Thursday, January 31, 2013

የኢትዮጵያዊነት መንፈስና የደቡብ አፍሪካው የአፍሪካ ዋንጫ


በፍቅር ለይኩን

There are two things that can bring this planet closer together: love and football.
--Iran coach Afshin Ghotbi

ይህ ለዚህ ጽሑፌ መግቢያ ይሆነኝ ዘንድ የመረጥኩትን ኃይለ ቃል በ1998ቱ የዓለም ዋንጫ ባለንጣዎቹ የዛሬዋ ልዕለ ኃያል አሜሪካና በአስር ሺህ ዘመናትን በሚያስከነዳ ግዙፍ ስልጣኔዋና ታሪኳ ምትኩራራው ኢራን በተፋጠጡበትና የእግር ኳስ መድረክ የኢራኑ አሰልጣኝ ስለዚህ አስደናቂ አጋጣሚ በአድናቆት የተናገረው ነው፡፡ የአሜሪካው የእግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንትም the mother of all games በሚል አጭር ቃል ነበር ሁለቱን አገራት ግጥሚያ የገለፁት፡፡ እስቲ ስፖርት በፖለቲካው መድረክ ካለው አዎንታዊ ሚና በመነሳት ስለ ሰሞኑ የአፍሪካ ዋንጫ ጥቂት ነገሮችን ልበል፡፡

አገራችን ኢትዮጵያ ከሦስት አሠርት ዓመታት በኋላ ተሳታፊ በሆነችበት በዘንድሮው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የፈጠረብን ደስታ፣ ሐሴትና ሞቅታ ገና ለአፍሪካ ዋንጫ ማለፋችንን የምታበስረውን የመጨረሻዋን ፊሽካ ከሰማንባት ቅጽበት ጀምሮ የተፈጠረ ውብና ልዩ ስሜት ነው፡፡

ይህ ብሔራዊ ስሜታችን ከኢትዮጵያዊነት ምሉዕ ኩራት፣ ስሜትና ትኩሳቱ ጋር አብሮን ዘልቆ በእግር ኳሱ መድረክ በዓለም ኅብረተሰብ ዘንድ አብዝተን ከምንታወቅበት ‹‹የራብና የጦርነት ምድር›› ከሚለው ገጽታችን ባሻገር ኢትዮጵያ ‹‹የኳስ ጥበብን የተካኑ የውብ ሕዝቦች አገር ናት!›› የሚለውን ሌላውን ውብና ተወዳጅ ገጽታችንን ለዓለም ሕዝብ አሳይቶ አልፏል፡፡

ይህን ብሔራዊ ቡድናችን ለአፍሪካ ዋንጫ ማለፉን ተከትሎ በደቡብ አፍሪካ ባሉ ኢትዮጵያውያን መካከል የነበረውን የኢትዮጵያዊነት ጥልቅ ፍቅርና የአንድነት ውብ ስሜት የታዘበ አንድ ደቡብ አፍሪካዊ ወዳጄ በኢሜይል ባደረሰኝ መልእክቱ እንዲህ ሲል ነበር አድናቆቱንና ትዝብቱን ያካፈለኝ፡-

Tuesday, January 22, 2013

1966ቱ የኢትዮጵያ አብዮት እና የነጻ ማኅበራት ፋይዳ




በ2004 የኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ‹‹መጅሊስ ይቀየር›› ጥያቄ መቀስቀሱን ተከትሎ ኦሮሚያ ክልል ውስጥ ከሚገኙ ዩንቨርስቲዎች በአንዱ ውስጥ በጉዳዩ ዙሪያ ለመወያየት ስብሰባ ተጠራ፡፡ ስብሰባው ላይ የዩንቨርስቲው የተማሪዎች ኅብረት ፕሬዚደንት የነበረው የእስልምና እምነት ተከታይ እጁን አውጥቶ ‹‹ትላንትና ምንም ነገር እንዳልናገር ከዩንቨርስቲው አስተዳደር ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶኝ ነበር፥ ሆኖም…›› ብሎ ሐሳቡን ተናገረ፤ ያ የዩንቨርስቲ የተማሪዎች ኅ      ብረት ፕሬዚደንት በማግስቱ ከኃላፊነቱ ተነሳ፡፡

ይህ በኢሕአዴግ ዘመን ያለውን ግለሰባዊም ሆነ ቡድናዊ መብት ደረጃ ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ምሳሌ ሲሆን በዚሁ ተንደርድረን፣ በ1966ቱ የኢትዮጵያ አብዮት ጉልህ ሚና የተጫወቱትን ተመሳሳይ አካላት እንመለከታለን፤ ለመሆኑ እነዚህ ሕዝባዊ አካላት እነማን ነበሩ?

የ1966ቱ የኢትዮጵያ አብዮት የኋላ ኋላ ገጠሬው ቢቀላቀለውም፣ በአብዛኛው የተመራው በከተማ ነዋሪዎች ነው ማለት ይቻላል፡፡ አንዳርጋቸው ጥሩነህ Ethiopian Revolution 1974-1987፡ A transformation from an aristocratic to a totalitarian autocracy (1993) በተሰኘው ጥናታቸው ላይ በአብዮቱ ዋና ተዋናይ የነበሩትን አካላት ከነ[ተቀራራቢ] ቁጥራቸው ዘርዝረዋቸዋል፡፡

“የኢትዮጵያ ንግድ ማኅበራት ኮንፌዴሬሽን 80,000 አባላት፤ የኢትዮጵያ መምህራን ማኅበር (አባላቱ የመንግሥት ሠራተኞች ነበሩ፤) ብዛታቸውም 18,000 ነበር፡፡ ከመንግሥት ሠራተኞቹ በተጨማሪ 10,000 የምድር ጦር እና 30,000 የፖሊስ አባላትን ጨምሮ 55,000 የሠራዊት አባላትን የሠራተኛ ማኅበሩ ያካትታል፡፡

በወቅቱ የተመዘገቡ ተማሪዎች ቁጥር 70,000 ነበር፤ ከነርሱ ውስጥ 6,000ዎቹ የዩንቨርስቲ ተማሪዎች ናቸው፤ (በተጨማሪም በውጭ ሃገራት የዩንቨርስቲ ጥናት ላይ የነበሩ ሌሎች 2,000 ተማሪዎች ነበሩ)፡፡

“ስለዚህ ከጠቅላላው 3 ሚሊዮን የከተማና ከተማ ቀመስ ቦታዎች ነዋሪ ሕዝብ ውስጥ ፖለቲካዊ ንቁ ተሳትፎ እያደረጉ የነበሩት የመንግሥት ሠራተኞች፣ ወታደሮች እና ተማሪዎች ከ300,000 የማይበልጡ የከተማ ነዋሪዎች ነበሩ፡፡”

በየማኅበራቱ የታቀፉት እና ፖለቲካዊ ንቁ የነበሩት ሕዝቦች ቁጥር ከጠቅላላው የከተማ ሕዝብ አንጻር እንኳን ሲታይ ከ10 በመቶ የማይበልጡ እና በወቅቱ ከነበረው ጠቅላላ የሕዝብ ብዛት አንጻር ከ1 በመቶ የማይበልጡ ቢሆንም አብዮቱን ማስነሳት ችለዋል፡፡ አብዮቱ ከተማ እና ኮርፖሬታዊ ጉዳዮች ላይ ብቻ ሳይወሰን አገር አቀፍ እንዲሆን በማድረግና ስር ሰድዶ የነበረውን ንጉሣዊውን ስርዓት በማንገጫገጭ ለማስወገድም ችሏል፡፡ ይህ ሊሆን የቻለው በተለያዩ ማኅበራት ጥንካሬ ነው እንጂ በተሳታፊዎቹ ቁጥር ብዛት አይደለም ብዬ አምናለሁ፡፡ በዝርዝር እንመልከተው፡-

Monday, January 21, 2013

አንድ እሁድን በማረሚያ ቤት…



ትላንት እሁድ (ጥር 12/2005) የርዕዮት ዓለሙ ወዳጆች ልደቷን አስመልክተው እንድንጠይቃት በፌስቡክ ሁሉንም ሰው ጋብዘው ነበር፡፡ እኛም ሰብሰብ ብለን ለመሄድ ተቀጣጠርን፤ ሆኖም የእሷ ልደት ላይ ከመገኘታችን በፊት ውብሸት ታዬን ለመጠየቅ ወስነን ከጠዋቱ አንድ ሰዓት ላይ ሳሪስ ተሰባሰብን፡፡ ውብሸት የታሰረው ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ነው፡፡ ቂሊንጦ የሚገኘው አቃቂ ድልድይ አካባቢ ከሚገኘው የጥሩነሽ ሆስፒታል፣ በፒስታ አጭር የታክሲ/ባጃጅ/ጋሪ መንገድ ከተጓዙ በኋላ ነው፡፡

ቂሊንጦ ከቃሊቲ ማረሚያ ቀለል ያለ መንፈስ አለው፡፡ እርግጥ ነው ቀለል የማለቱ ነገር የሚጀምረው መግቢያው ላይ ካለው የማረሚያ ቤቱ ፖሊሶች አቀባበል ነው፡፡ ከዚህ በፊት ቃሊቲ ስንመላለስ ባላየነው መልኩ የታራሚዎቹን ጠያቂዎች በአገልግሎቶቻቸው ላይ አወያይተዋል፡፡ አወያዩ ከዚህ በፊት ይደረግ የነበረው ውይይት ለአጭር ጊዜ ተቋርጦ የነበረ ቢሆንም አሁን ግን በወር አንዴም ቢሆን እንደሚቀጥል በመናገር ጀምሮ ጎብኚዎች እየገጠሟቸው ያሉ ችግሮች ካሉ ጠየቀ፡፡ ሆኖም አንዳንድ ሰዎች እጃቸውን እያወጡ ከማመስገናቸው በቀር የጎላ ይሄ ነው የሚባል ችግር እንዳልገጠማቸው ተናገሩ፤ ይህንንም ከገባን በኋላ ውብሸት ሁሉም ነገር ጥሩ እንደሆነ አረጋግጦልናል፡፡ ይህ የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አሠራር ቃሊቲ ማረሚያ ቤት ርዕዮትስ ስንጠይቅ ከሚገጥመን የፖሊሶች ማመነጫጨቅ፣ ላለማስገባት ሰበብ መፈለግ እና ከመሳሰሉት የሚያበሳጩ እና ተስፋ የሚያቆርጡ ተግባራት ጋር ሲተያይ ፍፁም ተቃራኒ ነው፡፡ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ልምድን ቢወስድ መልካም ነው፡፡

ከውብሸት ጋር የነበረን ቆይታ በሰዓት የተገደበ አልነበረም፤ (ይህ ቃሊቲ ቅዳሜ እና እሁድ ርዕዮትን ለመጠየቅ ስንገባ ከተሰጠን 30 ደቂቃ አንጻር ሲታይ ዓለም ነበር፡፡) ውብሸት በመልካም ጥንካሬ ውስጥ ነው፡፡ ንግግሩ ትህትና የተሞላበት ነበር፡፡ ከገባ ጀምሮ እስካሁን ስላለው ብዙ ጉዳዮች አጫወተን፡፡ ማረሚያ ቤቱ ውስጥ ካሉት ሰዎች ውስጥ በግምት 30 በመቶ የሚሆኑት በፖለቲካ ሰበብ እንደታሰሩ እና ከነዚህም ውስጥ አብዛኛዎቹ ከኦነግጋ ንክኪ አላችሁ በሚል እንደተፈረደባቸው አጫውቶናል፡፡ አንዳንዶቹ እስረኞች በጣም አፍላ ወጣቶች ከመሆናቸው የተነሳ ቢያጠፉ እንኳን መክሮ ከመልቀቅ በላይ እርምጃ እንደማይገባቸው አጫወተን፡፡ ውብሸት በአሁኑ ጊዜ ጠዋት ጠዋት በማረሚያ ቤት ውስጥ በሚገኘው የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ውስጥ የሚያስተምር ሲሆን በተጨማሪም የአረብኛ ቋንቋ ስልጠናም ለታራሚዎቹ በመስጠት ጊዜውን በአግባቡ እንደሚያሳልፍም ነግሮናል፡፡

Wednesday, January 16, 2013

ፎቶግራፍ የሌለው የጉዞ ማስታወሻ




የገና ማግስት በቅጡ ሳልዘጋጅ ከቤቴ በመውጣቴ ካሜራ እንደሚያስፈልገኝ የተረዳሁት 200 መቶ ኪሎ ሜትር ከተጓዝኩ በኋላ ነበር - አዋሽን ስንሻገር፡፡ ስለዚህ በዚህ የጉዞ ማስታወሻ ላይ ምስል ከሳች ትረካ እንጂ ምስል የለም፡፡ እየተጓዝኩ ያለሁት ወደአፋር ነው፤ ሰመራ፡፡ ከጠዋቱ ሁለት ሰዓት ገደማ ከአዲስ አበባ ተነስተን፣ የመኪና ጉዞ ምቾትን ትርጉም በሚያሰጠው ላንድክሩዘር ጉዞ ጀመርን፡፡ አዳማ ላይ ቁርጥ እና ጥብስ ለመብላት ሲቆሙ እኔም በሳቅ እና በፈገግታ አጀብኳቸው፡፡

ከአዲስ አበባ በወጣሁ ቁጥር የሚገጥመኝ ችግር ምርጫዬ የሆነ ምግብ ነው፡፡ ሁሉም ሰው ጥብስ ወይም ቁርጥ መብላት እንደሚያምረው ቁርጤን ስላወቅኩ… እኔም ሽሮ፣ ፓስታ፣ አትክልት የመሳሰሉትን ለብቻዬ እፈልጋለሁ፡፡ አብረውኝ ከሚጓዙት አንዱ ‹‹ቬጅቴርያን ነህ ወይ?›› አለኝ፤ ‹‹አይደለሁም›› አልኩት እንጂ ምንም የምለይበት የለኝም፡፡ እርግጥ ነው ዱለት፣ ክትፎ፣ አሩስቶ ምናምን ከተገኘ አልምርም፡፡ የዛን ዕለት ጠዋት ግን ለነርሱ ከቀረበው ጥብስ ላይ ጥቂት ዛላዎች እያነሳሁ ነካከስኩ፡፡

አዋሽ አርባ የተባለችው ከተማ ከመግባታችን በፊት የአዋሽ ወንዝን ማቋረጥ ነበረብን፡፡ የአዋሽ ወንዝ ሞልቶ ድልድዩ አግድርም የተዘረጋ ታንኳ መስሏል፡፡ ስንመለስ ታንኳው (ድልድዩ) በከፊል ሰምጧል፡፡ ስንሄድ ከአዋሽ አርባ ከተማ ወደግራ ታጥፈን ወደሰመራ ከማምራታችን በፊት የድንገቴ ዕቅድ ለውጥ አደረግን፤ ሐረርን አይቻት የማላውቀው እኔ በመሆኔ ለምን በጨረፍታ አናሳየውም ተባባሉ፤ እርግጥ ነው እኔን ሰበብ አርገውኝ ነው እንጂ እነርሱም መሄድ የፈለጉበት ምክንያት አላቸው፡፡

ሐረር - የታጠረች ከተማ?

በካፊያ ታጅበን ወደ12 ሰዓት ገደማ ሐረር ገባን፡፡ የ1000 ዓመቷን እመቤት ሐረር አንድ ቀን ለጉብኝት እንደምሄድባት አውቅ ነበር፤ ግን እንዲህ በድንገቴ ይሆናል ብዬ ስላላሰብኩ ድጋሚ መምጣት እንዳለብኝ እያሰላሰልኩ በወፍ በረር ጎበኘኋት፡፡ መቼም ጉብኝት ያውም በማታ፣ ያውም  (በእግር መንሸራሸሩ ባይቀና እንኳ) የሕዝብ ትራንስፖርት ሳይጠቀሙ የጉብኝትን ጣዕም ያሳጣል - ስለዚህ አየኋት ለማለት በማያስችል ሁኔታ ቃኘኋት፡፡ ምናልባት በዚያ ፍጥነት ካየሁት የማስታውሰው የአዲስ አበባውን አጤ ምኒልክ ሐውልት መንትያ የሚመስለውን የራስ መኮንን ሐውልት እና ጀጎልን ነው፡፡ ያቺ ጨረፍታ ግን ሐረር - የታጠረች ከተማ ሲባል የነበረኝን ግንዛቤ ለመቀየር በቂ ነበረች፡፡ በዘመኗ ከተማ የነበረችው አሁን ከአንድ የሀብታም ግቢ የምትሰፋ አይደለችም፡፡

Sunday, January 13, 2013

ትምህርት… ወዴት ዘመም ዘመም?


ዐፄው ስለትምህርት

በሀገራችን ዘመናዊ ትምርት የተጀመረው በዐፄ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት ቢሆንም ከመስፋፋቱ ጋር ስማቸው በታሪክ መዛግብት በጉልህ የሚነሳው ዐፄ ኃይለሥላሴ ናቸው፡፡ ከሸዋ ፖለቲካ የስልጣን ሽኩቻ በአሸናፊነት ብቅ ያሉት መልከ ቀናው ዐፄ ኃይለሥላሴ ኋላ ላይ ራሳቸው ከሸለሙዋቸው ተማሪዎች ጋር ስልጣናቸውን ያሳጣቸው ግጭት ውስጥ ቢገቡም እስከዛው ድረስ በየጠቅላይ ግዛቱ ያሉትን ልበ ብርሀን ተማሪዎች ሰብስቦ ከማስተማር ቤተመንግሥታቸውን እስከመልቀቅ ደርሰዋል፡፡ ከዚህም ባለፈ ለራሳቸውን የትምህርት ሚኒስትርነት ኃላፊነት በመስጠት ለትምህርት ሟች መሆናቸውን አስመስክረዋል፡፡ ጥሩ ውጤት አስመዝጋቢ ተማሪዎችን ከሀገር ዳርቻ ሰብስቦ ማስተማር፤ በአካል ተገኝቶ መሸለምና በቀለም የዘለቁትን ደግሞ ባሕር ማዶ ሄደው እንዲማሩ ማድረጋቸው ለትምህርት ጥራት የሰጡትን ትኩረት ያሳያል፡፡

በልላ በኩል ዐፄው ለመምህርነት የሚታጩ ተማሪዎች ላቅ ያለ ውጤት እንዲኖራቸው ስለሚጠበቅ "በዕደ ማርያም ትምህርት ቤት"  በተለየ ጥንቃቄ ይሰለጥኑ እንደነበር ጉዳዩን የሚያውቁ የሞያ ባልደረቦቼ አጫውተውኛል፡፡ የእነዚህ የዚያ የትምህርት ስርዓት ውጤት የሆኑት ሰዎች ልዩነት በቀን ተቀን የሥራ እንቅስቃሴያቸው ይታያል፡፡ በዕውቀታቸው ምጡቅ፤ በሥነ ምግባራቸው የተከበሩ እና ለሥራቸው ጠንቃቃ ባለሞያዎች ናቸው፡፡ አሁንስ አስተማሪ ለመሆን የሚሰለጥኑ ዕጩዎች ምን ይመስላሉ? በሌላ ጽሑፍ የምመለስበት ይሆናል፡፡

የፋኖዎቹ ጥንቃቄ

“ያረጀውን ዐፄያዊ ጨቋኝ አገዛዝ በአፍጢሙ ደፍቼ አዲሲቷን ኢትዮጵያ በሶሻሊዝም መዓዛ ይዤላችሁ መጣሁ” ያለው ደርግ  አገር አንድ የተማረ ሰው ለማፍራት ስንት አመት እንደሚፈጅባት ብዙም ስላልገባቸው "አንድ ጥርስ ቢኖራት በዘነዘና ተነቀሰች" እንዲሉ የነበሩትን በጣም ጥቂት ምሁራን 72 ሰዓት የጥፋት አዋጅ እንደ ገብስ እያጨደ ሬሳውን ቢከምርም የትምህርት ስርዓቱ ውስጥ ጣልቃ ልግባ ግን አላለም፡፡ የኢሠፓ ካድሬዎችም ቢሆኑ የካቲት 66 ወይም ሩሲያ ሄደው ማርክሲዝምና ሌኒንዝም እንዲጠጡና የገባቸውንም ያልገባቸውንም እንዲያነበንቡ አደረገ እንጂ የሁለተኛ ደረጃ ትምርታቸውን በቅጥ ዳር ያላደረሱ የመንደር አቢዮት ጠባቂዎችን ባለተደራራቢ ዲግሪ አላደረገም፡፡ እንግዲህደርግ መንግሥት ጥፋቶቹ የትዬለሌ ቢሆኑም በአፈሙዝ ወኔ የትምህርቱን ነገርም ከሆለታ ጦር ትምህርት ቤት  ላስኪደው አላለምና ይህ ያስመሰግነዋል፡፡

Friday, January 11, 2013

ዋኤል ጎኒም ኢትዮጵያዊ ቢሆን ኖሮ…?


-->ዋኤል ጎኔም የግብጽ ደኅንነት ሰዎች ደብድበው የገደሉትን ካሊድ ሰኢድ ለማሰብ ‹‹እኔም ካሌድ ሰኢድ ነኝ›› የተሰኘ የፌስቡክ ገጽ ከፍቶ ለግብጽ አብዮት ያበቃ ሰው ነው፡፡ የመጀመሪያውን የአደባባይ እንውጣ ጥሪ ያቀረበው ይኸው የፌስቡክ ገጽ ነው፡፡ ዋኤል አደባባይ የወጡበትን የመጀመሪያ ቀን (ጃንዋሪ 25) አንድ ዓመት ለማክበር (Revolution 2.0 የተባለ) መጽሐፍ አሳትሟል፡፡ የመጽሐፉ ገቢ በሙሉ በአብዮቱ ለተጎዱ ሰዎች መደጎሚያ እንደሚውልም ተነግሯል፡፡ አሁን እዚህ ልጽፍላችሁ ያሰብኩት ግን ዋኤል ገጹን እና የግል ማንነቱን አስመልክቶ ለሚቀርብለት ጥያቄ ይሰጥ የነበረውን መልስ ነው (መጽሐፉ ላይ እንዳሰፈረው)፤ ዋኤል ኢትዮጵያዊ ቢሆንና የከፈተው ገጽም ኢትዮጵያዊ ቢሆን ኖሮ… በሚል ምናባዊ ምሳሌ፡፡ ስለዚህ ጽሑፉ በዋኤል የተጻፈው በኢትዮጵያኛ ተተርጉሞ ነው ልትሉት ትችላላችሁ፡፡

ስምህ ማነው?

[1]ስሜ ሽብሬ ደሳለኝ ነው፤
[2]ስሜ ዩሱፍ አብደላ ነው፤
[3]ስሜ እስክንድር ነጋ ነው፤
[4]ስሜ ርዕዮት አለሙ ነው፤
[5]ስሜ አሕመዲን ጀበል ነው፤
[6]ስሜ አንዱአለም አራጌ ነው፤
[7]ስሜ በቀለ ገርባ ነው፤
[8]ስሜ ኦልባና ሌሊሳ ነው፤
[9]ስሜ መስፍን ነጋሽ ነው፤
[10]ስሜ አርጋው አሽኔ ነው፤

ስሜ…. ብዙ ነው፡፡

እኔ በጎዳና ላይ የተገደልኩ፣ ያለወንጀሌ የታሰርኩ፣ ያለሀጢያቴ የተገረፍኩ፣ መብቴን በፍርሐት የተነጠቅኩ፣ ከገዛ አገሬ የተሰደድኩ ኢትዮጵያዊ ነኝ፡፡

ዕድሜህ ስንት ነው?

ዕድሜዬ ይህን ያህል ነው አልልም፤ ነገር ግን ከተወለድኩ ጀምሮ ያለው ያው አምባገነን መሪ ነው፤… ሙስናውም ያው ነው፤…. ጭቆናው ያው ነው፤… እናም በአገሬ የገነነው የፖለቲካ ፓርቲ ‹‹ተስፋ የለም›› ይባላል፡፡

Saturday, January 5, 2013

ተቃዋሚን በአንድ የመፈረጅ ጣጣ




መቼም ተቃዋሚ ስል የትኛው ዓይነቱን ተቃውሞ ለማለት እንደፈለኩ ሳይገባችሁ የቀረ አይመስለኝም፡፡ በሃገራችን በአሁኑ ሰዓት የኢሕአዴግን አገዛዝ ወይም መንግሥትን የሚቃወሙትን ማለቴ ነው፡፡ በግለሰብ ደረጃ እና በተቋም መልክ ያልተደራጁትን ተቃዋሚዎች ትተን (እነርሱ ቢበዙም) ከምርጫ ቦርድ ዕውቅና ያገኙ ፓርቲዎችን ብቻ ብንቆጥር 79 ናቸው፡፡ (ምንጭ፤ የምርጫ ቦርድ ድረገጽ)

በተቃዋሚ ፓርቲዎች ብዛት ደረጃ የሚሰጥ ዓለም አቀፍ ተቋም ቢኖር ኖሮ በዚህ እንኳን ከመጨረሻ ሳይሆን ከመጀመሪያ አንደኛ እንደምንሆን ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ የተቃዋሚ ፓርቲዎችን በወቅቱ ያላቸውን የሥራ ብቃት እና ቆራጥነት ማነስ ትተን፤ በቁጥር መብዛታቸው ብቻ በራሱ የፖለቲካ አካሄዳችን ብዙ እንደሚቀረው እና የአመለካከት ችግር እንዳለ በግልፅ የሚያሳይ ነው፡፡ እንጂ በሰላም ሃገር ለአንዲቷ ሃገር ይሄ ሁሉ ፓርቲ እኔ ነኝ ብቸኛው አማራጭ በሚል የተለየዩ አካሄዶችን እያሳየ ልባችን ባልከፋፈለው ነበር፡፡

የተቃዋሚዎቹ ብዛት ከላይ እንደገለፅኩት ሆኖ ሳለ፤ በኢህአዴግም በተቃዋሚዎችም ዘንድ ተቃዋሚዎችን እንደ አንድ የመቁጠር/የመፈረጅ ችግር በስፋት የሚስተዋል ነገር ነው፡፡

ከኢሕአዴግ ጎራ

የኢሕአዴግ ፓርቲ፣ በፓርቲው ስር የሚገኙ ተቋማት፣ የፓርቲው አድናቂ፣ አፍቃሪ እና ተቆርቋሪ የሆኑ ከዚህ ምድብ ይካተታሉ፡፡ በዚህ ምድብ ያሉ ስለተቃዋሚዎች ሲናገሩ ስትሰሙ ወይም የጻፉትን ስታነቡ በአብዛኛው አስተያየታቸውን የሚሰጡት ሁሉንም እንደ አንድ በመቁጠር መሆኑን መታዘባችሁ ግድ ነው፡፡ እንግዲህ ያሳያችሁ 80 የሚጠጉ ተቃዋሚ ፓርቲ መኖራቸው እየታወቀ፤ ሁሉም ደግሞ የየራሳቸው ልዩነት እና አቋም እንዳላቸው እየታወቀ፤ ለምን ሁሉንም ጨፍልቀው በአንድነት፣ አንድ ዓይነት ስድብ እንደሚሳደቡ (መቼም ‹‹ምስጋና›› አንጠብቅባቸውም) ግራ የሚያጋባ ጉዳይ ነው፡፡ ተቃዋሚዎቹ አንድ የሚያደርጋቸው ነገር ቢኖር ኢህአዴግን መቃወማቸው እና ተቃዋሚነታቸው ብቻ ነው እንጂ የሚቃወሙበት መስመር፣ ምክንያት፣ የያዙት አጀንዳ፣ ዓላማቸውና እና የሚከተሉት አሰራር ፍፁም የተለያየ ነው፡፡

እውነቱ ይሄ ሆኖ ሳለ በዚህ ምድብ ያሉት ግን አንደኛው ተቃዋሚ ያለውን ሐሳብ ‹‹ተቃዋሚዎች እንዲህ አሉ፣ ሊያደርጉ ነው፣ ናቸው›› በሚል የሁሉም እንደሆነ በማስመሰል ተቃውሞን በሙሉ በአንድ በመፈረጅ አስቸጋሪ መልክ አስይዘውታል፡፡

እንግዲህ አስቡት፤ ለምሳሌ እኔ በግሌ /እንደ አንዲት ነጠላ ግለሰብ/ ኢሕአዴግን ተቃውሜ ያነሳሁትን ሐሳብ፤ ‹ተቃዋሚዎች እንዲህ አሉ› ወይም ‹ይላሉ› ተብሎ የኔ የግሌ ብቻ የሆነው ሐሳብ የሁሉም ነው ሲባል፤ ወይንም ደግሞ አንድ ተቃዋሚ ፓርቲ ተቃውሞ ያነሳውን ሐሳብ፤ የተቀሩት ተቃዋሚዎች እንዳሉት ተደርጎ ሲወሰድ እና የተቃዋሚዎች የጋራ ሐሳብ እንደሆነ ሲቀቆጠር፡፡

በተጨማሪም እነዚህ ምድቦች  የሚቃወምን ግለሰብ ከተቃዋሚ ፓርቲ ጋር የማስተሳሰር ክኅሎትም አላቸው፡፡ አንድ ግለሰብ ከተቃወም በቅድሚያ በአእምሯቸው የሚመጣው ከጀርባው የትኛው ፓርቲ እንዳለ ነው እንጂ፤ ግለሰብ እራሱን ችሎ መቃወም እንደሚችል አያስቡም ወይም ማሰብ የሚፈልጉም አይመስለኝም፡፡

ከተቃዋሚ ጎራ

በዚህ ምድብ ኢሕአዴግን በተለያየ ደረጃ የሚቃወሙ ግለሰቦች፣ ሚዲያዎች እና የፖለቲካ ፓርቲ መስርተው የሚቃወሙትን ይመለከታል፡፡ በዚህ ምድብ የሚገኙት ከላይ እንደተነጋገርነው ብዛታቸውም የትዬለሌ ነው ልዩነትም አላቸው፡፡ ሆኖም ብዙዎቹ ‹የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው› በሚለው ብሒል መሠረት የተቃኘ የእርስ በርስ ግንኙነት እንዲኖራቸው ይፈልጋሉ፡፡ ይህ ሲብራራ፡ እከሌ የተባለ ግለሰብ ወይም ሚዲያ ወይም ፓርቲ የተቃወመበትን ሐሳብ ሌሎችም በተለያየ ደረጃ የሚገኙ ተቃዋሚ ግለሰቦች፣ ሚዲያዎች ወይም ፓርቲዎች እንዲቀበሉት/እንዲደግፉት ይጠበቃል ማለት ነው፡፡ ካልሆነ የደጋፊ ብዛት ባለው ተቃዋሚ፤ ከተቃዋሚ ሰፈር የማግለል እና ስም የማጥፋት/ስም የመስጠት ዘመቻ ይካሄዳል፡፡ ገና ለገና በተቃዋሚ ጎራ ስላሉ በሁሉም ጉዳይ መስማማት እና ስምምነትንም መግለፅ ግዴታ መሆን የለበትም፡፡ አንደኛው ተቃዋሚ የሌላውን ሐሳብ ሁሉ (ኢሕአዴግን ስለተቃወመ ብቻ) መቀበል ከቻለማ መከፋፈልን እና ተለያይቶ መሥራትን ምን አመጣው? ለምንስ ያ ሁሉ ፓርቲ ተመሠረተ?

በሁለቱም ጎራ በተደጋጋሚ ተቃዋሚን በአንድ በመፈረጅ የሚሠሩትን ስህተቶች ለማስወገድ፤  በኢሕአዴግ ጎራ ያሉት፣ በተቃወሚው በኩል ያለውን ልዩነት ከግምት ውስጥ ያስገባ  እንቅስቃሴ ማድረግ እንደሚገባ እንዲሁም ተቃዋሚዎች ኢህአዴግን መቃወም ብቻ አንድ እንደማያደርግ በመገንዘብ ለልዩነቶቻቸው ዋጋ በመስጠት እና በመከባበር ላይ የተመሠረተ አካሄድ በመከተል፤ በሁለቱም ምድብ የሚገኙት የአመለካከት ለውጥ ማምጣት አለባቸው የሚል እምነት አለኝ፡፡
----
የዚህ ጽሑፍ ዋና ቅጂ በኢትዮጵያ እንዳይነበብ በታገደው የዞን ዘጠኝ ጦማር ላይ ይገኛል፡፡