Sunday, October 7, 2012

ጋዜጦችና መጽሔቶቻችን ባሳለፍነው ሳምንት




መሰናዘሪያ ጋዜጣ በማክሰኞ፣ መስከረም 22 እትሙ፡-
ስለ የኢትዮጵያ ዲስፖራና  ፖለቲካ ተጽዕኖው፣ የመሪነት ሚናና የብሔረሰቡ ስነ ልቦና፣ በአሥር ዓመት 15 ቢሊዮን ዶላር ስለመዘረፉ፣ ከብልሀቱ ፍርሃቱ ያዘነበለው የአጃቢዎች ጋጋታ፣ የእኔነት ስሜት ይሰማን በሚል ርዕስ የቀረበው ርዕሰ አንቀጽ እና ሌላም ሌላም ጽፏል፡፡

ሰንደቅ በረቡዕ፣ መስከረም 23 እትሙ፡-
ንግድ ባንክ ለ40/60 ቤቶች ግንባታ ብድር ለመፍቀድ ሥራውን ማጠናቀቁን እንደገለጸ፣ 800ሚሊዮን ዶላር የሚፈጀው ግዙፉ የጦሳ ብረታ ብረት ፋብሪካ የግንባታ ስምምነት እንደተፈረመ፣ ስለኦህዴድ የሰላ መደባዊ ትግል፣  ሞሳድ የኢትዮጵያን አውሮፕላን ማጋየት ለምን እንደፈለገ ዊኪሊክስን አጣቅሶ ሰፋ ያለ ማብራሪያ ይዞ ወጥቷል፡፡ በርዕሰ አንቀጹ ‹‹ፓርላማው ጠንካራ የክርክር መድረክ እንዲሆን ከአባላቱ ብዙ ይጠበቃል፡፡›› ይላል ስለኛ ፓርላማ መሆኑ ነው፡፡  በተጨማሪም መጅሊስ ምርጫው ያለስምምነት እንደቀጠለ ነው፣ ኢቢኤስ ቴሌቪዥን ወደ ስርጭቱ ለመመለስ የተመልካች እርዳታ ጠየቀ፣ በሰንደቅ ቃለመጠይቅ ‹‹የፖለቲካ ለውጥ ይመጣል ብዬ የማስበው ከተቃዋሚ ሳይሆን በኢሕዴግ ውስጥ ነው›› ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ በርሄ  


በጤና አምዱ ‹‹የአንጀት ካንሰር ወጣቶችን ሳይቀር ማጥቃት ጀምሯል›› ዶ/ር ዳንኤል ዘመንፈስ
‹‹ሐሳብን በነጻ በመግለጽ ነፃነት ስም እየተደፈረ ያለው የእስልምና ሃይማኖት፣
አለሙ ታዬ ‹‹የአስተሳሰብ ምጥቀት ወይም ትልቅነት በምን ይለካል›› ይለናል
ባለራዕይ የወጣቶች ማኅበር በኢህአዴግ ካድሬዎች አሁንም እየተቸገርኩኝ ነው አለ እና ሌሎችም

ሪፖርተር
ጠቅላይ ሚኒስቴር ኃይለማርያም ምን አሉ በሚል ርዕስ ከቪኦኤው ፒተር ሃይንላይን ጋር ያደረጉትን ቃለመጠይቅ አስፍሯል ፒተር ኢትዮጵያ በነበረበት ወቅት የሙስሊሞችን ተቃውሞ ሲዘግብ በመንግስት ኃይሎች ከአስተርጓሚው ጋር ታስሮ እንደነበር የሚዘነጋ አይደለም፡፡ ሰውዬው ገና መውጣታቸው ቢሆንም እስከመቼ ነው ስለራሳችን ከውጪ የምንቃርመው መቼ ነው ፈታ ብለን የፈለግነውን ጥያቄ የምንጠይቃቸው፡፡

‹‹ነጋዴዎች ስንባል ቀጣፊዎች ነን››፣ ‹‹መንግስት ዓይኑን ቢጨፍንልን ጥሩ ነው››፣ ‹‹መንግስት የንግዱን ነገር ለኛ ይተውልን›› ሼክ አል አሙዲ ለመንግስት ባለስልጣናት  ተፎካካሪ የሌላቸው የተረከቡትን መሬትን እንኳ አልምተው ያልጨረሱ ወይም ለቁጥር ያዳገቷቸው ባለኃብት ግለሒስ ከቀልድ ጋር አዋዝተው አቅርበዋል፡፡

የሪፖርተር ጋዜጣ የመሸጫ ዋጋ ከ 7ብር ወደ 10ብር ዛሬ (እሁድ፣መስከረም 27/2005) ገብቷል፡፡
‹‹የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከመመሪያው ውጪ ብድር የሰጣቸው አሉ›› የሚል ዋና ርዕስ በእሁድ ዜናው አስነብቧል፡፡

‹‹ተቃዋሚ ድርጅቶች ለኢትዮጵያ ሕዝብ የብቃት ማረጋገጫ ሊያሳየው ይገባል›› የሪፖርተር  የረቡዕ ርዕሰ አንቀጽ ነው፤ ጥፋቱን ሁሉ ለተቃዋሚ ያሸከመው ሪፖርተር (አማረ) ኢሕአዴግ ብቃት አለው ብሎ ይሆን፡፡

‹‹ስኳር ኮርፖሬሽን የፓኪስታኑን ፋብሪካ ከነባንክ እዳው ገዛ›› አንዲህ ነው ‹በእቅድ› መመራት!
 አቶ ጌታቸው በላይ አልተመለሱም፡፡

‹‹ከስህተቶቻችን ካልተማርን የኢትዮጵያ ዴሚክራሲያዊ ሽግግር አሁንም ሊመልጠን ይችላል›› ሰዬ አብርሃ

የሕዝብ ተራንስፖርት እጥረት ብሶበታል፤ ባለስልጣኑ ችግሩን ለመፍታት አማራጮችን እዘጋጀ መሆኑ ተጠቆመ፡፡ እና ሌሎችም፣

ሐሙስ መስከረም 24 የኛ ፕሬስ
ጠ/ሚ ኃይለማርያም ለመጀመሪያ ጊዜ ተቃውሞ አስተናገዱ በኒውዮርክ የነፃነት ቀንን ለማክበር ወጥተው የነበሩት ሰልፈኞች ጠ/ሚሩ ከቪኦኤው ፒተር ጋር ባደረጉት ቃለመጠይቅ ተበሳጭተው ሰልፉን ወደ ተቃውሞ እንደቀየሩት ጋዜጣው ዘግቧል፣ በርዕሰ አንቀፁ ‹‹መንግስት ለጥቅም ሽሚያ መቀነቱን ያጥብቅ›› በማለት አሳስቧል፣ የመድረክ አመራሮች በአትላንታ ስብሰባ አደረጉ፣ አዲሱ የግብፅ መንግስት ‹‹በአባይ ላይ ያለውን ፖሊሲ ወደፊት የምናየው ነው አለ››፣ አስመራ የሄዱት አቡነ መርቆርዮስ በኢሳያስ አፈወርቂ ተባረሩ›› ጋዜጣው ትግራይ ኦንላይንን ጠቅሶ እንደዘገበው፣ ሳዑዲ አረቢያ ኢትዮጵያውያንን ከሐጂ ኡምራ ጉዞ አገደች ሳዑዲም መጅሊሱን እውቅና ነሳችው ማለት ነው፣ ‹‹የእሬቻ በዓል ባእድ አምልኮ አይደለም›› የተከበሩ አቶ መሃመድ አህመድ ‹‹የጸሎት ስፍራችንን መንግስት ያስከብርልን›› አያንቱ ሄኖክ አየለ፣ ‹‹ቴሌ የሞባይል ሂሳባችንን እየሞጨለፈ ተቸግረናል›› ተጠቃሚዎች ‹‹ችግሩ እንዳለ እናምናለን›› ኤጀንሲው ግብር ከፋይ ዘራፊ መሆኑ ነው እንግዲህ፣ ‹‹ባለቤቴ ከዚህ በፊት ቀዳማይ እመቤት እንድትሆን ተጠይቃ እምቢ ብላለች›› ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ቀዳማዊ እመቤት መሆን የሚገባት ማን ነች ብለው ይጠይቃሉ ኢ/ር ዘለቀ ረዲ በፖለቲካ አምድ ስር፡፡

ሕገ-ወጥ በሆነ መንገድ ከገበያ እንዲወጣ ተገዶ የነበረው የፍትሕ ጋዜጣ በአዲስ ታይምስ ጋዜጣ በኩል መምጣቱ በሳምንቱ ከገጠሙን መልካም ዜናዎች ውስጥ አንዱ ነው፡፡

አዲስ ታይምስ ከፕ/ር ጌታቸው ኃይሌ ይድረስ ለሕወሓት በሚል ጽፈዋል፣ ‹‹የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ መንግስት›› በሚል ርዕስ ያሬድ ጥበቡ፣ ‹‹አማርኛ ካሳ እንዲከፍል አይገደድም›› በአሰፋ እንደሻው (ዶ/ር)፣ ‹‹ከመለስ በኋላስ 2›› በተመስገን ደሳለኝ… እንዲሁም ‹‹ቃሊቲን በጨረፍታ››፣

‹‹የሃይማኖት ነጻነትና መቻቻል›› በሚል ርዕስ ፕ/ር መስፍን ወልደማርማያም በጻፉት ላይ ስለ ሕገ-መንግስቱ አንቀጽ 27/1 አንስተው ‹‹ማንኛውምሰው የማሰብ፤ የሕሊናና የሃይማኖት ነፃነት አለው፣ ይህ መብት ማንኛውም ሰው የመረጠውን ሃይማኖት ወይም እምነት የመያዝ ወይም የመቀበል፣ ሃይማኖቱንና እምነቱን ለብቻ፣ ወይም ከሌሎች ጋር በመሆን በይፋ ወይም በግል የማምለክ፣ የመከተል፣ የመተግበር፣ የማስተማር፣ ወይም የመግለጽ መብትን ያካትታል›› በሚል መንደርደሪያ ስለ ሐሳብን በነፃነት መግለጽ መብት አጭር ምልከታ አድርገዋል ኃይማኖትም ቢሆን ከትችት እንደማያመልጥና ተከታዮቹን ሳንነካ ልንተች እንደምንችል አስረድተዋል፡፡ ተከታዮቹ ቢከፉም ያ ሰው ግን የራሱን ሐሳብ ወይም እውነት በመግለፁ የማንንም መብት እንዳልጣሰ ይገልጻሉ፤ ሐሳብን የመግለጽ መብት ጨዋነትን አይደመስስም መቻቻል ሰውን እንዳይናገር መገደብ አይደለም በማለት ከላይ የጠቀሱትን አንቀጽ ደጋግመን እንድናየው ይገፋፋሉ፤ ሲያጠቃልሉም፤ ‹‹ሐሳብን የሚፈራ ማኅበረሰብ እንደረጋ ውኃ ባለበት ይቀራል፤ የሚያድሰው መንገድ ሁሉ ስለተዘጋ አይታደስም፤ ከራሱ የሚተርፈውም አይኖረውምና ለማንም አይበጅም፡፡›› ይላሉ፡፡ ሙሉ ጽሁፉን ከመጽሄቱ ያንብቡ፡፡

የፍትሕ ዓምደኛው እንዳለ ጌታ ‹‹አንዳንድ የኢትዮጵያ ሕዝብ በአንዳንድ ከያኒ ስመስለው…›› በሚል ርዕስ ስለ አርቲስቶቻችን ልካቸውን ይነግርልናል፡፡ አርቲስቶቻችንን በራሱ ለዛ ባለው አቀራረብ መልሱ አልተሰጠም እንዳይከሰት ተጠንቅቆ በአምስት የከፈለልን እንዳለ ጌታ እንዲህ ይከፋፍላቸዋል ይርጋ ዱባለ፣ ሰለሞን ተካልኝ፣ እና ቴዎድሮስ ካሳሁን ሲሆኑ ሁለቱ ደግሞ የሥነ ጽሁፍ ሰዎች የሆኑት ወልደጊዮርጊስ ወልደ ዮሓንስና ተመስገን ገብሬ ናቸው፡፡ ባለስልጣናትና ምሁራን እንዲሁም ሸላሚዎቼና አጉራሾቼ ተገድለውብኝ ዘፈኔን ደርግ መፎከሪያ ሲያደርግብኝ እነሱን የገደለ እኔንም አይምርም ብዬ ዝም አልኩ የሚሉት አርቲስቱ 10ዓመት ሙሉ አብዮት አብዮት ወደፊት እያሉ አገር ሲያካልሉ ነበር ከደርግ ጋር በመሆን በመጨረሻም ለመሰደድ ያበቃቸው የእህታቸው ልጅ መገደል ነው፡፡ እንዳለ እንደሚለው አርቲስቶቻችን ችግሩ የሚታወቃቸው በራሳቸው ሲደርስ ብቻ ነው፡፡ ሙሉውን ከመጽሔቱ ምን ዋጋ አለው እንቶ ፈንቶ የለመዱት አርቲስቶቻችን ቁምነገር የሚጻፍበት መጽሄት ማንበብ አይቀናቸውም የቻላችሁ ግን አስነብቧቸው፡፡

ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌም ‹‹ይድረስ ለሕወሓት ድርጅት›› ተተኪዎቹ ስህተት እንዳይደግሙ መልካሙን አጋጣሚ እንዲጠቀሙ አሳስበዋል፡፡

No comments:

Post a Comment