Saturday, May 28, 2016

እኔ እና ዕድለቢሱ ትውልዴ


ሲራክ ተመስገን የ24 ዓመት ወጣት ሲሆን፤ በኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. ዘመን ተወልዶ ያደገ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር አንዳንዶቹ ‘The EPRDF Generation’ የሚሉት ትውልድ አባል ነው፡፡ ሲራክ ብቻ ሳይሆን ስልሳ አምስት በመቶው የኢትዮጵያ ሕዝብ ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. ሥልጣን ከያዘበት ጊዜ ወዲህ የተወለደ ሲሆን፤ ይሄም ከአገሪቱ አጠቃላይ ሕዝብ ሁለት ሦስተኛውን ይሸፍናል፡፡ ሲራክ በዚህ ዕድሜው “እኔና ትውልዴን ጠፍጥፎ የሠራን ኢሕአዴግ ተስፋ አስቆርጦኛል” ይለናል፡፡ ቁጭቱን አንብቡለት፡፡


ማንም ሰው ወዶ እና ፈቅዶ ‹በዚህ ጊዜና እዚህ ቦታ ልወለድ› ብሎ አልተወለደም። እኔም ቀን
ሲጎልብኝ የኢትዮጵያ ሕዝብ አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ.) ከበረሃ ተነስቶ ምኒልክ ቤተ መንግሥት ሲደርስ፣ በዚህች ምስኪን ድሃ አገር ተወለድኩ። እንደ መሰሎቼ ሁሉ የእኔን የፖለቲካ ማንነትም በአብዮታዊ ዴሞክራሲ ርዕዮተዓለማዊ ቅኝት በተቃኘች አገር ኢሕአዴግ ጠፍጥፎ ሠራው። የኢሕአዴግ ኢትዮጵያም፣ እኛም የግንቦት 20 ፍሬዎች ቀስ እያልን ማደግ ጀመረን። ዕድሜያችንም፣ ዕድልም 1997 አገራዊ ምርጫ ላይ አደረሰን። የተለያዩ የፖለቲካ ሐሳብ ያላቸው ቡድኖች መሐከል የሚካሄድ የአደባባይ የፖለቲካ ውይይት ለመጀመሪያ ጊዜ ለማዳመጥ ታደልን። እዚህ ላይ ነው እኔና የትውልዴ አባላት ነቃ ብለን ኢሕአዴግን በቆሪጥ ማየት የጀመርነው።

ኢሕአዴግ ልጆቹን እንዴት አሳደገን?

እኛ የኢሕአዴግ ልጆች ሁለት ተቃራኒ የማንነት ጥያቄዎች ከግራ እና ከቀኝ እየጎተቱን ነው ያደግነው። የአካባቢያዊ (የዘውግ) ማንነት እና አገራዊ (የዜግነት) ማንነት። አሳዳጊያችን ኢሕአዴግ መሠረቱን ያደረገው ፈግሞ በዚህ አካባቢያዊ ማንነት ላይ ነው። ገና በጨቅላ ዕድሜያችን አገራዊ ማንነነትን አፍሮሶ በአካባቢያዊ ማንነት የሚተኩ ንግግሮችን ከኢሕአዴግ አመራሮች አንደበት እየሰማን ነው ያደግነው። በእኔ እምነት እንሰማቸው የነበሩት እንደ “የአክሱም ሐውልት ለወላይታ ምኑ ነው?”፣ “ባንዲራ ጨርቅ ነው”፣ “የኢትዮጵያ ታሪክ የ100 ዓመት ታሪክ ነው”… የመሳሰሉት ንግግሮች አገራዊ ማንነትን በመተው አካባቢያዊ ማንነትን እንድንይዝ መሠረቱ ጥሏል ብየ አስባለሁ።

ካለፉ የታሪክ ኹነቶች ውስጥ አንድ ሊያደርጉን የሚችሉ ትርክቶችን ወደ ጎን በመግፋት፣ ሕዝቦችን ቅራኔ ውስጥ የሚከቱ ትርክቶች ብቻ ተመርጠው እየተመገብን ነው ያደግነው። ያለበሱን አገራዊ ማንነትን ሳይሆን አካባቢያዊ ማንነት ነው፡፡ ለዚህም ይመስለኛል አሁን ላይ የካቲት ሃያ ሦስትን የማያውቁ፣ ሕዳር ሃያ ዘጠኝን በሽር ጉድ የሚያከብሩ የትውልድ አጋሮቼ የበረከቱት፡፡

የትውልዳችን ፈተና

(ለመግባባት እንዲያመቸን ትውልዳችን ስል ኢሕአዴግ አዲስ አበባ በደረሰበት ዓመት እና በቀጣዩ ዓመት የተወለዱ ልጆችን ማለቴ እንደሆነ ይታወቅልኝ።)

የእኔ ትውልድ ብዙ ፈተናዎች አሉበት። እስኪ ዘርዘር አድርገን ለማየት እንሞክር።

ሀ. ‘ጸጥ-ለጥ’ ብሎ የተገዛው ትውልዴ

ሐሳብን የመግለጽ ነጻነት ኢሕአዴግ ባወጣው ሕገ መንግሥት ላይ ቢካተትም በሀገራችን ላይ በተጨባጭ የምናየው ግን ሐሳብን በነጻነት መግለጽ ከፍተኛ አደጋ ያለው እንደሆነ ነው፡፡ ብዙዎች ሐሳባቸውን በነጻነት በመግለጻቸው ተደብድበዋል፣ ተገድለዋል፣ ታስረዋል፣ ተሰደዋል። በአገራችንም ጠንካራ ‘ሚዲያ’ እንዳይፈጠር ቀን ከሌ’ት ገዢው ፓርቲ ትልቅ እንቅፋት ሆኗል።

ይህ የእኔ ትውልድ ከመንግሥት ጋር እንዲህ ዓይነት ቅራኔዎች ውስጥ አለመግባቱ የኢሕአዴግ ልጆች ‘ጸጥ-ለጥ’ ብለው እየተገዙ መሆኑን ያሳያል። ዘመናዊው ‘የማኅበራዊ ሚዲያ’ ላይ በጣም ጥቂቶች ሊባሉ የሚችሉ ግለሰቦች ፈራ-ተባ እያሉ መንግሥትን ሲተቹ ይታያሉ። ‘ጸጥ-ለጥ’ ብሎ የመገዛቱን ነገር የከፋ የሚያደርገው በእኔና ከእኔ ዕድሜ በታች ያሉ ሴቶች በአደባባይ መንግሥትን ሲተቹ አለማየት ነው።

ለ. ዕድለቢሱ ትውልዴ

ሌላው የእኔ ትውልድ ፈተና ዕድሎችን ማግኘት የሚችለው በብቃቱ ሳይሆን ለገዢው ፓርቲ ባለው ታማኝነት ወይም የገዢው ፖርቲ አካባቢ ተወላጅ ከሆነ ነው። ከ2005 ጀምሮ በመቶ ሺሕዎች የሚቆጠሩ የትውልድ አቻዎቼ ከተለያዩ ዩንቨርስቲዎች በየዓመቱ እየተመረቁ ነው። እኒህ ተመራቂ ተማሪዎች ትልቁ ፈተናቸው ሥራ ማግኘት ላይ ነው። ከመመረቂያ ሰርተፍኬታቸው ይልቅ ኢሕአዴግን ከመሠረቱት ከአራት ድርጅቶች የአንዱን በደም የሚመሳለውን መርጦ የአባልነት መታወቂያ ይዞ መገኘት የሥራ ዋስትና ነው። ኢሕአዴግን እየተቃወሙ የመንግሥት ሥራ የማግኘት ዕድል ያላቸው በጣም ጥቂቶች ናቸው። በተለያዩ የአመራርነት ቦታዎች መቀመጥ የማይታሰብ ነው። ከቀበሌ ካቢኔ አንስቶ እስከ ሚኒስትር ድረስ በኢሕአዴጋዊያን የተሞላ ነው። ባንድ ወቅት ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር አንድን ሰው በአመራርነት ቦታ ለማስቀመጥ ብቃት ሳይሆን ለፓርቲው ያለውን ታማኝነት እንደሚመርጡ በአደባባይ ተናግረዋል። ይህ ትውልድ ሥራ ሊያገኝ የሚችለው ወይ አመራር ሊሆን የሚችለው በብቃቱ ሳይሆን ለገዢው ፓርቲ ባለው ታማኝነት አለበለዚያ የዘር ሐረጉ ከገዢው ፓርቲ የሚመዘዝ ከሆነ ነው።

ኢሕአዴግ ዲሞክራሲን ሊያመጣ ይችላል?

በእኔ ትውልድ ዘመን የዴሞክራሲ ጭላንጭል ተስፋ በ1997 አገራዊ ምርጫ ወቅት ታይቶ ነበረ። መጨረሻው ጋዜጠኞችን፣ አራማጆችን፣ ፖለቲከኞችን… እስር ቤት በማጎር ቢዳፈንም። ከ’97 በኋላ የወጡትን የተለያዩ ሕጎች ብናይ ዴሞክራሲን የሚያቀጭጩ እንጂ የሚያፋፉ አይደሉም። መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች እና የሙያ ማኅበራትን በሚመለከት የወጣው አዋጅ፣ የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ፣ አሁን በረቂቅ ላይ ያለው የኮምፒውተር ወንጀል አዋጅ… እነዚህ አዋጆች የዴሞክራሲ መሠረት የሆኑትን የመደራጀት መብት፣ ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብትን ይደፈጥጣሉ። እነዚህን ሁኔታዎች ስናይ ኢሕአዴግ ምን ያህል በሩን ለዴሞክራሲ እንደዘጋ እንገነዘባለን። ከዚህም ተነስቼ የእኔ ትውልድም በዕድሜው ሌላ መንግሥት የማየት ዕድሉ ጠባብ ይመስለኛል። በትውልዴ መንግሥት ሲቀየር አለማየቴ ያበሳጫኛል - ያስቆጨኛል።

No comments:

Post a Comment