Thursday, June 28, 2012

የኢትዮጵያ ጦማሮች ምን ጻፉ?

አጥናፉ ብ

ሰሞኑን በኢንተርኔት ተጠቃሚ ዘንድ እያወዛገበ ያለው የቴሌኮም አዋጅ አቶ ሽመልስ ከማል በቴሌቭዥን መስኮት ብቅ ብለው ስካይፒን መጠቀም ይቻላል ካሉ በሗላ ጋብ ብሎ ቢቆይም አቶ በረከት ሰጡት በተባለው መግለጫ ደግሞ ስካይፒን እንዘጋለን ወይም “ስካይፕም ሆነ ሌሎች የቴሌን ገቢ የሚቀንሱ እና ለደህንነት ስጋት የሚሆኑ የኢንተርኔት አገልግሎቶችን እንዘጋለን” የሚል ግራ የሚያጋባ ንግግር በትነዋል፡፡

Sunday, June 24, 2012

ጋዜጣ እና መጽሄቶቻችን ከሰኞ እስከ ሰኞ - ሦስት

(ከሰኔ 11 እስከ ሰኔ 17፤ 2004)

የተመሰረተበትን አንደኛ ዓመት በልዩ ዝግጅት ለማክበር ደፋ ቀና እያለ ያለው ፍኖተ ነፃነት ጋዜጣ አንድነት ለፍትሕና ለዴሞክራሲ በዓይነቱ የተለየ ‹‹የንድፈ ሐሳብና የፖሊሲ ትንተና መጽሄት›› ሊያሳትም እንደሆነ የሚነግር ዜና ይዞ ወጥቷል፡፡ ‹‹.. በዓይነቱ የተለየ የንድፈ ሐሳብና የአማራጭ ትንተና የሚቀርብበት መጽሄት ለማሳተም ዝግጅት መጨረሱን አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ ለዝግጅት ክፍላችን አስታወቀ፡፡ ‹ዳንዲ› የሚል ስያሜ የተሰጣት መጽሄቷ ሙሉ ለሙሉ የንድፈ ሐሳቦችና አማራጭ የፖሊሲ መነሻ የሚሆኑ ሐሳቦች የሚተነተኑባት መሆኗ ተነግሯል፡፡

* * *


‹‹የመንግስት ገንዘብ ለሚያባክኑ መ/ቤቶች ከፍተኛ በጀት ተመደበ›› ያለው ደግሞ የኛ ፕሬስ ጋዜጣ ነው፡፡ ‹‹ከፍተኛ የመንግስት ገንዘብ ባለማወራረድ ዋና ኦዲተር ለመሰከረባቸው መስሪያ ቤቶች ከበፊቱ የበለጠ ከፍተኛ በጀት እንደተመደበላቸው ተጠቆመ፡፡›› ካለ በኋላ ባለፈው ዓመት 1.2 ቢሊዮን ብር ያባከኑትን መ/ቤቶች ሲዘረዝር ‹‹… መከላከያ ሚኒስቴር፣ የግብርና ቴክኒክና ሙያ ስልጠና፣ የመቀሌ ዩንቨርሲቲ፣ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ፣ የመቀሌ ጤና ሳይንስ፣ የአይደር ሪፈራል ሆስፒታል፣ የትምህርት ሚኒስቴር፣ ጎንደር ዩኒቨርሲቲ፣ የኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የመንግስትን ገንዘብ ያለበቂ ማስረጃ ወጪ በማድረግና ሳያወራርዱ በመቅረት በዋና ኦዲተር ጥቁር መዝገብ ውስጥ እንደገቡ አረጋግጧል፡፡›› በተመሳሳይ ዜና ፍኖተ ነፃነትም የመጪው ዓመትን በጀት ‹‹ለአፈና የሚውል በጀት›› ሲል ወርፎታል፡፡

* * *


‹‹የየመኑ ፕሬዘዳንት ሳላህ አዲስ አበባ መሽገዋል?›› የሚል መካከለኛ ሐተታ ይዞ የወጣው መሰናዘሪያ ‹‹…የብዙዎች ግምት ሳላህ ከእይታ የተሰወሩት ለደህንነታቸው በተፈጠረው ስጋት ሳይሆን ቀደም ሲል ስልጣን ላይ እያሉ ለሕዝባቸው እኔ በፊት በየቀኑ ጫት እቅም ነበር፡፡ አሁን የምቅመው በሳምንት አንድ ጊዜ ነው ስለዚህ እናንተም የእኔን አርአያ ተከተሉ በማለት ያስተላለፉትን መልዕክት መነሻ በማድረግ በኢትዮጵያ መሽገው ሱሳቸውን እያወራረዱ ነው ወይም ከሕዝብ በዘረፉት ገንዘብ አዲስ አበባ እየተመላለሱ ሱሳቸውና ፍላጎታቸውን እያጣጠሙ እንደሆነ የሚገልፅ ነው፡፡…››

* * *


ሪፖርተር ጋዜጣ ‹‹ዳኞች የፍርድ ቤት ተገልጋዮን በቁጣ ማሸማቀቃቸው ጥያቄ አስነሳ›› የሚል ዜና በረቡዕ ዕትሙ የፊት ገጽ ላይ ይዞ ወጥቷል፡፡ በዝርዝሩም ‹‹…በፌዴራል ፍርድ ቤቶች የተለያዩ የክስ ሒደቶችን የሚያስችሉ ዳኞች በተገልጋዮ ላይ በሚያደርሱት ቁጣ፣ ተገልጋዮቹ በችሎቱ የተገኙበትን ጉዳይ ሳያስረዱ ተሸማቅቀው እንደሚመለሱ ተገለጸ፡፡..›› እያለ ይቀጥላል፡፡ ይህ የተገለጸው ከሕዝብ በቀረቡ ጥያቄዎች እንደሆነ በዜናው ላይ ተገልጧል፡፡

* * *


ሰንደቅ ጋዜጣ ‹‹ተማሪዎችን በውጤት ያንበሸበሸው የአ.አ.ዩ. ባልደረባ ቅጣቱን እየጠበቀ ነው›› ሲል ዘግቧል፡፡ ‹‹በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሕግ እና የስነ-ትምህርት ፋኩሊቲዎች ውስጥ የተማሪዎች ሪከርድና ማኅደር ክፍል ሰራተኛ ሆኖ የ18 ተማሪዎችን ውጤት ከዲፓርትመንቱ መምህራኖች በመቀበል አሻሽሎ ወደሬጅስትራር አስተላልፏል ሲል የፌዴራሉ የሥነ-ምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚስን ዐቃቤ ሕግ ክስ የመሰረተበት አቶ ሰለሞን ኩምሳ….. የሰውም ሆነ የሠነድ መከላከያ ማስረጃ የለኝም በማለቱ የፍርድ ውሳኔ ለመስጠት.. ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቶታል፡፡››

* * *


ተመስገን ደሳለኝ ፍትህ ጋዜጣ ላይ ‹‹ፍትህን እና አልሻባብን ምን አገናኛቸው?›› ባለው መጣጥፉ ላይ ካልታወቀ እራሱን የአልሻባብ ወኪል ብሎ ከፍትህ ጋዜጣ ጋር ውል እንደነበረው ለማስመሰል በፍትህ ኢሜይል መልዕክት ስለላከ ሰው ጽፏል፡፡ ‹‹… እንደምታውቀው ለ30 ተከታታይ እትሞች 24,000 የአሜሪካን ዶላር ከፍለንሃል፡፡ አሁን ግን አልሻባብ ዕቅዶቹን ለመፈፀም የስልት ለውጥ አድርጓል፡፡ ስለዚህም 11,200 የአሜሪካን ዶላር የሚሆነውን የ14 እትሞች ክፍያ ለአልሻባብ እንዲመለስ እንፈልጋለን፡፡…›› የሚል እና ሌላም፣ ሌላም ይዘት ያለውን ደብዳቤ ተመስገን የተቀነባበረ ሴራ እንደሆነ ማረጋገጫ ያላቸውን ነገሮች ከዘረዘረ በኋላ ‹‹… ስርዓቱ እዚህ ድረስ ወርዶ ለመወንጀል እየሞከረ ያለው ሀገራችንን ጥለን እንድንሄድ አልያም ራሳችንን በዝምታ እንድንሸብብ ከሆነ፤ የሚሰማ ካለ አቋማችንን በተደጋጋመ ማሳወቃችንን ብቻ አስታውሶ ከማለፍ ውጪ አማራጭ የለውም፡፡..›› ብሏል፡፡

* * *


‹‹ዶ/ር እሌኒ ከኃላፊነታቸው ለቀቁ›› የሚል ዜና በፊት ገጹ ያስነበበው አዲስ አድማስ ‹‹… የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ዋና ሥራ አስፈፃሚ የነበሩት ዶ/ር እሌኒ ገ/መድህን፣ የሥራ ማስፋፊያ ዕቅዳቸው ተቀባይነት ማጣቱን ሮይተርስ የዘገበ ሲሆን ሥራ አስፈፃሚዋ ከነበራቸው ኃላፊነት ለቀዋል፡፡ ዶ/ር እሌኒ በምርት ገበያ መስራችነታቸው ዓለምአቀፍ እውቅናና ሽልማቶች እንዳገኙ የሚታወቅ ሲሆን ድርጅቱን ለመመስረትና ለመምራት አብረዋቸው እንዲሠሩ በዓለምአቀፍ መመዘኛ ቀጥረዋቸው የነበሩ ዘጠኝ ባለሙያዎችም ከሳቸው ጋር ለቀዋል፡፡ የደርጅቱን ሥራ ለማስፋፋት ከመንግስት ጋር ውይይት ሲያካሂዱ መቆየታቸውን የተናገሩት ዶ/ር እሌኒ፣ አንዳንድ ዋና ዋና እቅዶች እንደከሸፉ ለሮይተርስ ገልፀዋል፡፡…. በዶ/ር እሌኒ ምትክ የአቢሲኒያ ም/ፕሬዚደንት የሆኑት አቶ አንተነህ አሰፋ የተሾሙ ሲሆን፣ ኩባንያው ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ ሲሰሩና ልምድ ሲቀስሙ የነበሩ የአገር ውስጥ ተቀጣሪ የማኔጅመንት ባለሙያዎች፣ አመራሩን ተክተው ይሰራሉ ተብሏል፡፡…››

* * *


ላይፍ መጽሄት ‹‹‹ጥቁር ሰው› ለሚኒልክ፣ ‹ስቴድ›ስ ለማን ተዘፈነ?›› በሚል ርዕስ በጻፈው ጽሁፍ ላይ የብርቱኳን ሚዼቅሳን ምስል አስቀምጦ ለርሷ እንደተዘፈነ ተከራክሯል፡፡ እንደማስረጃ ያስቀመጠው ‹‹…ቃል እንዲህ ሆነ እንዴ…›› የሚለውን ሐረግ ሲሆን ይህንንም ያለው ብርቱኳን ለሁለተኛ ጊዜ ከመታሰሯ በፊት ‹‹ቃሌ›› ብላ የጻፈችውን ደብዳቤ በማጣቀስ ነው፡፡ በተጨማሪም ‹‹…ቃል እንዲ ሆነ እንዴ…›› ካለ በኋላ በደበሰባሳው ‹‹…በሃገሬ…›› የሚል ዜማ ያሰማል በማለት ክርክሩን አጠናክሯል፡፡

* * *


የቴዎድሮስ ተ/አረጋይን ቃለ ምልልስ በአዲስጉዳይ የሚያነቡ ከBBC - Hardtalk ጋር ያመሳስሉታል፡፡ በዚህ ሳምንት አቦይ ስብሃትን አነጋግሯቸዋል፡፡ ‹‹አቦይ ስብሃት ከኢሕአዴግ ፊትና ኋላ›› የሚል ርዕስ ከተሰጠው ምልልሳቸው ውስጥ እየቀነጫጨብን እንመለከታለን፡-

Friday, June 22, 2012

ህግ ምርኩዝ ነው ዱላ ?

ዘላለም ክብረት

ህዝብ አብሮ ሲኖር ግጭት ሊያስወግደው የማይችለው ነገር ነው፡፡ የሰዎች የእርስ በእርስ ግንኙነት እስካለ ድረስ ግጭት አለ፡፡ በግጭቱ ጉልበተኛው አሸንፎ ተሸናፊውን እንደፈለገ ይቀጣል ማለት ነው፡፡ ይህ እንግዲህ እንግሊዛዊው የስነ መንግስት ሊቅ Thomas Hobbes ‘State of Nature’ የሚለው ወይም ጉልበተኛ የሚገዛበት ደካማ የሚጠቃበት እና Hobbes “ life is solitary, poor, nasty, brutish, and short” ብሎ የገለፀው ሀሳባዊ አለም ነው፡፡

ይህ እንዳይሆን ህዝብ ስምምነት ላይ ደረሰ ይሄንም ስምምነት በልቦናው ፈረመ 'መንግስት' የሚባልም አካል መሰረተ፡፡ ይህ አካልም ከህዝቡ ጉልበት ተቀንሶ ጉልበተኛን ይቀጣ ዘንድ ተሰጠው እንዲሁም ይህ መብት እንዳለው ሁሉ የህዝቡን ሰላም የማስጠበቅም ግዴታ ተሰጠው፡፡ ማን ? መንግስት የተባለው አካል፡፡

ታዲያ መንግስት በጦር በጎራዴ ብቻ ሰላምን አያሰጠብቅም ይልቅስ ሰላማዊ መሳሪያውን ይመዛል ይሄም መሳሪያ የመንግስት ህግ ነው፡፡ ህዝቡም ያከብረው ዘንድ ይወዳል ወይም ይገደዳል፡፡ ስለዚህ የመንግስት ህግ ማለት መንግስት ህዝብ ከራሱ የተፈጥሮ ስልጣን ቀንሶ መንግስት ለተሰኝው አካል ስለሰጠው መንግስቱ ይሄን የህዝብ አደራ ለመጠበቅ የሚቀርብ በትር ነው፡፡

በመሰረቱ የኢትዮጵያም ታሪክ በዚህ የመንግስት ህልዮት ይገዛል፡፡ ነገሩ የሚበላሸው መንግስት የተባለው አካል የህዝብን አደራ በልቶ ሌላ ዳቦ መጋገር ሲጀምር ነው፡፡ የህዝቡን ዳቦ በልቶ የራሱን ሽልጦ ሲያነጉት ነው መከራው፡፡

መንግስታት በተቀያየሩ ቁጥር የህዝብን ሰላም እና ጥቅም ለመስጠበቅ ህግ ያወጣሉ፣ ይከለክላሉ፣ ያስጠብቃሉ፡፡ ይሄም እውነት በጠነከረ ሁኔታ አሁን ባለንባት ኢትዮጵያ ገዝፎ ይታያል፡፡

ለምሳሌ

Wednesday, June 20, 2012

የቴሌኮም ማጭበርበር ሕጉ አወዛጋቢነት

የቴሌኮም ማጭበርበር ሕጉ አወዛጋቢነት የሚጀምረው ‹‹አዋጁ ፀድቋል፣ አልፀደቀም?›› የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ ስንጀምር ነው፡፡ አዲስ አድማስ ጋዜጣ በግንቦት 18፤ 2004 እትሙ ‹‹አዋጁ ፀድቋል›› ብሎ ቢዘግብም ለገዢው ፓርቲ በሚወግኑ ጽሁፎቹ የሚታወቀው ጦማሪ ዳንኤል ብርሃነ ደግሞ ገና ‹‹የመጀመሪያውን የንባብ ደረጃ ማለፉ ነው›› ይላል፡፡ ፍኖተ ነፃነትም በበኩሉ በሰኔ 12፤ 2004 እትሙ ‹‹ፍርሀት የወለደው የቴሌ አፋኝ ረቂቅ ሕግ›› ባሰኘው ጽሁፉ ገና ረቂቁ በፓርላማ እንደቀረበ ነገር ግን ከፓርላማችን ያለፈ ልምድ መረዳት እንደሚቻለው ‹‹የቀናት ጉዳይ ነው እንጂ መጽደቁ እንደማይቀር›› ያትታል፡፡

በአገራችን ረቂቅ ሕጎች የሚመለከተው ሕዝብ’ጋ በግልፅ ሳይደርሱ በጭምጭምታ ይቆዩና ድንገት በነጋሪት ጋዜጣ ታትመው ሕግ የመሆናቸው የተለመደ ድራማ በዚህ ረቂቅ አዋጅ ይለወጣል ብሎ መገመት ሞኝነት ነው፡፡ ይሄም ጽሁፍ በጭምጭምታው እውነታነት እና በረቂቅ ሕጉ ዙሪያ መጠነኛ ትንታኔ ይሰጣል፡፡

በቃሉ ኃይሉ (ስሙ ለዚህ ጽሁፍ ሲባል የተቀየረ) በስካይፕ የሚያወራው ከሚናፍቃቸውና ባሕር ማዶ ከሚኖሩ፣ እሱን ለማግኘት ኮምፒዩተር ላይ ቁጭ ብለው ከሚጠብቁት ጓደኞቹ’ጋ እንደሆነ ይናገራል፡፡ ‹‹እኔ እስከማስታውሰው ድረስ›› አለ ለዞን ዘጠኝ አስተያየቱን ‹‹እኔ እስከማስታውሰው ድረስ፤ ምንም ዓይነት ሕግ ሲወጣ ብወደውም ብጠላውም እታዘዝለት ነበር፡፡ አሁን ግን በስካይፕ ማውራት ሕገ-ወጥ ከሆነ ከጓደኞቼ እና ከሕጉ መምረጥ ሊኖርብኝ ነው፡፡ ጓደኞቼን ከሕጉ የማስበልጥበት ምክንያት እስካሁን አይታየኝም፡፡›› በቃሉ ይህንን የተናገረው አዋጁ ስካይፕ መጠቀምን በወንጀልነት ፈርጆታል የሚለውን ወሬ ከሰማ በኋላ ነው፡፡

‹‹የቴሌኮም ማጭበርበር አዋጁ›› ከስያሜውና ከትርጉም ክፍሉ ውጪ 18 አንቀጾች ብቻ አሉት፡፡ በሕገ-ወጥ መንገድ ስልክ ማስደወልም ሆነ ሌሎች የቴሌኮም አገልግሎቶችን ያለ ኢትዮ ቴሌኮም እውቅና መስጠት የማይቻል መሆኑ ድሮም በሕግ የተደነገገ ቢሆንም አሁን የዚህ አዋጅ መውጣት አስፈላጊ የሆነው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በማሕበራዊ ደረገጾች ላይ እያደገ የመጣውን ፀረ-አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊነት ለመገደብ እንደሆነ ብዙዎች መጠራጠር ጀምረዋል፡፡ የአዋጁ መግቢያ ላይም እንዲህ የሚል ይነበባል፡፡ ‹‹…የቴሌኮም ማጭበርበር ከኤኮኖሚ ኪሳራውም ባሻገር ዋና የደህንነት ስጋት በመሆኑ…›› ህግ አውጪው በረቂቅ አዋጂ ከኢኮኖሚያዊ ምክንያቶች ባለፈ ለሃገር ደህንነት ማሰቡን በግልጽ ይናገራል፡፤(በዚህ ጽሁፍ ውስጥ አዋጁ የተጣቀሰው ከእንግሊዝኛው ቅጂ ሲሆን ትርጉሙ የዞን ዘጠኝ ነው፡፡)

ኢሕአዴግ ለአብዮታዊ ዲሞክራሲ የሚያደርገው ቅጥ ያጣ ጥበቃ አብዮታዊ ዴሞክራሲ ትችቶቹን በሐሳብ ማሸነፍ እንዳቃተው ያሳብቃል፡፡ በጥቅሉ የመረጃ መረብን እና በዋናነት ማሕበራዊ ድረገጾችን ማዕከል አድርገው የሚንቀሳቀሱት የመረጃ ምንጮች እንደ ዶ/ር ዳኛቸው አባባል ‹‹የመረጃ ኦና.›› (Information Vacuum) ለመፍጠርና አውራ ፓርቲው ‹የሕዝብ› መገናኛ ብዙሐንን በመጠቀም የሚያጮኻቸው ወደአንድ አስተሳሰብ ያዘነበሉ መረጃዎች ለሚፈጥሯቸው የገደል ማሚቱ ድምጾች እንቅፋት ሆነዋል፡፡

የቴሌኮም ማጭበርበር ሕጉ አወዛጋቢነት

የቴሌኮም ማጭበርበር ሕጉ አወዛጋቢነት የሚጀምረው ‹‹አዋጁ ፀድቋል፣ አልፀደቀም?›› የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ ስንጀምር ነው፡፡ አዲስ አድማስ ጋዜጣ በግንቦት 18፤ 2004 እትሙ ‹‹አዋጁ ፀድቋል›› ብሎ ቢዘግብም ለገዢው ፓርቲ በሚወግኑ ጽሁፎቹ የሚታወቀው ጦማሪ ዳንኤል ብርሃነ ደግሞ ገና ‹‹የመጀመሪያውን የንባብ ደረጃ ማለፉ ነው›› ይላል፡፡ ፍኖተ ነፃነትም በበኩሉ በሰኔ 12፤ 2004 እትሙ ‹‹ፍርሀት የወለደው የቴሌ አፋኝ ረቂቅ ሕግ›› ባሰኘው ጽሁፉ ገና ረቂቁ በፓርላማ እንደቀረበ ነገር ግን ከፓርላማችን ያለፈ ልምድ መረዳት እንደሚቻለው ‹‹የቀናት ጉዳይ ነው እንጂ መጽደቁ እንደማይቀር›› ያትታል፡፡

በአገራችን ረቂቅ ሕጎች የሚመለከተው ሕዝብ’ጋ በግልፅ ሳይደርሱ በጭምጭምታ ይቆዩና ድንገት በነጋሪት ጋዜጣ ታትመው ሕግ የመሆናቸው ነገር የተለመደ ድራማ በዚህ ረቂቅ አዋጅ ይለወጣል ብሎ መገመት ሞኝነት ነው፡፡ ይሄም ጽሁፍ በጭምጭምታው እውነታነት እና በረቂቅ ሕጉ ዙሪያ መጠነኛ ትንታኔ ይሰጣል፡፡

በቃሉ ኃይሉ (ስሙ ለዚህ ጽሁፍ ሲባል የተቀየረ) በስካይፕ የሚያወራው ከሚናፍቃቸውና ባሕር ማዶ ከሚኖሩ፣ እሱን ለማግኘት ኮምፒዩተር ላይ ቁጭ ብለው ከሚጠብቁት ጓደኞቹ’ጋ እንደሆነ ይናገራል፡፡ ‹‹እኔ እስከማስታውሰው ድረስ›› አለ ለዞን ዘጠኝ አስተያየቱን ‹‹እኔ እስከማስታውሰው ድረስ፤ ምንም ዓይነት ሕግ ሲወጣ ብወደውም ብጠላውም እታዘዝለት ነበር፡፡ አሁን ግን በስካይፕ ማውራት ሕገ-ወጥ ከሆነ ከጓደኞቼ እና ከሕጉ መምረጥ ሊኖርብኝ ነው፡፡ ጓደኞቼን ከሕጉ የማስበልጥበት ምክንያት እስካሁን አይታየኝም፡፡›› በቃሉ ይህንን የተናገረው አዋጁ ስካይፕ መጠቀምን በወንጀልነት ፈርጆታል የሚለውን ወሬ ከሰማ በኋላ ነው፡፡

‹‹የቴሌኮም ማጭበርበር አዋጁ›› ከስያሜውና ከትርጉም ክፍሉ ውጪ 18 አንቀጾች ብቻ አሉት፡፡ በሕገ-ወጥ መንገድ ስልክ ማስደወልም ሆነ ሌሎች የቴሌኮም አገልግሎቶችን ያለ ኢትዮ ቴሌኮም እውቅና መስጠት የማይቻል መሆኑ ድሮም በሕግ የተደነገገ ቢሆንም አሁን የዚህ አዋጅ መውጣት አስፈላጊ የሆነው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በማሕበራዊ ደረገጾች ላይ እያደገ የመጣውን ፀረ-አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊነት ለመገደብ እንደሆነ ብዙዎች መጠራጠር ጀምረዋል፡፡ የአዋጁ መግቢያ ላይም እንዲህ የሚል ይነበባል፡፡ ‹‹…የቴሌኮም ማጭበርበር ከኤኮኖሚ ኪሳራውም ባሻገር ዋና የደህንነት ስጋት በመሆኑ…›› ህግ አውጪው በረቂቅ አዋጂ ከኢኮኖሚያዊ ምክንያቶች ባለፈ ለሃገር ደህንነት ማሰቡን በግልጽ ይናገራል፡፤(በዚህ ጽሁፍ ውስጥ አዋጁ የተጣቀሰው ከእንግሊዝኛው ቅጂ ሲሆን ትርጉሙ የዞን ዘጠኝ ነው፡፡

ኢሕአዴግ ለአብዮታዊ ዲሞክራሲ የሚያደርገው ቅጥ ያጣ ጥበቃ አብዮታዊ ዴሞክራሲ ትችቶቹን በሐሳብ ማሸነፍ እንዳቃተው ያሳብቃል፡፡ በጥቅሉ የመረጃ መረብን እና በዋናነት ማሕበራዊ ድረገጾችን ማዕከል አድርገው የሚንቀሳቀሱት የመረጃ ምንጮች እንደ ዶ/ር ዳኛቸው አባባል ‹‹የመረጃ ኦና.›› (Information Vacuum) ለመፍጠርና አውራ ፓርቲው ‹የሕዝብ› መገናኛ ብዙሐንን በመጠቀም የሚያጮኻቸው ወደአንድ አስተሳሰብ ያዘነበሉ መረጃዎች ለሚፈጥሯቸው የገደል ማሚቱ ድምጾች እንቅፋት ሆነዋል፡፡

ከቻይና ምን መማር?
‘ሪፖርተርስ ዊዝ አውት ቦርደርስ’ የተባለ የጋዜጠኞች ድንበር የለሽ ቡድን ቻይናን ‹ከኢንተርኔት ጠላቶች› አንዷ እንደሆነች ያስቀምጣታል፡፡ የቻይና ኮሙኒስት ፓርቲ ልኡካን ቡድን ደግሞ በአዲስ አበባ ለሚገኘው አቻው - ኢሕአዴግ በብዙሐን መገናኛ እና ኢንተርኔት አስተዳደር ዙሪያ ያካበተውን ልምድ አካፍሎ ተመለሰው በቅርብ ጊዜ እንደሆነ በገዢው ፓርቲ ድረገጽ ላይ የሰፈረው ዜና ያስረዳል፡፡

ቻይና ‹‹የምዕራቡ ዓለም የመረጃ ነፃነት ባሕል የአገሬን ባሕል ያጠፋል›› በሚል ስም ለበርካታ ብዙሐን መገናኛ በሯን ዘግታለች፡፡ ለቻይና ብቻ ተብሎ የተዘጋጀው ጉግል አንዳንድ የኮሙኒስት ፓርቲን የሚያስቀይሙ ቃላቶችን እንዳይፈልግ ተደርጎ በልኳ ተሰፍቶላታል፡፡ ፌስቡክና ትዊተርም ታግደዋል፡፡

የቻይና የፍቅር ልጅ የሆነችው ሃገራችን ከቻይና በቀሰመችው ልምድና ቴክኖሎጂ የቪኦኤና የዶቼቬሌን ሬዲዮ ጣቢያ ማፈኗን መንግስቷ አምኗል፡፡ በርካታ ድረገጾችም ታግደዋል፡፡ አንድ የዞን ዘጠኝ አባል በግሉ ባደረገው ቅኝት 65 ነፃ ድረአምባዎች፣ 14 የፓርቲ እና ለፓርቲ የሚወግኑ ድረአምባዎች፣ 37 ጦማሮች፣ 7 የበይነመረብ ሬዲዮና ቴሌቪዥኖች እና 37 የፌስቡክ ቡድን ገጾች በኢትዮጵያ እንዳይነበቡ መደረጋቸውን አረጋግጧል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ ነው አዲሱ አዋጅ በመረጃ ደህንነት መረብ አርቃቂነት ለፓርላማ የቀረበው፡፡ ‹አዲሱ አዋጅ ምን ዓይነት በቀላሉ ትርጉማቸውን ሊጠመዘዝ የሚችሉ አንቀጾች አሉት? የማሕበራዊ ድረገጽ እንቅስቃሴዎችን እንዴት ያውካቸዋል? ሐሳብን በነፃ ከመግለጽ መብት አንጻርስ አዋጁ እንዴት ይታያል? ስካይፕና ጉግል ቶክን የመሳሰሉት በVoice over Internet Protocol የሚጠቀሙ አገልግሎቶችን ሕገወጥ ያደርጋቸው ይሆን?› የሚሉ ጥያቄዎችን የሚያጭሩ እና ለማብራሪያ ክፍት የሆኑ አንቀጾችን ከዚህ በታች እንጠቃቅሳለን፡፡

አወዛጋቢዎቹ አንቀጾች
በአዋጁ ክፍል አንድ በተለዩ ቃላት ትርጉሞች ላይ የሚከተሉትን ያስቀምጣል፡፡ አንቀጽ 2 ላይ ‹‹የቴሌኮሙኒኬሽን ቁሳቁስ ማለት ለቴሌኮሙኒኬሽን አገልግሎት የዋለ ወይም ሊውል የታቀደ ዕቃ፤ መገጣጠሚያ (accessories) እና ሶፍትዌሮችን ጨምሮ ማለት ነው፡፡›› ይላል፡፡ አንቀጽ 1 ላይ ‹የቴሌኮሙኒኬሽን አገልግሎት› የሚለውን ሲተረጉም በኤሌክትሮኒክ መንገድ የሚቀርቡ ጽሁፎች እና ምስሎች ከአገልግሎቱ እንደሚካተቱ ጠቁሟል፡፡ ሶፍትዌሮችን በዚህ ትርጉም ውስጥ በማካተት የተከታይ አንቀጾችን ትርጉም በዚያ መልኪ እንድናይ ያስገድደናል፡፡

ክፍል ሁለት፣ አንቀጽ 3 ‹‹ሚኒስትሩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመምከር የትኞቹ የቴሌኮሙኒኬሽን ቁሳቁሶች፣ አምራቾች፣ ገጣጣሚዎች፣ አስመጪዎች ፈቃድ እንደማይሹ ይገልጻል፤ ደንብ ያበጃል›› ይላል፡፡ ይህም በሚኒስትሩ (ሚኒስትሩ የሚባለው የኢንፎርሜሽን እና ኮምዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ነው፡፡) ያልተዘረዘሩ የመገናኛ ቴክኖሎጂዎችን መጠቀም፣ ተጠቃሚውን በወንጀልነት እስከ 4 ዓመት ፅኑ እስራት እና እስከ 40,000 ብር በሚደርስ ቅጣት፣ አስመጪ እና አከፋፋይ ድርጅቶችን ደግሞ ‹‹..ከ10 እስከ 15 ዓመት የሚደርስ ጽኑ እስራት እና ከ100,000ብር እስከ 150,000 ብር የሚደርስ ቅጣት..›› ሊያስከትልበት እንደሚችል ረቂቁ ይደነግጋል፡፡

የዚህ አንቀጽ ለትርጉም ክፍት መሆን የምንጠቀምባቸው የበይነመረብ ማሰሻዎች (Internet browsers)፣ ሶፍትዌሮች (skype, google talk…)፣ የስልክ ቀፎዎች (blackberry, iPhone, Android ስልኮች፣ ወዘተ…)፣ እና ሌሎችም ዓይነት በሚኒስትሩ ይወሰናሉ፣ ካልተወሰኑ ደግሞ ለመጠቀም ፈቃድ ያስፈልጋል የሚል አንድምታ ይኖረዋል ማለት ነው፡፡(የጆሮ ማዳመጫ የተጠቀመ ሰው ያልተፈቀደ መሳሪያ ገጣጥሞ ተጠቀመ ቢባል ሊስቀጣው ነው ማለት ነው እስከሚል የተለጠጠ ትርጉም ድረስ ሊወስደን ሁሉ ይችላል)

አንቀጽ 6(1) ደግሞ ‹‹ማንም የቴሌኮም መረብን ወይም መሳሪያን በመጠቀም በፀረሽብርተኝነት አዋጅ 652/2001 መሰረት የሽብር መልዕክት ቢያሰራጭ ወይም በወንጀለኛ መቅጫ ሕግ መሰረት የሚያስጠይቅ አጸያፊ መልዕክት ቢያሰራጭ… ከ3 እስከ 8 ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራት እና ከ30,000 እስከ 80,000 ብር ድረስ ይቀጣል›› ይላል፡፡በዚህ አንቀጽ የተጠቀሰውን ወንጀል መፈጸም በዚህ ህግ ቢካታትም ባይካተትም ማስጠየቁ የማይቀር ሆኖ ሳለ በድጋሚ የተለየ ሽፋን መስጠቱ የህጉን አስፈላጊነት እንድንጠይቅ ያስገድደናል፡፡

አንቀጽ 13 ‹‹የቴሌኮም ማጭበርበርን ለመከላከል፣ ለመመርመርና ለመቆጣጠር ብሔራዊ የቴክኒክ ሥራ ቡድን ከሚመለከታቸው አካላት ተውጣጥቶ ይቋቋማል፡፡››

አንቀጽ 14 ‹‹ፖሊስ የቴሌኮም ማጭበርበር ተከስቷል ወይም ሊከሰት ይችላል ብሎ ባመነ ጊዜ ከፍርድ ቤት የብርበራ ፈቃድ መጠየቅ ይችላል፡፡›› ይህም የአንድ ሰው የስልክ ንግግር፣ አጭር የጽሁፍ መልዕክቶች፣ የኢሜይል መልዕክት ልውውጦች እንደአስፈላጊነታቸው የሚበረበሩበትን የሕግ አግባብ ይሰጣል ማለት ነው፡፡ መንግስት የኢንተርኔት አጠቃቀምን በተመለከተ ለአገሪቱ ደህንነት የሚያሰጉ ነገሮች ካሉ መቆጣጠር አለበት የሚለው ነጥብ ላይ መስማማት ቢቻልም የግለሰቦችን ነፃነት በተራ ፍራቻ ማሳጣት ግን ከሰብአዊ መብት ጥሰት ውስጥ ሊመደብ ይችላል፡፡

ህጉ በአጠቃላይ ካሉበት መሰረታዊ ገደቦች(limitations) መካከል ዋና ዋናዎቹ የግለሰቦችን ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት በሃገር ደህንነት ስም መንጠቁ፣ለትርጉም ክፍት የሆኑ ሰፋፊ ሃሳቦችን ማጠቃለሉ እንዲሁም የህጉን አስፈላጊነት በሚገባ ሊያሳምን አለመቻሉ ናቸው፡፡

ከሌሎች የተለመዱ ሕጎች በተለየ የማስረጃ ሁኔታን የዳሰሰው ይህ አዋጅ ለወትሮ ከምንጠቀምባቸው የማስረጃ አይነቶች በተጨማሪ ተቀባይነት ያላቸው ያላቸውን ተጨማሪ የማስረጃ አይነቶች ይጨምራል፡፡ይህ ከመሰረታዊ ሰብአዊ መብት ጥበቃ ጋር እና ከመሰረታዊ የወንጀል ህግ ጋር መታረቁ ያልተገጋገጠ የማስረጃ ስርአት በህጉ ትግበራ ወቅት ታርሞ ይተገበራል ማለት ዘበት ነው፡፡

ወደ ኢንተርኔት ወደ ስልክ መደወልን፣ያልተፈቀዱ ሶፍትዌሮችን መጠቀምን፣ እንዲሁም የጽሁፎችን ይዘትን በብዙ ከሚወቀሰው የጸረ ሽብርተኝነት ህግ ጋር ማቀላቀሉ ህጉን ከተጸፈበት በላይ አላም እንዳለው ሌላ ምስክር ነው፡፡
ወደ ስልክ መደወል እና ማስደወልን የሚከለክለው የህጉ አንቀፅ አስር ከተከለከሉ ሶፍት ዌሮች ጋር ተደምሮ የኢንተርኔት የድምጽ ንግግርን ወደ ወንጀልነት ይቀይረዋል፡፡

VoIP (Skype, Google Talk…) በሚኒስትሩ ይፈቀዱ ይሆን?

የቀድሞዋ አዲስ ነገር መራኄ ኤዲተር መስፍን ነጋሽ በፌስቡክ ገጹ ላይ ‹Promote then criminalize!› በሚል ርዕስ ባሰፈረው አጭር የስዕል ማብራሪያ ላይ (ምስሉን እዚህ ጦማር ላይ መመልከት ይቻላል) ከሁለት ቀን በፊት በሚኒስትሩ ድረገጽ ላይ VoIPን (Voice over Internet Protocolን) የሚያስተዋውቅ ይዘት ያለው መልዕክት ተለጥፎ እንዳገኘ (ያ ገጽ አሁን በሌላ ይዘት ተተክቷል) በምስል አዘጋጅቶ እና የመጀመሪያው መስመር ላይ "ስለ VoIP ሰምታችሁ የማታውቁ ከሆነ የረዥም ርቀት የስልክ ጥሪዎችን የምታደርጉበትን መንገድ ለመቀየር ተዘጋጁ" የሚል ነገር እንዳነበበ ጠቅሶ ጽፎ ነበር፡፡ መስፍን ነጋሽ ይህንን ሁኔታ ከረቂቅ አዋጁ አንፃር በመታዘብ አገልግሎቱን እያስተዋወቁ፣ ተጠቃሚዎቹን ወንጀለኛ ከማድረግ የተቀነባበረ ሴራ ለይቶ እንደማያየው ተናግሯል፡፡

የሚኒስተሩ ድረገጽ በፍጥነት በሌላ ጽሁፍ መተካቱ አዋጁ እውነትም VoIP ኢላማ አድርጎ ተነስቷል ብሎ ለመጠርጠር እንደ አንድ ግብአት ሊቆጠር ይችላል፡፡ በሌላ በኩል እ.ኤ.አ. በ2002 የቴሌሴንተር አገልግሎት ፈቃድን በተመለከተ በወጣው መመሪያ አንቀጽ 13(2) ላይ VoIP (ከኮምፒዩተር ወደ ኮምፒዩተር የሚደረግ የድምጽ ግንኙነት ጨምሮ /ስካይፕን ያካትታል/) የተከለከለ ቢሆንም እስካሁን ድረስ የተለያዩ ኢንተርኔት ካፌዎች ስካይፕን በይፋ ሲጠቀሙ እንጂ በወንጀል ሲከሰሱ የታየበት አንድም መረጃ የለም፡፡ ሌላው ቀርቶ ኢቴቪ የሕዳሴው ግድብን አንደኛ ዓመት አስመልክቶ ለጠቅላይ ሚኒስቴሩ በስካይፕ ጥያቄ ማቅረብ ይቻላል እያለ ሲያስተዋውቅ መክረሙ የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡

በመሆኑም መመሪያው እያለ፣ የፀረ-ሽብርተኝነቱም ሆነ የወንጀለኛ መቅጫ ሕጉ እያሉ አዲሱ ‹የቴሌኮም ማጭበርበር አዋጅ› እዚያ የተካተቱትን ሕግጋት ደግሞ መውጣቱ ያስፈለገበት ምክንያት ግልጽ አለመሆን የእነዚህን የቴክኖሎጂ ውጤቶች መስፋፋት ተከትሎ እያደገ የመጣውን ሐሳብን በነፃ የመግለጽ መብት ለማፈን የተወሰደ እርምጃ ነው የሚለውን መላምት ያጠናክረዋል፡፡ ለዚህም እንደዋቢ መጥቀስ የሚቻለው በረቂቁ ላይ ‹‹መንግስት በሕዝቡ አመኔታ እንዲያጣ የሚያደርግ…››፣ ‹‹… አፀያፊ ጽሁፎች›› የሚሉ አሻሚ እና ሰፊ ትርጉም የሚኖራቸውን ሐረጎች መጠቀሙ የአዋጁ ኢላማ በተለይ ማሕበራዊ ድረገጾች ላይ በሚደረጉ የግል ሐሳብን በነፃ የመግለጽ መብት ላይ ስጋት የሚጥሉ ሆነዋል፡፡

ሚኒስትሩ VoIPን ከሚከለከሉ አገልግሎቶች መካከል እንደሚያስቀምጣቸው ለመጠርጠር የሚያበቃ ሌላም ምክንያት አለ - የገዢው ፓርቲ የቅርብ ሚዲያ እና ህግ አውጪው ሬድዮ ፋና፡፡ የዜና መጽሄት በተሰኘው ፕሮግራሙ ሬዲዮ ፋና የረቂቅ አዋጁ መንፈስ ሁሉንም ዓይነት VoIPን የሚጠቀሙ አገልግሎቶችን ለማገድ የወጣ እንደሆነ ፍንጭ ይሰጣል:: በተለይ (በፕሮግራሙ ላይ) አንድ የምክር ቤት አባል የአዋጁን አስፈላጊነት ለማስረዳት ሲናገሩ ኢትዮ ቴሌኮም እንደስካይፕ ያሉ በኢንተርኔት ስልክ የማስደወያ ሶፍትዌሮችን በሕግም ሆነ በቴክኖሎጂ ቁጥጥር ስር ማድረግ እንዳለበት አስረድተዋል:: አዲሱ የቴሌኮም አዋጅ ረቂቅ ደግሞ ለቴሌ ይህን ሕጋዊ ዳራ ይፈጥርለታል::

አዋጁ ከኢትዮ ቴሌኮምም በላይ በድብቅ የኢንተርኔት ማጥለል (Internet filtration) ሥራ በመስራት የሚታማውን የመረጃ መረብ ደህንነት ኤጀንሲን (INSAን) ነፃ ያወጣዋል - የረቂቁ አንቀጽ 13 ‹የቴክኒክ የሥራ ቡድን›መቋቋም የሚለው ከለላ በማስቀመጥ፡፡

ባሳለፍነው ሳምንት እየተዘዋወርን ያነጋገርናቸው ጥቂት የኢንተርኔት ካፌ አገልግሎት ሰጪዎች ከወዲሁ (አዋጁ ከመጽደቁ እና በነጋሪት ጋዜጣ ከመውጣቱ በፊት) የስካይፕ እና ማንኛውንም የድምጽ (Voice over IP) አገልግሎት መስጠት ማቆማቸውን ለመረዳት ችለናል፡፡

ዳንኤል ብርሃነ ከላይ ባጣቀስነው ጦማሩ ላይ ‹‹ስካይፕ በሕግ እንደማይታገድ የጥብቅና ባርኔጣዬን አስይዤ እወራረዳለሁ›› ሲል ከተከራከረው በተቃራኒ መደምደም እንደሚቻለው፣ አዋጁ አሁን አሁን እያቆጠቆጠ የመጣው በበይነመረብ ላይ ሐሳብን በነፃ የመግጽ ፍላጎት ላይ ክፉ ጥላ መጣሉ ነው፡፡ እንዲያውም አንዳንዶች የአዋጁ ብቸኛ ዓላማም ይኸው ነው ሲሉ ጥርጣሬያቸውን ከወዲሁ እየገለፁ ነው፡፡ ውጤቱን ለማየት ግን አዋጁ ፀድቆ(በፓርላማ ክርክር እና የጋለ ውይይት ጋር) የተግባር እርምጃው እስኪጀመር ጥቂት ወራት ብቻ መታገስ በቂ ይሆናል፡፡