Monday, August 26, 2013

ጋዜጦች ባሳለፍነው ሳምንት



ኢትዮ-ምኅዳር ማክሰኞ ነሐሴ 15/2005ዓ.ም.

·         ርዕሰ አንቀፅ፡ የሕግ የበላይነት እና የፍትህ ልዕልና ይከበር

“አንድ የመንግስት ሹመኛ እና አንድ የመንግስት ተቋም በእያንዳንዱ ዜጋ ላይ እንደፈለገው አድርጎ ወንጀል ይጋግራል፡፡ ለይምሰል ከፊል   ሕጋዊ አካሄድ ይከተላል፡፡ እናም ንጹሃንን ያሳቅቃል፣ ያሳስራል፣ ያሰቃያል፣ ይጎዳል፡፡ ሃብት ይነጥቃል፡፡
በአንዲት ቀጭን ስልክ የመንግስት አስፈፃሚ አካ ጥሪ፣ ዜጋን  ከእለት ተዕለት ባተሌ ኑሮ ወደ አሥረኝነት ትቀየራለች፡፡ በዚህ ጊዜ ለምን ብሎ መጠየቅ ሞኝነት ይሆናል፡፡ ምክንያቱም ችግሩ የህግ አሊያም የህገመንግስት ሳይሆን፣ የተፃፈውን እና የሆነውን በአግባቡ ከመተግበሩ ቁርጠኝነት ማጣት ላይ ነው፡፡”

·         ኢህአዴግን ጨምሮ አንድነት፣ ሠማያዊ፣ መድረክ እና ኤዴፓ ባለፈው ቅዳሜ በኢትዮጵያ ሬድዮ እና ቴሌቪዥን ድርጅት ውስጥ በፀረ ሽብር አዋጁ ላይ ለሶስት ሰዓት የቆየ ውይይት ማካሄዳቸውን፤ መድረክን ወክለው የኦፌኮ ፓርቲ ዋና ፀሃፊ አቶ በቀለ ነጋ፣ አንድነትን ወክለው አቶ ሃታሙ አያሌው፣ ሠማያዊን ወክለው የፓርቲው ፕሬዝዳንት አቶ ይልቃል ጌትነት እንዲሁም ኢህአዴግን በመወከል በሚኒስቴር ማዕረግ የጠቅላይ ሚ/ሩ ቃል አቀባይ አቶ ጌታቸው ረዳ እና የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር ዲኤታ አቶ ሽመልስ ከማል መቅረባቸውን፤ መኢአድ ላይ እንዲሳተፍ አለመጋበዙን

Monday, August 19, 2013

የሕዝብ ንቀት



በፍቃዱ ኃይሉ

‹ከናንተ መካከል የሕዝብ ንቀት የሌለበት ማነው?›

ከትንሹ እስከ ትልቁ፣ ከመንግሥት እስከ ልሒቁ፣ ከሊቁ እስከ ደቂቁ - ሁሉም መጠኑ ይለያይ እንጂ የሕዝብ ንቀት አለበት፡፡ ‹‹ይሄ ሕዝብ…›› ብሎ የበቀለበትን ሕዝብ የማይተች ግለሰብ ማግኘት ከባድ ነው፡፡ እኔ ራሴ ከዚህ በፊት ሕዝብን በአደባባይ ከተቸሁባቸው ጽሑፎች ውስጥ ‹‹ሁሉም ሕዝብ ገዢው መንግሥት ይመጥነዋል››፣ ‹‹ሕዝቦች ግለሰብን ይጨቁናሉ›› እና ‹‹ሕዝብ ምንድን ነው?›› የሚሉ ርዕሶች የሰጠኋቸው አይዘነጉኝም፤ የተሳሳተ መልዕክት ይዘዋል ማለቴ ግን አይደለም፡፡ ለዚህም ነው ሕዝብን እንደተራ መንጋ ብቻ መቁጠር በጣም ስህተት መሆኑን እና የእያንዳንዱ ዜጋ ድምር ውጤት መሆኑን እና ማኅበረሰቡን ወካይ መሆኑንም ለመጥቀስ ይህንን መጻፍ ያስፈለገኝ፡፡

ንቀት በያይነቱ

በአንድ መጽሔት ውስጥ ለተወሰኑ እትሞች በኤዲተርነት ተቀጥሬ በመሥራት ውስጣዊ አሠራራቸው ምን እንደሚመስል ለመገምገም እና ከተለያዩ በአገራችን በሚዲያ ሥራ ላይ ለረዥም ጊዜ ከተሰማሩ ሰዎች ጋር ለማውራት ሞክሬ ነበር፡፡ የተረዳሁት ነገር ቢኖር በማወቅም ይሁን ባለማወቅ የተፈጠሩ የሕዝብ ንቀቶችን ነው፡፡

ቢያንስ ብዙዎቹ የሚዲያ ሰዎች ‹‹ሕዝቡ የሚወደው እንዲህ ዓይነቱን ነገር ነው…›› የሚሉት ነገር አላቸው፡፡ በደንብ እንድንግባባ ‹‹ሎሚ›› መጽሔት በአሁኑ ሰዓት ከፍተኛ ገቢና ስርጭት ያለው ነገር ግን ከፌስቡክ እና ከተለያዩ ብሎጎች ላይ የተቃረሙ፣ ቢያንስ አንድ ሳምንት ያለፋቸው ታሪኮች ጥርቅም ነው፡፡ ይህ ተሞክሮ ሌሎቹን ሚዲያዎች ሎሚ ሞዴላቸው እንዲሆን እና ሕዝቡ ‹በቅጡ ያልታሰበበት እና ያለፈበት ጽሑፍ በተቀጠሩ ሠራተኞች በጥንቃቄ ከተዘጋጀ እና ከትኩስ መጣጥፎች የበለጠ ይመርጣል› የሚል ድምዳሜ ላይ እንዲደርሱ አድርጓቸዋል፡፡ በሁለት እና በሦስት ሠራተኛ ብቻ ከኢቪዲዮ ላይ በወረዱ ሥራዎች አንዱ ሲከብር ሌላው ሌላው ግን በርከት ያሉ ሠራተኞችን ቀጥሮ፣ ከየትም ቀራርሞ የሚያመጣው መረጃ ገዢ አያገኝም፡፡ ለዚህ ደግሞ ‹‹ተጠያቂው የሕዝቡ ቅሽምና ነው›› ይሏችኋል፡፡ እውነታው ግን ይሄ አይደለም፤ እውነታውን እንመለስበታለን… ከዚያ በፊት ግን ይህ ዓይነቱ ችግር ሚዲያው ላይ ብቻ ሳይሆን በየዘርፉ ያለ ችግር መሆኑን ተጨማሪ ምሳሌዎች መዘርዘር አለብን፡፡

ጋዜጦች ባሳለፍነው ሳምንት

ኢትዮ-ምኅዳር ማክሰኞ ነሐሴ 8/2005 ዓ.ም
  • በእነ ኤልያስ ክፍሌ መዝገብ በሽብርተኝነት ክስ ተፈርዶባቸው በማረሚያ ቤት ከሚገኙት አራቱ ኢትዮጵያውያን መካከል ይቅርታ ጠይቀው የነበሩት ሶስቱ፤ ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ፣ ወ/ሮ ሂሩት ክፍሌ እና አቶ ዘሪሁን ገ/እግዚአብሔር፤ ጥያቄያቸው ከቀረበ ከአንድ ዓመት ቆይታ በኋላ ሐምሌ 25/2005ዓ.ም የይቅርታ ቦርድ ጽ/ቤት ማህተም አርፎበት ለወ/ሮ ሂሩት ክፍሌ በተላከ ደብዳቤ የይቅርታ ጥያቄቸው ለፕሬዝዳንቱ ቀርቦ ውድቅ መደረጉን እንደተገለፃለቸው ነገር ግን የጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ እና የአቶ ዘሪሁም ገ/እግዚአብሔር ግን ምላሽ እንዳልደረሳቸው
  • የአምስት ፓርቲዎች ጥምረት የሆነው የኢትዮጵያ ፌደራላዊ አንድነት መድረክ ቅዳሜ ነሐሴ 1 ቀን 2004ዓ.ም ባካሄደው ጉባዔ ዶ/ር መራራ ጉዲናን ሊቀመንበር አድርጎ መምረጡን እና ለሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት መድረክን እንደሚመሩ
  • አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) የፀረ ሽብር ህጉን እንዲሰረዝ የሚያካሂደውን የ3ወር የሚሊዮኖች የነፃነት ድምፅ ንቅናቄ የመጀመሪያው ምዕራፍ ማጠናቀቂያ አስመልክቶ መስከረም 5 ቀን 2006ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ሊያደርግ እንዳቀደ
  • ሁለት የሬድዮ ቢላል ጋዜጠኞች ክስ ሳይመሰረትባቸው ከሣምንት በላይ ታስረው መቆየታቸው እንዳሳሰበው የጋዜጠኞች ተንከባካቢ ቡድን (CPJ) ባለፈው ሳምንት ባወጣው መግለጫ ማሳወቁን
 
የኛ ፕሬስ ማክሰኞ ነሐሴ 8/2005 ዓ.ም
  • ነሐሴ 14/2004ዓ.ም ከዚህ አለም በሞት የተነጠሉት የጠ/ሚ መለስ ዜናዊ በሥላሴ ካቴድል ቅጥር ግቢ ውድ በሆነ የእምነበረድ አይነት የታነፀው የተቀማጠለ መካነ መቃብር ተጠናቆ በመጪው ሳምንቶች ይመረቃል ተብሎ እንደሚጠበቅ
  • የወሲብ ድረገፆችን በማሰስ ኢትዮጵያ፤ ስሪላንካን ተከትላ ሁለተኛ መውጣቷን ጎግል የተሰኘው እውቅ ዓለም አቀፍ ተቋም ይፋ ማድረጉን እና ኢትዮጵያ ከቀዳሚዎቹ ተርታ እንድትቀመጥ በዘንድሮ ኣመት በደቡብ አፍሪካ እየተካሄደ ባለው የቢግ ብራዘር አፍካ ውድድር ተሳፊ የነበረችው ቤቲ አበራ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንዳበረከተች
  • ከስምንት ወር በፊት ለተለያዩ ስልጠናዎች ወደ ደቡብ ኮሪያ ካመሩ 59 ኢትዮጵውያን መካከል 38 ኢትዮጵያውያን የኮርያን መንግስት ጥገኝነት መጠየቃቸውን

Tuesday, August 13, 2013

የግብጹ ሙስሊም ወንድማማቾች ፓርቲ ውድቀት እና የናይል ፖለቲካ


በሚኪያስ በቀለ    

እንደ መነሻ፤ የግብጽ አብዮቶች

ግብጽን ለሠላሳ ዓመታት ያስተዳደራት የሁስኒ ሙባረክ መንግሥት ወዳጆቹን በሙስና አበለፀገ፣   የኑሮ ውድነትን ከማየት በቀር መፍትሔ ማምጣት አቃተው፡፡ በቱንዚያ የሕዝቡን ሥልጣን ያዩት የግብጽ ሕዝቦች በቃን እንዲሉ ምክንያት ሆናቸው፡፡ ሠላሳ ዓመታት ተንደላቀው ሀገሪቷን ያስተዳደሯት፤ ሙባረክን ጨምሮ የተለያዩ ኃላፊዎች ዕጣ ፈንታቸው በሰልፉ ላይ የተሳተፉ ግለሰቦችን በማስገደል እና በፈፀሙት ሰፊ የሙስና ተግባር ችሎት መቆም ሆነ፡፡ በመቀጠል የወታደራዊ መንግሥት ግብጽን ያስተዳድር ጀመር፡፡ አሰተዳደሩን በሲቪል ለመቀየር ሀገራዊ ምርጫ ተሰናዳ፡፡

በሙርሲ የሚመራውና በሙስሊም ወንድማማቾች የተመሠረተው የነጻነት እና ፍትሕ ፓርቲ (Freedom and Justice Party) አባላት 47.1 በመቶ በሆነ ጠባብ አብላጫ ድምጽ ግብጽን ለማስተዳደር ምክር ቤቱን ተቀላቀሉ፡፡ ሙሐመድ ሙርሲም 51.7 በመቶ ድምጽ አግኝተው የሃገሪቷ ጠቅላይ ገዥ ሆኑ፡፡ ነገር ግን ፕሬዘዳንት ሙርሲ የሥልጣን መንበራቸውን ከያዙ በኋላ ውሳኔያቸው በፍርድ ቤት ሳይቀር አይተችም የሚል መመሪያ አወጡ፡፡ የሀገሪቷን ኢኮኖሚ ቁልቁል ለቀቁት፡፡ ሕዝቡ የሙባረክ አስተዳደር በምን ጣዕሙ ይል ጀመር፡፡ የታህሪር አደባባይ በአዲሱ ፕሬዘዳንት ላይ ተቃውሞ በሚያቀርቡ ግብጻዊያን በድጋሚ ተሞላች፡፡ እራሳቸው የሾሙዋቸው የወታደሪያዊ ኃላፊዎች ሙርሲ ለሃገሪቷ መፍትሄ ማምጣት አይችሉም አሉ፡፡ አደባባይ የወጡትን ሰዎች ፍላጎት እንዲያሟሉ እና ውጥረቱን እንዲያረግቡ የ48 ሰዓት ገደብ አውጡላቸው፡፡ ሙርሲ አሻፈረኝ አሉ፡፡ በጭብጨባ በተሾሙ በዓመታቸው በወታደሩ ጉልበት እና በሕዝቡ ጩኸት ከመንበራቸው ተነሱ፡፡ የሙርሲ ደጋፊዎችም ዲሞክራሲ ለእስላም አይሠራምን? ብለው ጠየቁ፡፡ የመረጥናቸው ፕሬዘዳንት በመፈንቅለ መንግሥት ነው የተነሱትና ወደ ሥልጣናቸው ይመለሱ በሚል አመጻቸውን አቀጣጠሉ፡፡ ፖሊስ እና ወታደሩ በከፈቱት ተኩስ 54 የሙርሲ ደጋፊዎች ሐምሌ 2 ቀን ተገደሉ፡፡ አንዳንዶች በመሣሪያም ሳይቀር እንዋጋለን ብለው ሲያስተጋቡ ተደመጡ፡፡

Monday, July 29, 2013

ኢትዮጵያዊው ዳያስፖራ


በታዬ ዘሐዋሳ

በሃገራችን በነበረው ፖለቲካዊ ቀውስ ወይም አመለካከት የተነሳ በርካታ ኢትዮጵያውያን በስደት እንደሚኖሩ ይታወቃል:: የሚኖሩበትም ሃገር ብዛትና ስብጥር በራሱ ከሌሎች ሃገራት ዜጎች የተለየን ያደርገናል ብዬ አስባለሁ:: እንደ ሃገራቱ ስብጥር እና ብዛት ሁሉ የሃበሻ አመለካከትም እጅግ ብዙ ነው:: ይህ ብዛት ያለው ስብጥር ደግሞ ወጥ የሆነ አመለካከት እንዳይኖረን አድርጓል:: ክፍፍላችንም እንደዚያው ብዙ ነው:: ፍረጃችንም ጭምር:: የዛኑ ያክልም ኢትዮጵያዊ ዳያስፖራ ለመፈራረጅ ወይም ለመሞጋገስ ከንፋስ የፈጠነ ነው:: ፍረጃው ከተለያዩ አካላት ይጀመር እንጂ አብዛኛዎቹን ፍረጃዎች በማዳነቅና በማሟሟቅ ረገድ የሁሉም ድርሻ አለበት:: አንዲት የፌስቡክ ወዳጅ ስለፍረጃዎች ብዛት እና ጥልቀት ትዝብቷን አካፍላን ነበር:: ከነዚህ የርስ በርስ ፍረጃዎች ውስጥ የሚከተሉት በስፋት የምናስተውላቸው ናቸው:-

 . ኢቲቪ ወይም ኢሳት
 . ኢህአዴግ ወይም ተቃዋሚ
. አይጋ ፎረም ወይም ኢትዮጲያን ሪቪው
. አዲስ ዘመን ወይም ፍትህ
. ኢትዮጲያ ወይም ሞት ወይም ገንጣይ ተገንጣይ
. እምየ ሚኒሊክ ወይም አፄ ዮሃንስ
. ኢትዮጲያ ፈርስት ወይም ኦሮሞ ፈርስት
. ልማት ወይም ሰብአዊ መብት
. ንኡስ ከበርቴ ወይም ደሃ
. ኪራይ ሰብሳቢ ወይም ልማታዊ
. ሰለፊስት ወይም አህባሽ
. የውጪ ሲኖዶስ ወይም የሃገር ውስጥ ሲኖዶስ
. የምርጫ ትግል ወይም የትጥቅ ትግል
. ጠባብ ወይም አገር ወዳድ
. ባንዳ ወይም ጀግና
. የባንዳ ልጅ ወይም የጀግና ልጅ
. X ወይም Y እያለ ይቀጥላል::

ይህን የፍረጃ ብዛት እና አይነት ለግዜው በዚህ እናብቃው:: የፅሁፌ መነሻ ርዕሥ በርካታ ሃሳቦችን ማስነሳት እንዲሁም ኢትዮጵያዊ ዳያስፖራን በተመለከተ የተለያዩ ሃሳቦችን ማንሳትና ማወያየት እንደሚችል ግልፅ ነው:: አነሰም በዛም እነዚህን ሃሳቦች እያነሱ መወያየትም ሆነ መተራረም ስለ ድክመታችን አውቀን የማስተካከያ እርምጃ እንድንወስድ ይረዳናል:: ድክመቱን በገደምዳሜ እያየን የምናልፈው ከሆነ ግን ለሃገራችንም ሆነ ለህዝባችን ፋይዳ አናመጣም:: መፅሃፉ እንዳለውም አስቀድሞ በአይናችን ያለውን ምሰሶ ማውጣት ስንችል ነው የጓደኛችንን ጉድፍ ማየት የምንችለው:: ነገር ግን የኛ ዳያስፖራ እሱ ያለው እንጂ ሌላው የሚለው ትክክል አይደለም ብሎ የማሰብ አዝማሚያ ያሳያል:: እናም ምናልባት የኔ ሃሳቦች ከተወደደው ዳያስፖራ ሃሳብ ጋር ካልተስማሙ የማይስማሙበትን ሁኔታ ለመስማት ዝግጁ መሆኔን አስቀድሜ ልግለፅ:: የባህርያችንን ጥልቀት ለማሳየትም ይመስላል "ኢትዮጵያ የገባ አንድ ፀሃፊ በማግስቱ ስለ ኢትዮጵያውያን ከአንድ በላይ መፅሃፍ ሊፅፍ ይችላል:: በሁለተኛው ቀን ምናልባት ከተሳካለት ለጋዜጣ የሚሆን መጣጥፍ ሊፅፍ ይችላል:: ሳምንት ሲቆይ ግን ሰው ስለ ኢትዮጵያውያን አንድ አረፍተ ነገር እንኳ መፃፍ አይችልም" አለ የሚባለው:: ለማንኛውም ለዛሬ የሚከተሉትን "እዛም እዛም የረገጡ" ሃሳቦችን ላንሳ:: ነገር ግን የማነሳቸው ሃሳቦች ከጥቂት ኢትዮጵያውያን ዳያስፖራዎች ጋር ግንኙነት የሌላቸው እና እንደማይመለከታቸውም ባውቅም ብዙሃኑን ይወክል ዘንድ እነዚያን ጥቂቶችም የፅሁፌ አካል አድርጌያቸዋለሁ:: ለዚህ አስቀድሜ ይቅርታ እጠይቃለሁ::