Thursday, September 3, 2015

ከሕወሓት መማር

በፍቃዱ ዘ ኃይሉ What to Learn From TPLF
እስከዚያው ከሓት መማር የሚቀናቀኑትን አካል በቅጡ መረዳት ግማሹን መንገድ መምጣት ነው፡፡ የሕሓትን ታሪክ፣ የፖለቲካ አስተሳሰብ እና ወዘተርፈ መለየት ለሠላማዊ ትግላችን ሰፊ አስተዋፆ ይኖረዋል፡፡

ትምህርት አንድ
ሓት መራሹ የኢሕአዴግ መንግሥት በአውራ ፓርቲ ሥም፣ አሀዳዊ ፓርቲ ስርዓት እየዘረጋ ነው፡፡ መላ አገሪቱ ከቀበሌ እስከ ፓርላማ በአንድ አይነት አስተሳሰብ የተቃኙ፣ የአንድ ፓርቲ ሰዎች እንዲሞሉት አድርጓል፡፡ ይህ አመል ኢሕአዴግ የመንግስት ሥልጣን ከጨበጠ በኋላ የመጣ ይመስላል፡፡ ግን አይደለም፡፡ ሕሓት ከቀድሞ ወዳጁ ሻዕቢያ የተማረው ‹‹በአንድ ሜዳ ሁለት ኃይል አይኖርም›› የሚል አባባል አለው፡፡ በዚህ ፍልስፍና ሻዕቢያ ጀብሃን አጠፋ፡፡ ሕወሓት ደግሞ ሕግሐኤ፣ ኢዴኃ (EDU)፣ ኢሕአሠን በኃይል ደምስሷል፡፡ ሕዋሓት ደርግን ከመደምሰሱ በፊት አምባገነኑን ደርግን እንወጋለን ብለው ግን ደግሞ ከሱ በጥቂቱ የተለየ የፖለቲካ ፍልስፍና ይዘው ከጎኑ የተሰለፉ ኃይሎችን አጥፍቷቸዋል፡፡ ይህ የጫካ አመሉ ያደገበት ሓት (ኢሕአዴግን ለብሶ) ከተማ ሲገባ የቱንም ያክል ‹‹ዴሞክራሲ ለኢትዮጵያ አማራጭ የሌለው አማራጭ ነው›› እያለ ቢፎክርም፣ የተለየ አስተሳሰብ የሚያራምዱ ወገኖችን መታገስ አልቻለም፡፡
ሓት/ኢሕአዴግ የተለየ አስተሳሰብ የሚያራምዱ ወገኖችን ቀርቶ በውስጡ የሚከሰቱ የዴሞክራሲ ጥያቄዎችን እንኳን መታገስ አይችልም፡፡ ትግል ላይ በነበሩት ጊዜ የተነሳው የመጀመሪያው ሕንፍሽፍሽ (ቀውስ) ‹የአሽዓ (አክሱም፣ ሽረ እና አደዋ) ሰዎች የሥልጣን የበላይነት (ልክ አሁን የትግራይ ልሒቃን የሥልጣን የበላይነት በፌደራል መንግስቱ ውስጥ በዛ እንደምንለው) ፓርቲያችን ላይ እየታየ ነው› የሚል አቤቱታ ያቀረቡ አባላቱን በማስወገድ ነው የተጠናቀቀው፡፡ በ1993 በተፈጠረው ቀውስ ደግሞ የሉአላዊነት ጥያቄ ያነገቡ አባላቱን የውስጥ ሕገ-ደንቡን (ሓትን በማዳን ስም) ሽሮ፣ ምርጫ ቦርድ ባለበት አገር በጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ ማሕተም የተፃፈ ደብዳቤ ነበር ያሰናበታቸው፡፡ ይሕ ባሕል ከጫካ ተከትሏቸው የመጣ ባሕል ነው፡፡ የውብማር አስፋው ‹ፊኒክሷ ሞታም ትነሳለች› ባለችው መጽሐፏ እንዲህ ትለናለች፡-
‹‹ሓት ደንብ መሠረት አንጃ መፍጠር እስከ ሞት የሚደርስ ቅጣት ያስከትል ስለነበር፣ የሓት ፖሊት ቢሮ ይህንን ሲያስቀምጥ በማኅበሩ አመራር ውስጥ የማይፈልጋቸውና የሚጠላቸው የአመራር አባላት ሊኖሩ እንደሚችሉ ያመለክት ነበር፡፡ . . . ›› (ገጽ 112፣ ጋዜጠኛ ዮናስ በላይ እንዳጣቀሰው)
እነዚህ ችግሮች ስር ሰደው ነው የአሁኑን አማራጭ ሐሳብ የማይቋቋም ኢሕአዴግ የፈጠሩት፡፡ ይህንን የ1993ቱ የሓት ቀውስ ወቅት ከፓርቲው ከወጡት ታጋዮች መካከል አረጋሽ አዳነ ለጥሕሎ መጽሔት በሰጠችው ቃለምልልስ ከስር ከስሩ ባለመታረሙ የመጣ ጣጣ ነው በማለት ከታሪክ እንድንማር ትመክረናለች፡-
‹‹እነዚህ ሁሉ [ጥያቄዎችን በኃይል የመጨፍለቅ] ችግሮች ገና ድሮ ከመፈጠራቸው፣ [ስ]ር ከመስደዳቸው በፊት ቀደም ብለን ለዚህ ሁሉ መሰረት የሆኑትን ችግሮች . . . አስተውለን ከስር ከስር ወይም ደረጃ በደረጃ እየታገልናቸው ያለመምጣታችን አሉታዊ ፍፃሜ ነበር ብዬ አስባለሁ፡፡››
(ገጽ 77፣ ዮናስ በላይ፣ የትግራይ ሕዝብ፣ ወያኔዎቹና ሽፍቶቹ)
የቀድሞ የሓት ታጋዮች ፀፀትም ሆነ የአሁን ታሪኩ የሚያስተምረን ዴሞክራሲ መንገድ እንጂ መዳረሻ አለመሆኑን ነው፡፡ በዴሞክራሲያዊ መንገድ ያልመጣ ኃይል ዴሞክራሲን ሊያመጣ አይችልም፡፡

ትምህርት ሁለት
ሓት ደርግን ወግቶ ለድል እንዲበቃ በተለይ ሁለት ዘዴዎች ረድተውታል፡፡ ሠላማዊ ታጋዮች እነዚህን ዘዴዎች በራሳቸው መንገድ ተርጉመው ሊጠቀሙበት የችላሉ፡፡ የመጀመሪያው ደርግን እራሱን መጠቀሚያ ማድረግ ነው፡፡  ሓት የደርግን ክፋት ለራሱ ተቀባይነት መግዣ በማድረግ ተጠቅሟል፡፡ ለምሳሌ በትግል ወቅት የማረካቸው ወታደሮች ‹ተሃድሶ› ካሰለጠናቸው በኋላ ሁለት አማራጭ ይሰጣቸው ነበር፡፡ አንድ ከጎን ተሰልፈው ደርግን እንዲወጉ አልያም ወደቀዬአቸው እንዲመለሱ፡፡ የትኛውንም ቢመርጡ ሕዋሓት ያተርፋል፡፡ ተመላሾቹ የገጠማቸውን ለቀሪው ወታደር ስለሚናገሩ ወታደሩ በወኔ ለመዋጋት ይለግማል እነርሱም ተመልሰው ሓትን አይወጉም፡፡ የደርግ አባል የነበሩት ሌ/ኮሎኔል ደበላ ደንሳ ተመላሽ ‹‹ምርኮኞችን መልሶ ማዝመት›› ደርግን እንዲሸነፍ ያደረጉት ካሏቸው 13 ነጥቦች አንዱ ነው ብለዋል፡፡ ሠላማዊ ታጋዮች ተቀናቃኜ የሚሉትን አካል ከጎናቸው ማሰለፍ የሚችሉበትን ስልት መንደፍ አለባቸው፡፡ በሐሳብ በመብለጥ! የሓት ወገን የነበሩ በመሆናቸው ብቻ በለውጡ እንደማይቀጡ ዋስትና ይፈልጋሉ፣ ሁለተኛ በለውጡ ሐሳብ መማረክ አለባቸው፡፡
ሁለተኛው የሕዋሓት ብልሐት ደርግን የሚዋጋበትን መሣሪያ ከራሱ ከደርግ ማግኘት መቻሉ ነው፡፡ የአሁን ሰላማዊ ታጋዮች ሕዋሓት (ኢሕአዴግን ለማሸነፍ ወይም በዴሞክራሲያዊ ፓርቲ እና ስርዓት ለመተካት የራሱን መሳሪያዎች መጠቀም መቻል አለባቸው፡፡) ሕገ-መንግሥቱን፣ የመንግሥት መዋቅሮችን፣ የመንግሠት ሠራተኞችን፣ ወዘተርፈ ለሠላማዊው ትግል የሚፈይዱበትን ዘዴ መቀየስ ይበጃል፡፡

ትምህርት ሦስት
ሓት ትግሉ ሕዝቡ ውስጥ ስር እንዲሰድ ከረዱት መንገዶች መካከል ሳይጠቀስ የማይታለፈው ኪነትን መጠቀም መቻሉ ነው፡፡ በተለይ በዘፈን ረገድ የተሠሩ ሥራዎች በወኔ የሚቀሰቅሱ፣ ሕልም እንዲያልሙ የሚረዱ እና የራሳቸውን የዘመን ወግ (Folklore) መፍጠር የቻሉ ነበሩ፡፡ ለምሳሌ ‹ንገሪን እንደ ሐለፋይ . . . › የሚለው (በትርጉሙ ‹‹ንገሪኝ እስቲ እናቴ፣ ወዴት ነው የሄደው አባቴ?›› የሚል) የማሚት እና ብርሃነ (ሐለፋይ) የቅብብሎሽ (duet) ዘፈን፣ አሳዛኝ እና የተከፈለው መስዋዕትነት ለሚመጥነው ዋጋ መሆኑን የሚዘክር ዘፈን ነው፡፡ ይህንን ዘፈን ትግሪኛ ተናጋሪ ጓደኞቼን ‹‹ንገሪኝ እስኪ እናቴ፣ ለዚህ ነበር ወይ የሞተው አባቴ?› በሚል ምፀት እንዲቀይሩት ጠይቄያቸው በተለያዩ ምክንያቶች ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ . . . ጥበብ (ኪነ ጥበብ ይሁን ሥነ ጥበብ) በጥቅሉ ከአመፃዊ ይልቅ ለሠላማዊ ትግል መሣሪያ መሆን የችላል፡፡ በዚህ ረገድ በዓለማችን ብዙ ትምህርት የሚሆኑ ሥራዎችን አይተናል፡፡ የማርያ ማኬባ ፀረ-አፓርታይድ ዜማዎች፣ የቦብ ማርሌይ የነፃነት ሬጌምቶች፣ . . . እና በአገራችንም የቴዲ አፍሮ ‹‹ጃ ያስተሰርያል›› ከነዚሁ ተርታ ይመደባል፡፡ የቀድሞዎቹን የጦር ሽለላዎችና ቀረርቶዎች በመጠቀም ያውም ለዚህ ትውልድ ጆሮ በሚስብ መልኩ በሂፕሆፕ (ራፕ) መልኩ፣ የለውጥ ሰባኪ ግጥሞች ተጽፈውለት መሥራት ይቻላል፡፡ ኬናን የተባለ ካናዳ-ሶማሊያዊ ራፐር ይህንን አሳይቷል፡፡
በጥበብ ረገድ የሚደረጉ ሠላማዊ ተጋድሎዎች በዘፈን ብቻ ሊገደቡ አይገባም፡፡ በሥዕል፣ በሥነፅሁፍ፣ በቲያትር፣ ፊልም፣ ካርቱኖች እና ሌሎችም አማራጮች ቀርበው ሁሉንም እንደየፍላጎቱ ሊደርሱት ይገባል፡፡

…ይቀጥላል፡፡

ይህ ጽሁፍ በፍቃዱ ዘ ኃይሉ ‹‹ ጨዋ›› ነዎት ‹‹ባለጌ››? በሚል ርዕስ ከሚያወጣቸው ተከታታይ ጽሁፎች ውስጥ አንዱ ነው፡፡ 

No comments:

Post a Comment