Tuesday, June 2, 2015

ፍርድ ቤቱ በአቤል ዋበላ ላይ የ4 ወር የእስር ቅጣት በ2 አመት ገደብ ወሰነ

በእነ ሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ 7ኛ ተከሳሽ የሆነው ጦማሪ አቤል ዋበላ ዛሬ ግንቦት 25/2007 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ብቻውን ቀርቧል፡፡ አቤል ግንቦት 19/2007 ዓ.ም የዞን ዘጠኝ ጦማርያንና ወዳጅ ጋዜጠኞች በነበራቸው የፍርድ ቤት ውሎ ወቅት ‹‹ችሎት ደፍረሃል›› በሚል ጥፋተኛ ያደረገው ፍርድ ቤቱ ዛሬ የቅጣት ውሳኔ አሳልፏል፡፡

በዚህ መሰረት ፍርድ ቤቱ በአቤል ላይ የ4 ወር የእስር ቅጣት የበየነ ሲሆን፣ አቤል ድርጊቱን የፈጸመው በስሜታዊነት መሆኑን በመገንዘብ ቅጣቱ በ2 አመት ገደብ እንዲወሰን በማድረግ ማቅለሉን ፍርድ ቤቱ በብይኑ ላይ አመልክቷል፡፡ ጦማሪ አቤል ባለፈው የፍርድ ቤት ውሎ ወቅት ጥያቄ ለማንሳት እድል እንዲሰጠው ሲጠይቅ ‹‹ስነ-ስርዓት አድርግ!›› በሚል ኃይለ ቃል ፍርድ ቤቱ ሲናገረውና ሀሳቡን እንዳይገልጽ ሲገድበው፣ ዳኞችን ‹‹እናንተ ራሳችሁ ስነ-ስርዓት አድርጉ!›› በማለቱ ችሎት ደፍረሃል መባሉ ይታወሳል፡፡

ሌሎች የዞን ዘጠኝ ጦማርያንና ወዳጅ ጋዜጠኞች ፍርድ ቤት ውስጥ በአቤል ላይ የጥፋተኛነት ውሳኔ የሚሰጥ ከሆነ የእሱ ሃሳብ እኛንም የሚመለከት ስለሆነ ቅጣቱን አብረን እንቀበላለን፤ ስለሆነም በቅጣት ውሳኔው ዕለት እኛም ፍርድ ቤት እንድንቀርብ ይታዘዝልን ብለው የነበር ቢሆንም በዛሬው የፍርድ ቤት ውሎ ሳያቀርቧቸው ቀርተዋል፡፡ አቤል ከጓደኞቹ ተለይቶ ለመጀመሪያ ጊዜ ብቻውን ችሎት ፊት የቀረበ ሲሆን፣ ፍጹም ልበ-ሙሉነትና ዘና ያለ ስሜት ታይቶበታል፡፡

ጦማሪ አቤል በቅጣት ውሳኔው ላይ ምንም ሀሳብ አልሰጠም፡፡ ፍርድ ቤቱ ግን ‹‹እስካሁን እንደነበረው አካሄድ ከስሜታዊነት በወጣ መልኩ ወደፊት ችሎቱን ተከታተል›› የሚል ‹ምክረ ሀሳብ› አቅርቦለታል፡፡

ችሎቱን የአቤል ቤተሰቦች፣ ወዳጆቹ፣ ጋዜጠኞችና ከአሜሪካና ጀርመን ኤምባሲዎች የመጡ ተወካዮች ተከታትለውታል፡፡ የዞን ዘጠኝ ጦማርያንና ሶስቱ ወዳጅ ጋዜጠኞች በቀጣይ ሰኔ 8/2007 ዓ.ም ለ30ኛ ጊዜ ፍርድ ቤት ሲቀርቡ በአንደኛ ተከሳሽ ሶልያና ሽመልስ ላይ አቃቤ ህግ አቅርቤዋለሁ ባለው የዶክሜንተሪ ማስረጃ ላይ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ ያሳልፋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በተያያዘ ዜና ምክንያቱ በግልጽ ባልታወቀ ሁኔታ በቅሊንጦ ታስረው በሚገኙ የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ዞን ላይ ለውጥ የተደረገ ሲሆን ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ እና ጦማሪ ናትናኤል ፈለቀ ወደ ተለያዬ ዞኖች ተዘዋውረዋል፡፡

በዚህም መሰረት
በዞን1 ጦማሪ ዘላለም ክብረት ፣ ጦማሪ አቤል ዋበላ እና ጦማሪ ናትናኤል ፈለቀ
በዞን2 ጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ ፣ ጦማሪ አጥናፍ ብርሃኔ እና ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ
በዞን3 ጋዜጠኛ አስማማው ሃይለጊዮርጊስ ይገኛሉ ፡፡

ስለሚያገባን እንጦምራለን !
ዞን9

No comments:

Post a Comment