋዎች ስርዓተ ጾታን በተመለከተ የጻፉት ሐሳብ ከሰው ልጅ ልማድ መላቀቅ ያልቻለ ነው። ይህን አስተሳሰብ በአግባቡ ለመቃኘትና ክርክሮቻችንን አዲስ መልክ ለመስጠት የፌሚኒስቶችን ሐሳብ መዳሰስና የቅርብ ጊዜ ፀረ-ፌሚኒዝም አስተሳሰቦችን መፈተሽ ያስፈልጋል። በበኩሌ በዞን ዘጠኝ አባላት የተነሱት ነጥቦች የአገራችን የከተማ ወጣቶች ከስርዓተ-ጾታ አንፃር ያሉበትን ነባራዊ ሁኔታ በመግለጽ በኩል በቂ ናቸው ብዬ ባምንም ሁኔታውን በመተርጎምና በመተንተን በኩል ግን ውስንነቶቻቸውን ታዝቤያለሁ። ስለዚህም ጽሑፎቹ ትኩረት የነፈጓቸውን ወይም የዘነጓቸውን ጉዳዮች በአጭሩ በማቅረብ የክርክሩ ሂደት ቅርፅ እንዲይዝ ለማገዝ ጥቂት ነጥቦችን ማንሳት ፈለግሁ። በጉዳዩ ላይ በቀጣይ ሰፋ ያለ ሐሳብ ለማቅረብ ስላሰብኩ ለጊዜው የማነሳቸው ነጥቦች ውሱንና በቀረቡት ጽሑፎች ዙሪያ ያጠነጠኑ ናቸው። 

ጾታዊ ማንነት (Essentialism)

ማንኛውንም ነገር በሁለት ተቃራኒ ጎራ የመክፈል ልማድ (Dichotomy) በስርዓተ ፆታ ጉዳይም የተጠናወተን አባዜ ነው። በራሳችን አዕምሮ ውስጥ የፈጠርናቸው የማንነት ተቃራኒ ምድቦች የራሳቸው ሕልውና እንዳላቸው የመውሰድ አስተሳሰብ ለምድቦቹ ሥነ-ሕይወታዊ ዳራ እንድንሰጣቸው አድርጎናል። ስለዚህም በክርክሮቻችን ውስጥ ሴትና ወንድ እንደ ቋሚ ማንነቶች (Essences) የሚቆጠሩበትና ማንኛውንም ግለሰብ ከሁለት ተቃራኒ የማንነት ቅርጫቶች ውስጥ በአንዱ ለመጨመር የምናደርገው ጥረት ሊፈተሽ ይገባዋል። ይህ አስተሳሰብ በግለሰቦች መካከል ያለውን ልዩነት የዘነጋና የግለሰብ ባህርይ የሚቀዳው ከሁለቱ ተቃራኒ "የተፈጥሮ" ቡድኖች መሃል ካንዱ እንደሆነ ታሳቢ የሚያደርግ ነው። የፌሚኒስቶች ንቅናቄ በጥልቀት የፈተሸው አንዱ እውነታ ይህ ነው። ይህም የፌሚኒስቶች ሙግት "ማንነት" የምንለውን ጉዳይ በእጅጉ የፈተነና "የተቃራኒ ጾታ" የፍቅር ግንኙነትን ታሪካዊ መሠረት ያናወጠ ነው። ይህን ጉዳይ በአግባቡ ለማጤን እንዲቀየሩ የፈለግናቸውን የወንድና የሴት ባህርያት ማሰብ በቂ ነው። እነዚህ ባህርያት ከተቀየሩ ወንድና ሴት የሚባሉ ማንነቶች ከየት ይመጣሉ? ይህን ጥያቄ በስነ-ህይወታዊ ትንታኔ ለመመለስ መሞከር ስርዓተ-ፆታችን ካለበት እንዳይንቀሳቀስ መፍቀድ ነው። ዋናው ነጥብ ግን በሁለቱም ጽሑፎች ላይ ይህ ጉዳይ በልማድ ዕይታ ሙሉ ለሙሉ እንደተሸፈነ መታዘቤ ነው። ይህን ስል አሮጌው የጾታ ስርዓት በቋንቋችን ላይ የፈጠረውን ውሱንነት ዘንግቼ አይደለም።

Sunday, November 11, 2012

የቀለም ልዩነት(መድልኦ) በአገራችን ኢትዮጵያ



ይህን ጽሑፍ ከላይ ርዕሱን አይታችሁ ምን ለማለት ፈልጎ ነው? አሊያም ሁሌም ጠንካራ ጎናችን የሆኑትን መስማትና ማንበብ ስለለመድን ይህ ሐሳብ ግርታ የሆነ ስሜት ሊፈጥርባችሁ ይችላል። ሐቅ ቢመርም መዋጥን መልመድ አለብና የተሰማኝን ጻፍኩት የሚሰማችሁን በጨዋ ደንብ አክሉበት። (ፀያፍ ካልተሳደቡ አስተያየት ያልሰጡ የሚመስላቸውን ታታሪ ተሳዳቢዎችን ነው ማሳሰቢያው የሚመለከተው!)

በኢትዮጵያችን ውስጥ ጥቁሩ ማኅበረሰብ (ከጠይም በላይ የጠቆሩትን ማለቴ ነው) በቆዳው ቀለሙ ብቻ መድልዖ ይደርስበታል የማግለልና በቀለም ብቻ የሚፈፀሙት በደሎችና መንስኤዋችን ለመዳሰስ እሞክራለሁ።

፩፡-የሥራ ዕድል

ሥራ ለማግኘት ከትምህርትና  ከችሎታ መመዘኛዎች በተጨማሪ የምትጠየቀው ወይ የሚፈለግብህ/ ነገር አለ፡፡ የት አገር እንዳትሉኝ በእኛዋ ኢትዮጵያችን ውስጥ መልከ መልካም መሆን አሊያም ጠይም የቆዳ ቀለም ሚዛኑን ትደፉ ዘንድ ከፍተኛውን ድርሻ ይወስዳሉ። የስራ አመራር፣ አስተዳደራዊና ፖለቲካዊ ሹመቶች ወዘተ... ግርማ ሞገስና ውበት ከብቃት ይልቅ ሚዛን ይደፋሉ። የቤት ሠራተኝነት የምትቀጠር አንዲት ሴት ጠቆር ካለች የመጥፎ ገድ ምልክት ተደርጋ፣ ልጆቻችን ሊፈሩ ይችላሉ ተብሎ፣ ያቺ ምስኪን የሥራ ዋስትና ታጣለች። በተፈጠሩበት አገር ላይ መገለል ጉዳቱ ምን ያህል መሆኑን ከቀመሱት በላይ ማን ሊሰማው ይችላል?

(
አካላዊ ውበትና ቅርፅ የሚሹ የሥራ መስኮች የሉም እያልኩኝ ግን አይደለም!)

፪፡-የፍቅርና የትዳር አጣማጅ ማግኘት ጫናዎች

አንዲት የአገራችን ልጅ ከናይጀሪያዊ ጓደኛዋ ጋር በፍቅር ከነፈች ሲበዛ በጣም ትወደዋለች እሱም በጣም  ይሳሳላታል፣ የተማረ ስልጡን ባለሙያ ነው። በፍቅር የወደቀችለት ልጅን አግብቶ ቤተሰብ መመሥረት ይፈልጋል፤ እሷም ትፈልጋለች ግን ያደገችበት ማኅበረሰባዊና ቤተሰባዊ ጫና በትምህርት ያገኘችውን ዕውቀት በልጦ በጭንቀት ማዕበል ውስጥ በሰመመን እየተብከነከነች መኖርን አስመረጣት። ለምን እየወደደችው፣ እያፈቀረችው የትዳር አጣማጁ መሆንን አትሻም? መልሱ ቀላል ነው የቀለም ልዩነት ብቻ ነው። የቆዳው መጥቆር፣ የከንፈሩ መተለቅ አካላዊ ገፅታውን እሷ ብትወድለትም ቤተሰቦችዋ ግን እንደማይቀበሉት ታውቃለች፡፡ ያንንም በቀጥታም በተዘዋዋሪም ነግረዋታል የመካነ አዕምሮ (ዩንቨርሲቲ) መምህሩ ወንድሟ በፌስቡክ ላይ ምስሉን አይቶ ዘራችንን ልታበላሺ ላልጠፋ ወንድ ባርያ ትይዣለሽ? በማለት አሸማቋታል (ይህ ሰው ለተማሪዎቹ ምን ይሆን የሚያስተምራቸው? የዘር፣ የቀለም ልዩነት ወንጀል በሆነበት ዘመን ያልተለወጠ ሰው በተለይ መምህር መሆኑ ጥፋቱን ያሰፋዋል!)

Wednesday, November 7, 2012

የትምህርት ጥራት ነገር (ክፍል አንድ)



በመልማት ላይ ያሉ ሀገራት ካላቸው የመዋለ-ነዋይ ውስንነት አንፃር መንግስቶቻቸው የትኛው መስክ እና የትኛው ስራ ቀድሞ መከናወን እንዳለበት ለመወሰን አስቸጋሪ የሆነ አጣብቂኝ ያጋጥማቸዋል፡፡ ድህነትን ለማሸነፍ በሚደረገው ጥረት ውስጥ ከፍተኛ እና ፈጣን ውጤት የሚያስመዘገቡት መስኮች እና ተግባራት ወይንም ደግሞ ከሌሎች መስኮችና ተግባራት ይልቅ አንገብጋቢ ለሆኑት ችግሮች መፍትሄ መስጠት  የሚችሉት የመዋለ-ነዋይ ፍሰት ከሚደረግባቸው ተግባራት የመጀመርያውን ረድፍ ያገኛሉ፡፡ ብዙዎቹ ተግባራት ግን አይጠቅሙም ወይንም አያስፈልጉም ከሚል መነሻ ሳይሆን ድሀ ሀገራት በሚለዩባቸው የአቅም ውስንነት ብቻ ሳይተገበሩ ይቀራሉ፡፡


ሀገራችን ኢትዮጵያ ደሀ ናት፡፡ ከፍተኛ የሆነ የመዋለ-ነዋይ ውስንነት፣ ቢሰራ ህዝቡን ይጠቅማል ብሎ መንግስት የሚያስባቸውን ተግባራትን እውን እንዳያደርግ ማፈናፈኛ ያሳጡታል፡፡ (በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንዲሉ ከዚህም በላይ በብልሹ አሰራር እና በሙስና ምክንያት ሀገሪቱ እጅግ አድርጋ የምትፈልገው ነዋይ ያለ አግባብ ይባክናል፡፡) የኢትዮጵያ መንግስትን የአቅም እጦት አጣብቂኝ ውስጥ ከሚከተው ተግባራት መካከል የትምህርት ጥራት ከተደራሽነት ጋር እኩል ማራመድ አለመቻሉ ይጠቀሳል፡፡ በርግጥ ለትምህርት ጥራት መጓደል ሌሎች አያሌ ምክንያቶችን መደርደር ይቻላል፡፡ ነገር ግን የአቅም ውስንነት ትልቅ ሚና እንዳለው የማይካድ ነው፡፡


ዜጎች ለሀገራቸው ዕድገት ጉልበታቸውን፣ ገንዘባቸውን እና ዕውቀታቸውን በመጠቀም የየራሳቸውን አስተዋፅዎ ያደርጋሉ፡፡ የላቀ ዕውቀት ባለቤት የሆኑ ዜጎች የበዙባት ሀገር ከድህነት ለመላቀቅ መንገዱ እጅግ የቀለለ ይሆንላታል፡፡ ዜጎቿ ዕውቀታቸውን በመጠቀም ከድህነት የምትወጣበትን ውጤታማ መንገድ ይቀይሳሉ፣ ሀገር ተረካቢውን ትውልድ በሚገባ ይቀርፃሉ፡፡ የተማሩ ዜጎች የተመሰረተ ቤተሰብን መጥኖ መውለድ ስለሚሰጠው ጥቅም ለማገንዘብ ብዙ ወጪ አያስፈልገውም፡፡ በቤተሰቡ ውስጥ የሚወለዱ ህፃናትም እድሜያቸው ለትምህርት እንደደረሰ ትምህርት ቤት የመግባታቸው እድል ያልተማሩ ዜጎች በመሰረቱት ቤተሰብ ውስጥ ከተወለዱት ህፃናት አንፃር ሲገመገም የጎላ ልዩነት አለው፡፡


በአሁኑ ወቅት እድሜያቸው ከ15 ዓመት በላይ ከሆኑት ኢትዮጵያዊያን መካከል 30 በመቶ የሆኑት መሰረታዊ የሆነውን ዕውቀት ማንበብና መፃፍ ይችላሉ፡፡ ቀሪዎቹ ግን ጣቶቻቸውን ፊደላትን ለመከተብ እና አይኖቻቸውን ከወረቀት ላይ ተክለው ፊደል ቆጥረው መረጃ ለማግኘት አይቻላቸውም፡፡ ላቅ ያለ ዕውቀት ኖሯቸው ሀገራችን ከድህነት አረንቋ ለመውጣት በምታደርገው ሩጫ ንቁ ተሳታፊ ሆነው የጎላ አስተዋፅዎ ማድረግ የሚችሉት ዜጎች ደግሞ እጅግ በጣም ጥቂቶቹ ናቸው፡፡