Wednesday, August 20, 2014

የዛሬው ችሎት የዞን9 ጦማርያኑን እና የጋዜጠኞቹን የዋስትና ጥያቄ ውድቅ አደረገ

#Ethiopia #FreeZone9bloggers #FreeEdom #FreeTesfalem #FreeAsemamaw 

የልደታ ፍርድ ቤት 19 ወንጀል ችሎት የዞን9 ጦማርያኑን እና የጋዜጠኞቹን የዋስትና ጥያቄ ውድቅ አደረገ 

ስድስቱን የዞን ዘጠኝ አባላት ማለትም በፍቃዱ ኃይሉ፣ አቤል ዋበላ፣ ማኅሌት ታሁን፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ ዘላለም ክብረት እና አጥናፍ ብርሃነ እንዲሁም በሌለችበት ክሷ እየታየ ያለው በሶልያና ሽመልስ እንዲሁም በጋዜጠኞቹ ኤዶም ካሳዬ፣ ተስፋለም ወልደየስ እና አስማማው /ጊዮርጊስ በልደታ 19ኛው የወንጀል ችሎት ዛሬ ጠዋት የተሰየመ ሲሆን ከሙስሊም ኮሚቴ አመራሮች ጋር በአንድ ችሎት እንዲታደሙ በመደረጉ የታሳሪዎችን ቤተሰቦችም ሆነ ወዳጆችን ለማስተናገድ ቦታ የለም በሚል ለጋዜጠኞች ብቻ የፍርድ ሂደቱ እንዲታይ በፖሊስ ተፈቅዶ ነበር፡፡

በሌለችበት የተከሰሰችው ሶልያና ሽመልስ መጥሪያ በጋዜጣ መውጣቱን ፍርድ ቤቱ ያረጋገጠ ሲሆን የዋስትና መብትን በተመለከተ በዛሬው ዕለት ተሰይሞ የነበረው ችሎት በጸረ ሽብር አዋጁ መሰረት በአንቀጽ 3 የሽብር ተግባራት ተብለው ከተዘረዘሩት ውስጥ አንድም ወይም ሁለትም ከዚያም በላይ ወንጀል የፈጸመ መሆኑ ወይም ለመፈጸም ያቀደ ለመሆኑ ተገልጾ ክስ ሲቀርብ ነው በተመሰረተባቸው ክስ ዋስትናን ሊያሳጣቸው የሚችለው ብለው ጠበቆቻቸው የተከራከሩ ሲሆን ደንበኞቻቸው በአዋጁ መሰረት የሰሩት የሽብር ተግባር ክስ አልቀረበባቸውም ስለዚህ በአዋጁ ተጠቀሰ ማለት በአዋጁ መሰረት ክስ ቀርቧል ማለት ስለማይቻል የዋስትናው ጥያቄ በመደበኛ ስርዓት እንጂ በጸረ-ሽብር ሕጉ መሰረት ሊታይ አይገባም፤ በተጨማሪም አዋጁ ዋስትና ይከለክላል ተብሎ ቢተረጎምም ከሕገ-መንግስቱ ጋር ስለሚጋጭ ዋስትና ሊፈቀድላቸው ይገባል ቢሉም፤ ፍርድ ቤቱ አንቀጽ ተጠቅሶ መከሰሳቸውን እንጂ በዚህ መከሰስ ነበረባቸው ወይም አልነበረባቸውም ብሎ ለማየት ፍርድ ቤቱ አይገደድም እንዲሁም የጸረ-ሽብር አዋጁ ከሕገ-መንግስቱ ጋር አይጋጭም ብለዋል በዚሁም መሰረት የዋስትና ጥያቄውን ውድቅ ተደርጎ ለጥቅምት 5 ቀን 2007. ቀጠሮ በመስጠት የዛሬው ችሎት የተጠናቀቀ ሲሆን ጠበቆቻቸውም የዋስትና ጉዳይ በተመለከተ ለጠቅላይ ፍረድ ቤት ይግባኝ እንደሚያቀርቡም ታውቋል፡፡

ችሎት ውስጥ መግባት የቻሉት ጥቂት ጋዜጠኞች እና ጉዳዩን ለመታዘብ የተገኙ ዲፕሎማቶች ብቻ ናቸው፡፡

በቦታው በመገኘት አጋርነታችሁን ላሳያችሁ ሁሉ ከፍ ያለ ምስጋናችን ይድረሳችሁ፡፡

No comments:

Post a Comment