Friday, February 22, 2013

#Ethiopia, #StopCensorship: ሳንሱር ዋጋ ያስከፍላል


በናትናኤል ፈለቀ

ለምዕራባዊያኑ የመጨረሻ  ወር በሆነው ዲሴምበር ወር መጀመርያ በሀገረ አሜሪካ ኢትዮጵያዊውን ጦማሪ እና እስክንድርነጋን ለማሰብ የተዘጋጀ መድረክ ነበር፡፡ በመድረኩ ላይ ስለ እስክንድር ነጋ የተናገሩት ተዋናይ ሊዬቭ ሽሬ የይበር እና ጸሐፊ ካርል በርንስቴይን ነበሩ፡፡ በርንስቴይን  ከ40 ዓመታት በፊት የዋሽንግተን ፖስት ዘጋቢ ሆኖ በሚሠራት ወቅት ከባልደረባው ቦብ ዉድወርድ ጋር በመሆ ን በአሜሪካ መንግስት ታሪክ ትልቅ የተባለውን እና የዋተርገቱ ቅሌት በመባል ሚታወቀውን የመንግሥት ባለሥልጣናት ያሳተፈ የሙስና ቅሌት አጋልጠዋል፡፡ በነዚህ ሁለት ዘጋቢዎች ታሪካዊ ማጋለጥ ምክንያት በወቅቱ አሜሪካን በፕሬዝዳንትነት ይመሩ የነበሩት ሪቻርድ ኒክሰን ስልጣናቸውን በገዛ ፈቃዳቸው እንዲለቁ ሆኗል፡፡

የዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ምሳሌ ተደርጋ የምተጠቀሰው አሜሪካ በወቅቱ የመንግሥት ባለሥልጣናትን ተጠያቂነት ለማረጋገጥ አቅም የሚያንሳት ሀገር አልነበረችም፡፡ የፖለቲካ ባህሏም  (በጥቅሉ) ተጠያቂነትን የሚያበረታታ እና ሙስናን የመሰሉ ተግባራትን አፀያፊ አድርጎ የሚቆጥር ነበር/ነው ማለት ይቻላል፡፡ በዚህም ሥርዓት መሐከል ግን እንክርዳድ አይጠፋውም፡፡ እናም መደበኛው የተጠያቂነት ሥርዓት ያልደረሰበትን ማማ አራተኛው የመንግሥት ክንፍ  (fourth organ of government) በመባል የሚታወቀው ሚዲያ አጋለጠው፡፡

ነጻ የሆኑ መገናኛ ብዙኃን መኖር እና ዜጎች ሐሳባቸውን መግለጽ እና መወያየት መቻላቸው የመንግሥትን እና የባለሥልጣናቱን ተጠያቂነትን ለማረጋገጥ እንዲሁም ሕዝብን ከአደጋ ለመጠበቅ ቁልፍ መሣሪያዎች ናቸው፡፡
እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ደሃ ሀገራት እያንዳንዱ የመንግሥት መዋለ ነዋይ ለሚፈለግለት ዓላማ መዋል አጥብቆ የሚፈለግ ነገር ነው፡፡ እውነታው ግን ይሄ አይደለም፡፡ በደሃ ሀገራት ስልጣን የሚይዙት ሰዎች/የፖለቲካ ፓርቲዎች ግን አንድም የራሳቸውን ግለሰባዊ ችግር ከሀገሪቱ ችግር በማስቀደም ወይንም በስግብግብነት አልፎ አልፎም ደግሞ ከብቃት ማነስ ሀገራቸው እጅግ አድርጋ የምትፈልገውን መዋለ ነዋይ ያባክናሉ፡፡ ይባስ ብሎም አብዛኞቹ ደሃ ሀገራት የሚመሩት ሁሉንም ነገር መቆጣጠር በሚፈልጉ እና ለምንም አይነት ነጻነት እና መብት ደንታ በማይሰጣቸው መሪዎች  (totalitarian) ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የሀገር ሃብት ሲመዘበር እና አለአግባብ ጥቅም ላይ ሲውል ለምን ብሎ የሚጠይቅ አካል አይኖርም፡፡ ካለምፍዳው እጅግ ብዙ ይሆናል፡፡


የሕዝብ ውክልና የሌላቸው/የሚጎላቸው የድሃ ሀገራት መሪዎች ስልጣን ላይ በሕይወት እስካሉ ድረስ ለመቆየት ሀገራቸው ላለባት ምጣኔ-ሃብታዊ እና ሌሎችም ችግሮች እራሳቸውን ብቸኛ አማራጭ አድርገው ያቀርባሉ፡፡ ይህንን ለማድረግ አብዛኛዎቹ መሪዎች ሕዝብ በከፈለው ግብር የሚተዳደሩ መገናኛ ብዙኃንን የራሳቸውን ተረክ ለመፍጠር ይጠቀሙበታል፡፡ እነሱ ከሌሉ ሀገሪቷ የምትገባበትን ‹ሲኦል›  ይሰብኩበታል፡፡ ይህ ብቻ አይበቃቸውም፡፡ ምንም ዓይነት የተለየ ተረክ ለሕዝብ እንዲደርስ አይፈቅዱም፡፡ የሐሳብ አሀዳዊነትን በሕዝብ ላይ ለመጫን ይመቻቸው ዘንድ የበይነ-መረብ ማጥለል፣ የተለየ ሐሳብ ያላቸውን ጋዜጦች፣  መጽሔቶች ይዘጋሉ፤ ጋዜጠኞችን ያዋክባሉ፣  ያስራሉ፡፡ በዚህም የተነሳ ስልጣን ላይ ያሉት ሰዎች ሀገርን የሚጠቅም ነው ብለው የሚያወጧቸው ምጣኔ-ሀብታዊ (ሌሎችም) ፖሊሲዎችን የተለየ ምልከታ ሰጥቶ ጥቅሞቹን እና ጉድለቶቹን ተንትኖ እና ከሕዝብ ፍላጎት ጋር ያላቸውን መጣጣም አመዛዝኖ ለሕዝብ የሚያቀርብ አማራጭ እንዳይኖር ያደርጋሉ፡፡ እናም ፖሊሲዎች መታረም ከሚችሉት ህፀፆቻቸው ጋር በሰሠሯቸው ሰዎች ተደጋግመው ከተወደሱ በኋላ ወደሥራ ይገባሉ፡፡

እነዚህ መሪዎች አንድ መሠረታዊ የሆነ የሰው ልጆች ተፈጥሮን ዘንግተዋል፡፡ ማንኛውም ጤነኛ ሰው የሚቀበለውን መረጃ እንደተሰጠው አይውጠውም፡፡ ሁልግዜም ባይሆን ባመዛኙ፣  የሰው ልጆች የሚሰጣቸውን መረጃ ማመዛዘን ይፈልጋሉ -  በተለይም ድጋፍ መስጠት/አቋም ሊይዙበት ለሚፈልጉት ጉዳይ ሲሆን፡፡ አማራጭ ትንተና ያጡ ዜጎ ችአንድ አንዳንዶቹ (ጥቂቶቹ) የራሳቸውን ትንተና በመስጠት አቋም ሲወስዱ አብዛኞቹ ለድጋፍም ሆነ ለተቃውሞ የሚበቃ አቋም ለመውሰድ በቂ ትንተና ለማግኘት ይቸገራሉ፡፡በመጨረሻም ፖሊሲውን ተፈፃሚ ለማድረግ የሕዝብ ተሳትፎ/ድጋፍ አጥሮናል ብለው የሚያማርሩ የመንግሥት ድምፆችን መስማት እንጀምራለን፡፡

ምጣኔ ሃብት እና ሐሳብን የመግለጽ ነፃነት

እ.አ.አ 1989 ድሬዝ እና ሴን የተባሉ የምጣኔ ሀብት ተመራማሪዎች ባያደረጉት ጥናት ነጻ መገናኛ ብዙኃን ባለበት ሀገር አንድም ግዜ ረሀብ ተከስቶ እንደማያውቅ ጠቁመዋል፡፡ ይህንንም ሲደግፉ ነጻ የሆነ የመረጃ ፍሰት ባለባቸው ሀገራት መንግሥታትን (ዴሞክራሲያዊ ባይሆኑም እንኳን) ከሕዝብ የሚመጣ ጫና ውስጥ ስለሚከታቸው እና ይህንንም ለማስወገድ ሲሉ ቀድመው የሕዝብን ጥያቄ የሚመልስ እርምጃ ስለሚወስዱ እንደሆነ ይተነትናሉ፡፡ ኢሻም፣ ካፍ ማን እና ፕሪቼት የተባሉ ምሁራን እ.አ.አ  1997 ባደረጉት ጥናት መሠረት ደግሞ ግለሰባዊ ነጻነቶች  (ሐሳብን የመግለፅን ጨምሮ) ማክበር በመንግስት ቁጥጥር ስር የሚከናወኑ ፕሮጀክቶችን ምጣኔ-ሃብታዊ ውጤት  (Project’s Rate of return) እስከ 20 በመቶ ያክል ድረስ ይጨምረዋል፡፡ እንደነዚሁ አጥኚዎች ትንተና መሠረት ግለሰባዊ መብቶችን  (ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ/የመሰብሰብ ነፃነት፣ ሐሳብን በነፃነት የመያዝ እና የመግለጽ፣ ሕዝባዊ ጉዳዮች ላይ በነፃነት የመሳተፍ እና ነፃ ማኅበር ማቋቋም) አለማክበር በእኩል መጠን ከሚከሰት የዓመታዊ ምርት መቀነስ፣ የበጀት እጥረት ወይንም የወጪ እና ገቢ ንግድ ላይ ከሚያጋጥም ንዝረት ባልተናነሰ ሁኔታ በመንግስት የሚካሄዱ ፕሮጀክቶች ውጤታነት ላይ ተፅዕኖ ያደርጋል፡፡

እንደ በመንግስት የሚተዳደሩ ፕሮጀክቶች ባይሆንም በግል ባለሀብቶች እና ተቋማት የሚካሄዱ ንግዶች ሐሳብን በነጻነት መግለጽ በሚቻልበት ሀገር ለገበያ የሚያቀርቧቸው ዕቃዎች እና አገልግሎቶች የኅብረተሰቡን ደኅንነት ወይንም ጥቅም አደጋ ላይ የሚጥል እንዳይሆኑ ከፍ አድርገው ይጠነቀቃሉ፡፡ በግድየለሽነት ወይንም በአጭር ጊዜ ለመክበር በሚያደርጉት ሙከራ የህብረተሰቡን ደህንነት ወይንም ጥቅም አደጋ ላይ የሚጥል ዕቃ ወይንም አገልግሎት ቢያቀርቡ ነፃ መገናኛ ብዙሃን ሁኔታውን በማጋለጥ ህብረተሰቡን ከጉዳት ይጠብቃሉ፡፡

የሳንሱርዋጋ

የሐሳብ ብዝኃነትን በመቆጣጠር ሕዝብ እነሱ የሚሉትን ብቻ እየሰማ እንዲነዳ የሚፈልጉ መንግሥታት ሐሳብን ለማፈን ብዙ ርቀት ይጓዛሉ፡፡ ሐሳብ ለማፈን ከከሚጠቀሙባቸው መንገዶች በይነ መረብን ማጥለል እና ጦማሮች እዳይከፈቱ ማገድ፣ በይነመረብን በመጠቀም ዜጎች ላይ መሰለል እና በሳተላይት የሚተላለፉ የሬድዮ እና የቴሌቪዥን ስርጭቶች ሞገዶችን መከልከል ይጠቀሳል፡፡

የአውስትራሊያ መንግስት  በ2009 ዓ.ም ሊተገብረው ያሰበው የበይነ መረብ ማጥለልን በተመለከተ ዴቪድ በርድ የተባለ ጦማሪ እንደጻፈው በበይነ መረብ የሚተላለፉ መረጃዎችን ለማጥለል ጥቅም ላይ የሚውሉት ቴክኖሎጂዎች የበይነ መረብ አገልግሎት ፍጥነትን ከ2 በመቶ እስከ 70 በመቶ ይቀንሳሉ፡፡ የማጥለል ሥራውን  ‹በውጤታማነት የሚያከናውኑት› ቴክኖሎጂዎች ደግሞ ፍጥነቱን በደንብ የሚቀንሱት ናቸው፡፡

ባሳለፍነው ነሐሴ ወር ደግሞ ኒውዮርክ ታይምስ አንድዜና ለኢትዮጵያዊያን ይዞልን ወጥቶ ነበር፡፡ ፊንፊሸር የተባለ በይነ መረብን በመጠቀም ዜጎች ላይ ስለላ ለማድረግ የሚያስችል የረቀቀ ቴክኖሎጂን እንደሚጠቀሙ ከታወቁት  10 ሀገራት አንዷ ሀገራችን መሆኗን፡፡ እንደዘገባው ቴክኖሎጂውን ለመግዛት ከ350ሺህ  በላይ የአሜሪካን ዶላር ወጪ ማድረግ ይጠይቃል፡፡ ቁጥር አንድ ጠላቷ ድህነት ለሆነ ሀገር ሕገ-መንግሥቱን ጥሶ ዜጎች ላይ ለመሰለል ይህን ያህል ወጪ ማውጣት እውነትም አሀዳዊ ተረክ ለመፍጠር ምን ያህል ርቀት እንደሚኬድ ማሳያ ነው፡፡

በሳተላይት የሚተላለፉትን ሬዲዮ እና የቴልቪዥን ስርጭትን ለመደገፍ ምን ያህል የተወሳሰበ ቴክኖሎጂ እንደሚያስፈልግ እና እሱም ምን ያህል ወጪ እንደሚያስወጣ መገመትም ቀላል ነው፡፡

ምንም እንኳን አከራካሪ ቢሆንም ዜጎች በነጻነት ሲያስቡ እና ሐሳባቸውን በነጻነት መግለጽ ሲችሉ አዳዲስ እና ውጤታማ የንግድ ሐሳቦች ማፍለቅ ቀላል ይሆንላቸዋል፡፡ ይህም ሐሳብን የመግለጽ ነጻነት መንፈግ ከሚያስከፍሉት ቀጥተኛ ያልሆኑት ዋጋዎች ውስጥ ሊካተት ይችላል፡፡

No comments:

Post a Comment