Sunday, September 9, 2012

የ2004 ዓ.ም. የጊዜ መስመር (timeline)


ይህን ጽሑፍ ለማዘጋጀት ስናስብ የትኞቹ ጉዳዮች ጉልህ ስፍራ ይኖራቸዋል የሚለውን ለመምረጥ  ብዙ ዐሳብ በህሊናችን ተመላልሷል፡፡ በአጠቃላይ ግን አብዛኛውን ሰው የሚያስማሙ ክስተቶችን ለማካተት የሞከርን ሲሆን በተለመደው ሚዲያ ስርዓት በመንግስትም ሆነ ‘ነጻ’ ሚዲያዎች  ትኩረት የተነፈጋቸውንም ለማካተት ጥረት አድረገናል፡፡እንደአለመታደል ሆኖ አማራጭ ትርክትን የሚያቀርብ የሚዲያ ተቋም በማጣታችን ምክንያት እነዚህ ጉዳዮች በወቅቱ ተቀራራቢ ሽፋን አለማግኘታው ከግምት ውስጥ ይገባልን ዘንድ እንጠይቃለን፡፡
መስከረም

የጋዜጠኞችና ፖለቲከኞች መታሰር
መስከረም 4 ቀን 2004 ዓ.ም የአንድነት ለፍትህ እና ለዲሞክራሲ ፓርቲ አመራር አባላት የሆኑት አንዱአለም አራጌ እና ናትናኤል መኮንን እንዲሁም በኢትዮጵያ የግል ፕሬስ ከተፈቀደ ጀምሮ የተለያዩ ጋዜጦችን በዋና አዘጋጅነት እና በኋላም በተለያዩ ብሎጎች ላይ ስለ ሰብአዊ መብት መንግስትን በሚሞግቱ ፅሁፎቹ የሚታወቀው እስክንድር ነጋ ከሌሎች ተጨማሪ ተከሳሾች ጋር በአሸባሪነት ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር ዋሉ፡፡


አስናቀች ወርቁ ከዚህ አለም በሞት ተለየች
ታዋቂዋ ድምጸዊት እና የመድረክ ሰው አስናቀች ወርቁ በአመቱ መጀመሪያ በሞት ካጣናቸው የጥበብ ሰዎች አንደዋ ነበረች፡፡ አስናቀች ለረዥም ጊዜ በህክምና ስትረዳ ቆይታ መስከረም ወር 2004 አም 76 አመትዋ ከዚህ አለም በሞት ተለይታለች፡፡ አስናቀች እንደእየሩሳሌም በተሰኘው ታዋቂ ዘፈንዋ እንዲሁም በቀድሞ ጊዜ በነበሩ የመድረክ ስራዎችዋ ትታወቃለች፡፡

የትግራይ ፖሊስ ኦርኬስትራ ቡድን አባላት ላይ የመኪና አደጋ ደረሰባቸው
መስከረም 15 ቀን 2004 ዓ.ም ከትግራይ ክልል ተነስተው ወደ ሱዳን ሲገዙ በነበሩት የትግራይ ፖሊስ ኦርኬስትራ ቡድን አባላት ጭኖ ይጓዝ የነበረ አውቶቢስ ላይ የመኪና አደጋ ደረሰ፡፡

የደርግ ባለሥልጣናት በይቅርታ ከዕስር ተፈቱ
መስከረም 23 ቀን 2004 ዓ.ም በፍርድ ቤት የተወሰነባቸው የሞት ፍርድ ግንቦት 24 ቀን 2003 ዓ.ም ወደ ዕድሜ ልክ እስራት መቀየርን ተከትሎ 16 ያህል የሚሆኑ የደርግ ባለስልጣናት የጠየቁት ይቅርታ በመንግስት ተቀባይነት አግኝቶ ከ20 አመት የእስር ቤት ቆይታ በኃላ በነጻ ተለቀቁ፡፡

ኢትዮጲያ የኤሌክትሪክ ሃይል ወደውጭ መላክ ጀመረች
መስከረም 24 ቀን 2004 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ጅቡቲ በመገኘት 35 ሜጋ ዋት ከኢትዮጲያ በኤክስፖርት መልክ ማስተላለፍ የጀመረውን ማስተላለፊያ ጣቢያ መርቀው ስራ አስጀመሩ፡፡ ማተላለፊያ ጣቢያው የተገነባው ኢትዮጲያና ጅቡቲ የኤሌክትሪክ ሃይል ለመገበያየት የ25 አመት ስምምነት መፈራረማቸውን ተከትሎ ነበር፡፡ በምረቃ ስነ-ስርዓቱ ላይ የመብራት መቋረጥ ተከስቶ እንደነበር ይታወሳል፡፡

ጥቅም


መድረክ ግንባር ሆነ
ጥቅምት 2 ቀን 2004 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክሪያሲያዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) ከፓርቲዎች ህብረት ወደ ግንባርነት መሸጋገሩን አስታወቀ፡፡ ወደ ግንባርነት መሸጋገሩ የበለጠ የተጠናከረ ሰላማዊ እና ዴሞክሪያሲያዊ ትግል ለማካሄድ እንደሚረዳው ገልፆ ነበር - ግንባሩ፡፡ በወቅቱ ዶ/ር መራራ ጉዲና ወደ ግንባርነት የተሸጋገርነው ግንባርን በግንባር ለመግጠም ነው የምትል ንግግር ጣል አድርገው ነበር፡፡

ስዊድናውያኑ ጋዜጠኞች ታሰሩ
ጥቅምት 9 ቀን 2004 ዓ.ም መንግስት አሸባሪ ድርጅትን አግዛችኋል እንዲሁም የሀገሬን ድንበር በህገ-ወጥ መንገድ ጥሳችሁ ገብታችኋል በሚል ሁለት የሲዊድን ዜግነት ያላቸው ጋዜጠኞች ላይ የመሰረተው ክስ መታየት ጀመረ፡፡ ሁለቱም ጋዜጠኞች ከአሸባሪ ድርጅት ጋር በተያያዘ የተመሰረተባቸውን ክስ ጥፋተኛ አይደለንም ሲሉ በሁለተኛው የሀሪቱን ድንበር በህገ-ወጥ መንገድ ጥሶ በመግባት የተመሰረተባቸውን ክስ አምነዋል፡፡ ጋዜጠኞቹ በቁጥጥር ስር ሲውሉ ከኦጋዴን ነፃ አውጪ ግንባር ተዋጊዎች ጋር ነበሩም ተብሏል፡፡

የመምህራን ደሞዝ ጭማሪ እና አድማ
መምህራን የተደረገላቸውን የደሞዝ ጭማሪ ከንቀት የሚቆጠር እና የሞያውን ክብር ዝቅ ያደረገ ነው በማለት ተቃውሞ አሰሙ፡፡ መምህራኖቹ የደሞዝ ጭማሪውን ቢቃወሙም መንግስት እና “የመምህራን ማህበሩ” ጭማሪ ሳይሆን የእርከን ማሻሻያ ነው ብለው ያስተባበሉ ሲሆን መምህራኑ በበኩላቸው ከደሞዛቸው ለማህበሩ የሚቆረጠው ገንዘብ እንዲቆምና ማህበሩ እንደማይወክላቸው ተናግረው ነበር፡፡ ጥያቄው እስኪመለስ ድረስ በተለያዩ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ትምህርት ለተወሰነ ጊዜ ተቁዋርጦ የነበረ ሲሆን የመንግስት አካላት የተለያዩ ድርድሮች በማድረግ ትምህርት እነዲቀጥል ማድረግ ችለዋል፡፡

የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ከምክር ቤት አባላት ለቀረበላቸው ጥያቄዎች መልስ ሰጡ
በተመሳሳይ ቀን የቀድሞ የኢፌደሪ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በ2004 ዓ.ም ለመጀመሪያ ጊዜ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርበው መስከረም 30 ቀን 2004 ዓ.ም በፕሬዝዳንት ግርማ ቀርቦ የነበረውን የመንግስት አመታዊ መረሃ-ግብር ላይ ከምክር ቤት አባላት ለቀረበላቸው ጥያቄዎች መልስ ሰጡ፡፡ በአሸባሪነት ተጠርጥረው ስለተያዙት የፖለቲካ ፓርቲ አባላት እና ጋዜጠኞች ተጠይቀው - በቂ መረጃ እስኪያገኝ ነው እንጂ በቁጥጥር ስር የዋሉት ግለሰቦች በሽብርተኝነት ተግባር ላይ መሰማራታቸውን መንግስት ካወቀ እንደቆየ አሁንም መረጃ እየተሰባሰበባቸው ያሉ በሽብርተኝነት ላይ የተሰማሩ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር አባላት እንዳሉ በመጥቀስ መልሰዋል፡፡ ሁለቱን ስዊድናዊያን በሚመለከትም የሀገሪቱን ድንበር ጥሰው ከሽብርተኛ ቡድን ጋር ታጥቀው እንደተያዙ እና እንደማንኛውም ሽብርተኛ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እንደሚታይ ተናግረው ነበር፡፡ ‹‹የነጭም ደም ቀይ ነው፤ የጥቁርም ደም ቀይ ነው… ጋዜጠኞቹ የአሜሪካንን ድንበር ጥሰው ታጥቀው ቢገኙ ማንም የኔ ናቸው ሳይሆን አላውቃቸውም ነበር የሚለው›› ብለው ነበር፡፡

አቶ ያረጋል አይሸሹም ንብረታቸው ታገደ
ጥቅምት 9 ቀን 2004 ዓ.ም የቤንሻንጉል ጉምዝ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስትን በፕሬዝዳንትነት ያገለገሉት አቶ ያረጋል አይሸሹም በሳቸውና በቤተሰቦቻቸው ስም የተመዘገበ ማንኛውም ንብረት እንዳይንቀሳቀስ ታገደ፡፡ የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ትዕዛዙን ያስተላለፈው የስነ-ምግባርና የፀረ-ሙስና አቃቤ ህግ ግለሰቡን በሙስና ወንጀል በመጠርጠር ባቀረበው ጥያቄ መሰረት ነበር፡፡

የንግድ ሚኒስትሩ እና ሚኒስትር ዲኤታው ከስልጣናቸው ተነሱ
የንግድ ሚንስቴር ሚኒስትር አቶ አብዱራህማን ሼክ መሐመድ እና ሚኒስትር ዲኤታው አቶ አሕመድ ቱሳ ከስልጣናቸው ተነሱ፡፡ የስልጣን ሽረቱ የተካሄደው የዋጋ ግዥበትን ለመቆጣጠር ለአምስት ወር ቆይቶ ያለምንም ውጤት እንዲነሳ የተደረገው የዋጋ ተመን ውድቀት ጋር በተያያዘ ባሳዩት የብቃት ማነስ መሆኑ ተገልጾ ነበር፡፡

የአወሊያ ተማሪዎች አመጹ
ኢትዮጵያዊያን ሙስሊሞች መንግስት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ አይግባ እና ስልጣን ላይ ያለው መጅሊስ አይወክለንም፤ በምርጫ ይተካልን በሚል ሰላማዊ በሆነ መንገድ ጥያቄያቸውን ማሰማት ጀመሩ፡፡በዚህ በአወሊያ ተማሪዎች የታገዱ መምህራኖቻችን ይመለሱ ጥያቄ ተነሳው የሙስሊሞች ጥያቄም በመጠንም ሆነ በይዘት ሰፍቶ ለወራት ዘለቀ፡


ህዳር

የኔሰው ገብሬ ራሱን አቃጠለ
ኢትዮጵያዊው መምህር የኔሰው ገብሬ ፍትህ መልካም አስተዳደር እና ልማት የለም በሚል አርብ ህዳር 1 ቀን 2004 ዓ.ም አቃጠለ፡፡

ዳዊት ከበደ እና አቤ ቶኪቻው ከአገር ተሰደዱ፡፡
ህዳር 5 ቀን 2004 ዓ.ም ታዋቂው የፍትህ ጋዜጣ አምደኛ አቤ ቶኪቻው ህዳር 9 ቀን ደግሞ የአውራምባ ጋዜጣ ባለቤትና ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ዳዊት ከበደ ከአገር ተሰደዱ፡፡ አበበ ቶላ ለ6 ወራት የደህንነት መስሪያ ቤት መታወቂያ የያዘ ሰው በተለያየ መንገድ ጫና እና ክትትል ሲያደርግበት መቆየቱን የገለጸ ሲሆን የዳዊትን መሰደድ ተከትሎ ደግሞ አውራምባ ታይምስ ጋዜጣም ተዘጋ፡፡

ኢትዮጲያ ወታደሮቿን ዳግም  ወደ ሱማሌ ላከች
ህዳር 15 ቀን 2004 ዓ.ም አዲስ አበባ ላይ በተደረገው የኢጋድ ጉባዔ ኢትዮጲያ ለአፍሪካ ህብረት ሰላም አስከባሪ ሃይል እገዛ ሚያደርግ ሃይል ወደ ሶማሊያ እንድትልክ አባል ሃገራት ተስማሙ፡፡ በስምምነቱ መሰረትም የኢትዮጲያ ወታደሮችዋን በድጋሚ ወደ ሶማሊያ ላከች፡፡


ታህሳስ

የሁለት ምርጫዎች ወግ መጸሃፍ ተመረቀ
ታህሳስ 10 ቀን 2004 ዓ.ም የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ፅህፈት ቤትን በበላይነት የሚመሩት አቶ በረከት ስምኦን ‹‹የሁለት ምርጫዎች ወግ›› ሲሉ የሰየሙትን መጽሐፋቸውን ለንባብ አቀረቡ፡፡መጽሐፉ ለሽያጭ የቀረበው በ90.00 ብር  ሲሆን በሸራተን ሆቴል በተካሄደው ምርቃት ስነስርአት ላይ ሼህ አላሙዲን መጻሃፉን ባያነቡትም በጣም ጥሩ እንደሆነ ተናግረው ነበር፡፡፡

በብርጋዴር ጀነራል ከማል ገልቹ የሚመራው ኦነግ የመገንጠል አቅዋሙን እንደቀየረ ገለጸ

በብርጋዴር ጄነራል ከማል ገልቹ የሚመራው ኦነግ የመገንጠል ሃሳቡን ከፕሮግራሙ ላይ ማንሳቱን አሳወቀ፡፡ በሜኒሶታ ከተደረገው ልዩ ስብሰባ በሁዋላ ጄነራሉ እንደተናገሩት የሁሉንም ብሄሮች  መብቶች እና እኩልነትን ያረጋገጠች ኢትዮጲያን መመስረት እነደሚደግፉ ገልጸዋል፡፡በዚሁ መግለጫ ላይ ኦነግ ለኦሮሞ ህዝብ ነጸነት ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጲያውያን ነጸነትም እንደሚታገል አንዲሁ ተገልጹዋል፡፡


ጥር

የኤርታሌ ቱሪስቶች በታጣቂዎች ጥቃት ተፈፀመባቸው
ጥር 9 ቀን 2004 ዓ.ም በአፋር የኤርታሌን አካባቢ ለመጎብኘት በቦታው የነበሩ የውጭ ሀገር ጎብኚዎች እና ኢትዮጲያዊያን አስጎብኚዋቻቸው ላይ ታጣቂዎች ጥቃት ፈጸሙ፡፡በጥቃቱም 5ቱን ጎብኚዎች ሲገደሉ 2ቱን በከፍተኛ ሁኔታ ቆስለው 2 ኢትዮጵያዊያን እና 2 የውጪ ዜጋ ጎብኚዎች ደግሞ ታፍነው ተወሰዱ፡፡ጥቃቱ የተፈፀመው ኢትዮጵያ እና ኤርትራ ከሚዋሰኑበት ድንበር 25 ኪ.ሜ አካባቢ ሲሆን የኢትዮጵያ መንግስት ለጥቃቱ ሽብርተኞችን እያሰለጠነ ወደ ኢትዮጵያ ይልካል ያለውን የኤርትራ መንግስት ተጠያቂ አድርጎ ነበር፡፡


የአፍሪካ ሕብረት ሕንፃ ተመረቀ
ጥር 18 ቀን 2004 ዓ.ም በቻይና መንግስት እርዳታ የተገነባው አዲሱ የአፍሪካ ህብረት ህንፃ ተመረቀ፡፡ በአዲሱ ህንፃ ቅጥር ጊቢ በአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምስረታ ወቅት ምዕራባዊ አፍሪካዊት ሀገር ጋናን ይመሩ የነበሩት የክዋሜ ንክሩማ ማስታወሻ ሀውልት የቆመ ሲሆን በወቅቱ የኢትዮጵያ አቻቸው የቀዳማዊ አፄ ኃይለስላሴ ሀውልት አለመሰራት ጥቂት የማይባሉ ኢትዮጵያንን አስከፍቶ ነበር፡፡

አወዛጋቢው የሊዝ አዋጅ ፀደቀ
ጥር 30 ቀን 2004 ዓ.ም የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በአመቱ ለሁለተኛ ጊዜ የሕዝብ ተወካች ምክር ቤት ተገኝተው መንግስት ተግባራዊ እንዲሆን ያስፀደቀውን የመሬት ሊዝ አዋጅ በተመለከተ ማብራሪያ ሰጡ፡፡አዋጁ ከጸደቀ በኃላ በሰጡት በዚህ ማብራሪያ ላይ ስለ መንግስት ሌቦች እና የግለሰብ ሌቦች በመሬት ዙሪያ ያለውን ችግር እንዳባባሱት ተናገሩ፡፡


የካቲት

አንዱአለም ተደበደበ
የካቲት 7 ቀን 2004 ዓ.ም. አንዱአለም አራጌ በእስር ቤት ውስጥ ድብደባ ተፈፅሞበታል ሲል አንድነት ፓርቲ አስታውቀ፡፡ አንዱአለም በድብደባው ምክንያት ጭንቅላቱ ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰበት ተዘግቦ የነበር ሲሆን የአንዱዋለም ጉዳዩን በሚገባ የሚያብራራ ጹሁፍ በፍትህ ጋዜጣ በኩል ለንባብ በቅቶ ነበር፡፡

ደራሲና ጋዜጠኛ ስብሃት ገብረ እግዚአብሔር አረፈ
የካቲት 12 ቀን 2004 ዓ.ም ደራሲ ስብሃት ገብረ እግዚአብሔር በህክምና ሲረዳ ቆይቶ  በተወለደ በ76 አመቱ ከዚህ አመት በሞት ተለየ፡፡ በትኩሳት፣ሌቱም አይነጋልኝ እና በአምስት ስድስት ሰባት መጸሃፍቶቹ የሚታወቀው ጋሽ ስብሃት አድናቂዎቹ እና ባልደረቦቹ በተገኙበት የቀብር ስነስርአቱ በቅድስት ስላሴ ካቴድራል ቤተ ክርስቲያን ተፈጸመ፡፡

ደራሲና ጋዜጠኛ ማሞ ውድነህ አረፉ
የካቲት 23 ቀን 2004 ዓ.ም ደራሲና ጋዜጠኛ ማሞ ውድነህ ከዚህ አለም በሞት ተለዩ፡፡ የ54 መጻህፍት ደራሲና ተርጓሚ የነበሩት አቶ ማሞ የ82 አመት ባለፀጋ እና የ6 ልጆች አባት ነበሩ፡፡ ቀብራቸውም የካቲት 24 ቀን 2004 ዓ.ም. በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል፡፡


የዩኒቲ ኮሌጁ ዶ/ር ፍስሐ ተሰደዱ
የካቲት 29 ቀን 2004 ዓ.ም የዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ መስራችና ባለቤት የነበሩት ዶ/ር ፍሰሐ እሸቱ ከሀገር ተሰደዱ፡፡ ዶ/ር ፍስሐ ሀገር ለቀው ለመውጣት የተገደዱት ከአስር በላይ አዋጪ የሚሏቸውን የንግድ ሃሳቦች ወደ ተግባር ለውጦ ለሀገርን ለወገን ጥቅም እንዲሰጡ የነበራቸው ህልም በመንግስት ምክንያት እውን መሆን ስላልቻሉ መሆኑን ተናግረው ነበር፡፡ ሙሉ ሰአታቸውንም የኢትዮጲያ ብሔራዊ የሽሽግግር ጉባዔ Ethiopian National Transition Council (ENTC) ለማቋቋም እንደሚያውሉም ተናግረዋል፡፡


ጋቢት     
       
 የኢትዮጵያ ጦር የኤርትራ መንግሥት ላይ  የማጥቃት እርምጃ ወሰደ
መጋቢት 6 ቀን 2004 የኢትዮጵያ መንግስት የኤርትራ መንግስት እና “የተላላኪዎቹን” የጥፋት  ማዕከላትን ማውደሙን አስታወቀ፡፡በአፋር ክልል በጉብኝት ላይ የነበሩትን ቱሪስቶች ላይ መግደሉንና ማሰቃየቱን የሚል ሰበብን እንደመነሻ ምክንያት በመውሰድ  በሦስት ካምፖች ተሰባስቦ  የነበረውን የኤርትራ መንግስት ሀይል ላይ ወታደራዊ እርምጃን ወስዷል፡፡የኢትዮጵያ ሀገር መከላከያ ሚኒስቴር የኢንዶክትሬሽንና የሕዝብ ግንኙነት ማዕከል ኃላፊ ኮሎኔል ገብረ ኪዳን ገብረ ማርያም ለኢዜአ  እንደገለጹት ሠራዊቱ ማለዳ ላይ ባደረሰው ጥቃት በሦስት ካምፖች ተሰባስቦ  የነበረውን ኃይል ለማውደም ተችሏል። ኮሎኔሉ ዝርዝሩ ወደፊት ይፋ ይደረጋል ማለታቸውን የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዘገባ በወቅቱ ቢያመለክትም ይህ የጊዜ መስመር እስከተዘጋጀበት ሰዓት ድረስ ያገኘነው መረጃ የለም፡፡

የወልድባ ገዳም እና የስኳር ልማት ፕሮጀክት
በዋልድባ ገዳምና በወልቃይት ስኳር ልማት ፕሮጀክት መካከል  አለመግባባት ተፈጠረ፡፡የኢትዮጵያ ስኳር ልማት ኤጀንሲ ከያዛቸው የስኳር ማስፋፊያ  ፕሮጀክቶች አንዱ የሆነው የወልቃይት ስኳር ልማት ፕሮጀክት ግድብ ግማሽ ክፍል የገዳሙ ክልል ውስጥ መገንባቱ ፣ በገዳሙ ያረፉ ቅዱሳን አፅም መነሳቱ  ፣በገዳማውያኑ የሚተዳደሩ ሦስተ አቢያተ ክርስቲያናት መነሳታቸው ክርክሩን ያስነሱ ሲሆን ችግሩን ለመፍታት መነኮሳቱ አዲስ አበባ ድረስ ደርሰው  በጠቅላይ ቤተ ክህነት እና በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት የደረሰባቸው  አላግባብ ያለሆነ ማንጓጥና እንግልት ጉዳዩን የበለጠ አባብሶታል ተብሎዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ፕሮጀክቱ በኢትዮጵያ እና በሌላው አለም በሚገኙ ምእመናን አለም አቀፍ ተቃውሞሞ ደርሶበታል፡፡ መንግስት በአደባባይ ብዙ መግለጫዎችን በመስጠት ውይይቶች  ማካሄዱን ቢገልጹም በድብቅ ደግሞ መነኮሳቱን በማስፈራራት እና በማሰር እየታማ ጉዳዩ በእንጥልል እንደቆመ አለ፡፡

የዝቋላ ገዳም ቃጠሎ
ሊበን ዝቋላ ወረዳ አዱላላ ከተማ የሚገኘው የዝቋላ ደብረ ከዋክብት ጻድቁ አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ ገዳም በሚገኝበት ተራራ  ላይ በመጋቢት 8 ቀን 2004 ዓ.ም ቀትር  የተነሣው የእሳት ቃጠሎ ሁለት ጋሻ መሬት የሚሸፍን ደን  አወድሞ በቁጥጥር ስር ዋሎዋል ፡፡ በእሳት አጥፊ አውሮፕላን ወይም ሄሊኮፕተር በሚረጭ ኬሚካል በመንግስት በኩል አለመመደቡ መንግስትን ቢያሳማውም ከአዲስ አበባ እና ሌሎች የአከባቢው ከተሞች የሚገኙ ነዋሪዎችና የፌዴራል ፖሊስ አባላት ባደረጉት ከፍተኛ ርብርብ ቃጠሎው  በቁጥጥር ስር ውሏል፡፡
የአማራ ተወላጆች ከደቡብ ክልል ጉራ ፈርዳ መፈናቀል
1000 ያህል የአማራ ተወላጅ አባወራዎች ከደቡብ ክልል ቤንች ማጂ ዞን ጉራ ፈርዳ ወረዳ ተፈናቀሉ፡፡ አነዚህ አባወራዎች ከአማራ ክልል በተለያዩ የድርቅ ወቅቶች በሰፈራ ኑሮዋቸውን የመሰረቱ ሲሆኑ ለረጅም አመታት በቦታው መኖራቸውን ይናገራሉ፡፡ እነዚህ አባ ወራዎች መሬታቸውን ተቀምተው የተፈናቀሉ ሲሆን ወደ አዲስ አበባ በመምጣት በመላው ኢትዮጲያ አንድነት ድርጅት(መኢአድ) ጹ/ቤት ቅጥር ጊቢ ውስጥ ተጠልለው ነበር፡፡ በወቅቱ የአቶ ሽፈራው ሽጉጤ አስተዳደር ዜናውን ከእውነት የራቀ ሲል አስተያየት መስጠቱ ይታወሳል፡፡

የፕሬዚዳንት ግርማ ወልደ ጊዮርጊስ ያልተጣራ ዜና እረፍት
የኢ.ፌ.ድ.ሪ ፕሬዚዳንት ግርማ ወልደ ጊዮርጊስ በልብ ህመም ምክንያት ማረፋቸው የተገለጸው መጋቢት 4 2004 ዓ.ም. ነበር፡፡ መንግስት  እንደተለመደው ማስተባበያው በተገቢው ጊዜ አለማቅረቡ ወሬው እንዲዛመት አስተዋእጾ ያደረገ ሲሆን ብዙዎች የቀብሩ ቀን መች እንደሆነ በሚጠባበቁበት ሰዓት ኢዜአ ፕሬዚዳንቱ ለተለመደ የጤና ምርመራ በሳውዲ አረቢያ እንደሚገኙ በመግለጹ ወሬው ቀስ በቀስ ከሚዲያ ጠፍቷል፡፡


ሚያዝያ

የአለም ደቻሳ ጥቃትና ሞት
በሊባኖስ የኢትዮጲያ ቆንስላ ቢሮ በር ላይ በአሰሪዋ ስትደበደብ የታየችው አለም ደቻሳ ከጥቂት ቀናት በሁዋላ ራስዋን አጠፋች መባሉን ተከትሎ ኢትዮጲያውያንን በአለም አቀፍ ያስቆጣ ክስተት ነበር፡፡የአለምን ሞት ተከትሎ የተለያዩ አካላት አጋርነታቸውን የሚያሳይ የተለያዩ ዝግጅቶች በአለም አቀፍ ደረጃ የተካሄዱ ሲሆን ለቤተሰቦችዋም በገቢ ማስገኛ ፕሮግራሞች ድጋፍ ተደርጎላቸዋል፡፡ የአለም ሞት በወቅቱ ከአልጀዚራ ጀምሮ የተለያዩ ታለላቅ የአለም ሚዲያዎች ከፍተኛ ሽፋን ተሰጥቶት ነበር፡፡

እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ዜና እረፍት
እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ በጨጓራ አልሰር ምክንያት አዲስ አበባ በሚገኘው ካዲስኮ ጠቅላላ ሆስፒታል በህክምና ሲረዱ ቆይተው ሚያዝያ 02/2004 ዓ.ም ምሽት 2 ሰዓት 45 ደቂቃ ላይ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ በሀገራቸውና በአውሮፓ ለረጅም ዓመታት የሥነ ጥበብ ሙያን የተማሩ ሲሆን በሀገራቸውና በዓለም አቀፍ ደረጃም በተለያዩት ጊዜያት በርካታ የስዕል አውደ ርዕዮችን በማቅረብ ትልቅ አድናቆትንና ክብርን ለመጎናጸፍ ችለዋል። ሚያዝያ 6 ቀን 2004 ዓ.ም. የቀብራቸው ሥነ ሥርዓት በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እኩለ ቀን ተፈጽሟል፡፡

የቴዲ አፍሮ አራተኛ አልበም ተለቀቀ
ሚያዝያ 6 ቀን 2004 ዓ.ም ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) ጥቁር ሰው ሲል የሰየመውን አራተኛ አልበሙን ለቀቀ፡፡ በህዝብ ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት ካገኘው ሶስተኛው አልበሙ ቀጥሎ በተፈጠሩ ሁኔታዎች ድምጻዊው ለረጅም ጊዜ አዲስ ስራ አለማቅረቡ በከፍተኛ ጉጉት እንዲጠበቅ አድርገውታል፡፡ አልበሙ በስርጭት ብዛት እና በሽያጭ ገቢ ከፍተኛ ከሚባሉት የሙዚቃ ስራዎች መካከል መመደብ ችሏል፡፡ይሁንና አልበሙ ሙዚቀኛው በፊት ከነበረው የተሻለ ብቃት አለማሳየቱን ብዙዎች ቢገልጹም አልበሙ ተወዳጅነት አልቀነሰውም፡፡

ግንቦት

ጋዜጠኛ አበበ ገላው መለስ ዜናዊን በአደባባይ ነቀፈ
ግንቦት 10 ቀን 2004 ዓ.ም በቡድን ስምንት ሀገራት የመሪዎች ጉባዔ ላይ ጋዜጠኛ አበበ ገላው መለስ ዜናዊን በአደባባይ ነቀፈ ፡፡በአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ግብዣ መሰረት በምግብ እህል ራስን መቻል አስመልክቶ የሚደረግ ውይይት ላይ ለመሳተፍ ዋሽንግተን ዲሲ የተገኙት የቀድሞው ጠቅላይ ሚንስትር መለስ ዜናዊ በምግብ እህል እራስን መቻል አስመልክቶ በሚያደርጉት ንግግር  መሐል ላይ በስፍራው በነበረው ጋዜጠኛ አበበ ገላው የተቃውሞ ድምፅ ንግግራቸውን በድንጋጤ አቋረጡ፡፡ ጋዜጠኛ አበበ ገላው ‹‹መለስ ዜናዊ አምባገነን ነው፣ እስክንድር ነጋንና ሌሎችም የፖለቲካ እስረኞች ይፈቱ፣ መለስ ዜናዊ የሰብአዊ መብት ጥሰት ፈፅመዋል፣ ያለነፃነት ስለምግብ አታውሩ” ብሎ ሲናገር ተደምጧል፡፡ይህም ዜና በሀገር ውስጥ ሚዲያዎች(ከፍትህ ውጪ) ሽፋን ባያገኝም በማኀበራዊ መካነ ድሮች እና ሌሎች የዜና አውታሮች ዜናውን ተቀባብለውታል፡፡በተለይ የኢሳት ቴሌቪዥን ጉዳዩን የበለጠ ትኩረት መስጠት ጋዜጠኛ አበበ ገላውን በማናገር ፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሚዲያ ሽፋን መራቅ ጋር በማያያዝ ከፍተኛ የጤና መቃወስና የመንፈስ መረበሽ እንደደረሰባው ለማሳመን ጥረት አድርገዋል፡፡


ሰኔ

የሴቶች ቡድን ለአፍሪካ ዋንጫ አለፈ
የኢትዮጰያ የሴቶች እግር ኳስ ብሄራዊ ቡድንም ቅዳሜ ሰኔ 9/2004 የታንዛኒያ አቻውን 1 ለ 0 አሸንፎ ለአፍሪካ ዋንጫ አለፈ፡፡ይህን ተከትሎ ከተለያዩ አካላት ማበረታቻ ሽልማት ተበርክቶለታል፡፡በኢኳቶሪያል ጊኒ አስተናጋጅነት የሚከናወነው 8ኛው የአፍሪካ ሴቶች እግር ኳስ ዋንጫ ኢትዮጵያ ከካሜሩን፣ አይቮሪኮስትና ናይጄርያ ምድብ ተደለደላለች፡፡

የዶ/ር እሌኒ ገ/መድህን  የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ለቀቁ
ሰኔ 11 ቀን 2004 ዓ.ም የኢትዮጵያ ምርት ገበያ መስራች እና ዋና ስራ አስፈፃሚ የነበሩት ዶ/ር እሌኒ ገ/መድሕን ስራ አስፈፃሚነታቸውን በራሳቸው ፈቃድ እንደሚለቁ አስታወቁ፡፡ ስራቸውን የሚለቁት ምርት ገበያው ሲመሰረት ጀምሮ በታቀደው የመተካካት መርሕ መሰረት ሲሆን ስልጣናቸውን ቀደም ሲል የአቢሲኒያ ባንክ ምክትል ፕሬዚዳንት ለነበሩት አቶ አንተነህ አሰፋ እንደ ሚያስረክቡ ተናግረዋል፡፡
 እርሳቸው ገበያው ሲመሰረት ጀምሮ በታቀደው መተካካት መሰረት እንደለቀቁ ቢናገሩም በመንግስት በኩል ጫና እንደደረሰባቸውና ለሚዲያ ይፋ ያልሆኑ ከገንዘብ ጋር የተያያዙ ችግሮች መኖራቸውን የተለያዩ ሚዲያዎች ዘግበዋል፡፡

የቴሌኮም ማጭበርበር ሕጉ
የቴሌኮም ማጭበርበርን ለመከላከል በሚል ሽፋን መንግስት የተለያዩ የመገናኛ መንገዶችን ከልክለዋል ተብሎ የታማበት የቴሌኮም ማጭበርበር ረቂቅ አዋጅ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀረበ፡፡ በዚህ በመረጃ ደህንነት መረብ መስሪያ ቤት የተረቀቀው አዋጅ ዙሪያ ከፍተኛ የአለም አቀፍ የሚዲያዎች የተለያዩ ፕሮግራሞች የሰሩ ሲሆን እነደተለመደው የመንግስት ማስተባበያ በአቶ ሽመልስ ከማል በኩል ዘግይቶ ቀረበ ሲሆን ስካይፕ እና የንግድ ያልሆኑ ግንኙነቶችን ህጉ አይከለክልም ሲሉ አቶ ሽመልስ አብራሩ፡፡ነገር ግን ህጉ ያለምንም ጠንካራ ማሻሻያ በሃምሌ መጀመሪያ በተወካዮች ምክር ቤት በአስቸኩዋይ ጉባዔ ጸደቀ፡፡


ሐምሌ

በአሸባሪነት የተከሰሱት ተፈረደባቸው
ሐምሌ 6 ቀን 2004 ዓ.ም የከፍተኛው ፍርድ ቤት ሶስተኛ ወንጀል ችሎት አንዱአለም አራጌን፣ ዶ/ር ብርሀኑ ነጋን፣ አንዳርጋቸው ፅጌን እና ፋሲል የኔአለምን በእድሜ ልክ ፅኑ እስራት፤ እስክንድር ነጋን፣ ኦባንግ ሜቶን፣ ፀጋስላሴ ዘለቀን፣ ናትናኤል መኮንን እና ክንፈሚካኤል ደበበን በ18 አመት ፅኑ እስራት፣ ጋዜጠኛ አበበ ገላው እና አበበ በለውን በ15 አመት ፅኑ እስራት እንዲሁም የአዲስ ነገር ጋዜጣ መስራች እና ኤዲተር የነበሩት አብይ ተክለማሪያምን እና መስፍን ነጋሽን የ8 አመት ፅኑ እስራት ወስኖባቸዋል፡፡ የቅጣት ፍርዱ የተሰጠው ሰኔ 10 ቀን 2004 ዓ.ም የዋለው ችሎት ተከሳሾችን በተከሰሱበት የሽብርተኝነት እና ሽብርተኝነትን የማገዝ ወንጀል ጥፋተኛ ናቸው ብሎ መወሰኑን ተከትሎ ነው፡፡

መለስ የሌሉበት የአፍሪካ መሪዎች ጉባኤ ተካሄደ
ሐምሌ 7-8 ቀን 2004 ዓ.ም የአፍሪካ ህብረት 19ኛው መደበኛ የመሪዎች ጉባዔ በአዲስ አበባ ተካሄደ፡፡ ጉባዔው አዲስ አበባ ላይ እንዲካሄድ የተወሰነው እንድታዘጋጅ የተመረጠችው ማላዊ ጉባዔውን በሌላ ሀገር እንዲካሄድ ከጠየቀች በኃላ ነበር፡፡ በጉባዔው ላይ ኢትዮጵያ የተወከለችው በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ደሳለኝ ሲሆን ይህም ጠቀላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ከሪዮ 2012 የከባቢ አየር ውይይት ላይ ከሌላው ጊዜ ከስተው እና ጤና ያጡ መስለው ለመጨረሻ ጊዜ ከታዩ በኃላ እየጠነከረ የመጣውን ጠ/ሚኒስትሩ በጠና ታመዋል የሚለውን ወሬ ይበልጥ አጋጋለው፡፡ አቶ መለስ ዜናዊ የሽግግር መንግስት ፕሬዚደንት ሆነው ስልጣን ከያዙ አንስቶ የአፍሪካ መሪዎች ጉባዔ ላይ ሳይሳተፉ ሲቀሩ የመጀመሪያ ጊዜያቸው ነበር፡፡

የሙስሊሙ ማህበረሰብ ተወካዮች ታሰሩ
በከፍተኛ ብልጠት ለወራት ሳይቁዋረጥ የቀጠለው የሙስሊሞች ተቃውሞ ተወካዮቻቸው በመታሰራቸው ወደ ሌላ ምእራፍ ተሸጋገረ፡፡ያልተፈቀደ የሰደቃ ስነስርአት ማካሄድ አይቻልም የተባለውን የመመንግስትን ክልከላ ተከትሎ አወልያ ትምህርት ቤት ውስጥ በምሽት  በመንግስት ሃይሎች እና በሙስሊሞች መካከል ግጭት የተፈጠረ ሲሆን በተከታዩቹ ቀናት የሙስሊሙን ህብረተሰብን የሚወክለው ኮሚቴ አባላት ለእስር ተዳረጉ፡፡የኮሚቴው አባላት ክስ የጠመሰረተባቸው በሽብርተኝነት ሲሆን አራዳ ፍ/ቤት ቀርበው የጊዜ ቀጠሮ ተጠይቆባቸዋል፡፡

 ፍትህ ጋዜጣ ከዝውውር ውጪ ሆነች

በተለያዩ ጠንካራ ትችቶችን መንግስት ላይ በማቅረብ የምትታወቀው ፍትህ ጋዜጣ በፍትህ ሚ/ር ትእዛዝ የአንድ ሳምንት ከተቁዋረጠች በሁዋላ ብርሃን እና ሰላም ማተሚያ ቤት አላትምም በማለቱ ፍትህ ጋዜጣ ከዝውውር ውጪ ሆናለች፡፡ዋና አዘጋጅዋ ተመስገን ደሳለኝም ተከሶ ፍርድ ቤት ቀርቦ ለ1 ሳምንተ ያህል ከታሰረ በሁዋላ አቃቢ ህግ ባልታወቀ ምክንየት ተጨማሪ መረጃ ለመሰብሰብ ክሱን አቁዋርጦታል፡፡


ነሐሴ

የለንደን ኦሎምፒክ እና ኢትዮጵያውያን አትሌቶች
ከሐምሌ 20-ነሐሴ 6 ቀን 2004 ዓ.ም 30ኛው የኦሎምፒክ ውድድር በእንግሊዝዋ ዋና ከተማ  ተካሄደ፡፡የአትሌቲክሱ አንድ ዘርፍ በሆነው በሩጫ ብቻ ነበር፡፡ በዚህም 3 የወርቅ 1 የብርና 3 የነሐስ በጠቅላላው 7 ሜዳሌያዎችን ማግኘት ችላለች፡፡ የወርቅ ሜዳሌያዎቹን ያስገኙት በሴቶች በ10 ሺህ ሜትር ጥሩነሽ ዲባባ፣ በሴቶች ማራቶን ቲኪ ገላና እና በሴቶች 5 ሺህ ሜትር መሰረት ደፋር ናቸው፡፡ ብቸኛው የብር ሜዳሊያ ደግሞ በወንዶች 5 ሺህ ሜትር በደጀን ገ/መስቀል የተገኘ ነው፡፡ በወንዶች 10 ሺህ ሜትር ታሪኩ በቀለ፣ በሴቶች 10 ሺህ ሜትር ጥሩነሽ ዲባባ እና በሴቶች 3 ሺህ ሜትር መሰናከል ሶፊያ አሰፋ የነሐስ ሜዳሊያዎቹን ያመጡ አትሌቶች ናቸው፡፡ ከውድድሩ ጋር ተያይዞ የአንዳንድ አትሌቶች ብቃት መውረድ እና ከውድድሩ ተሳታፊዎች በላይ ቁጥር ያላቸው የልዑካን ቡደኑ አባላት ወደ ስፍራው ማምራታቸው ከፍተኛ ክርክርን አስነስተዋል፡፡

ብፁህ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ አረፉ

ነሐሴ 9 ቀን 2004 ዓ.ም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ-ክርስቲያን ፓትሪያርክ የነበሩት አቡነ ጳውሎስ ባደረባቸው ህመም አረፉ፡፡ ስርአተ ቀብራቸውም ነሐሴ 17 ቀን 2004 ዓ.ም በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ስላሴ ካቴድራል ተፈፀመ፡፡ ብፁህነታቸው የኢትዮጲያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ለመምራት ከተመረጡበት 1984 ዓ.ም ጀምሮ ለ20 አመታት በፓትሪያርክነት ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡


መለስ ዜናዊ አረፉ
ነሐሴ 15 ቀን 2004 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክሪያሲያዊ ሪፐብሊክ ጠቅላይ ሚንስትር አቶ መለስ ዜናዊ ነሐሴ 14 ቀን 2004 እኩለ ሌሊት 5፡40 ላይ መሞታቸውን የሚኒስትሮች ካቢኔ መግለፁን የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ይፋ አደረገ፡፡ የኢፌደሪ ጠቅላይ ሚኒስትር በመሆን ለአራተኛ የምርጫ ዘመን በማገልገል ላይ የነበሩት አቶ መለስ የሁለተኛ አመት የህክምና ትምህርታቸውን ካቋረጡበት ከ19 አመታቸው ጀምሮ ህይወታቸው በፖለቲካ ትግል እና ስልጣን የተሞላ ነበር፡፡ የአቶ መለስ ዜናዊ ብሔራዊ የቀብር ስነ-ስርዓት ብዛት ያላቸው አፍሪካውያን እና ሌሎች መሪዎች በተገኙበት ነሐሴ 27 ቀን 2004 በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል፡፡ አቶ መለስ የሁለት ሴት እና የአንድ ወንድ ልጅ አባት ነበሩ፡፡

No comments:

Post a Comment